የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በጆርዳን ተቀጥረው ለሚሰሩ ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች ዝቅተኛው የወር ደሞዝ የተጣራ 275 ዶላር እንዲሆን መወሰኑን ሰምቻለው በማለት ሪፖርተር ጋዜጣ ዘግቧል።
ውሳኔው ባለፉት ሁለት ዓመታት የቤት ሰራተኞች ፍላጎት በጨመረባት ሀገር ጆርዳን የሚገኙ ከ20,000 በላይ ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች ላይ ተፈጻሚ የሚሆን መሆኑን ዘገባው ጠቅሷል።
ለሰራተኞቹ የደመወዝ ጭማሪ በአመት ይደረጋል የተባለ ሲሆን ለዚህም ከኢትዮጵያና ከጆርዳን መንግስት ተወካዮች የተውጣጣ ጥምር ኮሚቴ ተቋቁሞ ወቅታዊውን ሁኔታ ያገናዘበ የደመወዝ ጭማሪ እንዲደረግ ክትትል የሚደረግ መሆኑ ተገልጿል።
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በዚህ ሳምንት ባደረገው ስብሰባ በኢትዮጵያ መንግስት እና ጆርዳን መንግሥት መካከል የተደረገውን የመግባቢያ ስምምነት ያፀደቀ ሲሆን የመግባቢያ ስምምነት ሰነዱ ከቤት ሰራተኞች ውጪ ያሉ ለሌሎች በጆርዳን ተቀጥረው ለሚሰሩ ኢትዮጵያውያን የወር ደሞዝ ዝርዝሮችን ያላካተተ መሆኑ ተጠቁሟል።
ይህ የመግባቢያ ስምምነት ሰነድ የቤት ሰራተኞቹ በቀን 8 የስራ ሰዓት እንዲሰሩ እና በሳምንት 48 ሰአት የእረፍት ጊዜ እንዲሰጣቸው ያስቀመጠ መሆኑም ተጠቁሟል።
በርካታ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ለኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች በራቸውን የከፈቱ ሲሆን መንግስት ወደ ቀጠናው መጓዝ የሚፈልጉ ሰራተኞችን መደበኛ እና ህጋዊ ማድረግ የጀመረ ቢሆንም የሰራተኛ መብት ተከራካሪዎች የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ለቤት ሰራተኞች የሚከፍሉት ክፍያ ያነሰ ነው በማለት የሚተቹ ስለመሆኑም ነው የተገለፀው።
@TikvahethMagazine