የመጽሐፉ ርዕስ፦ አኰቴተ ቍርባን
የመጽሐፉ አዘጋጅ፦ ቀሲስ ዶ/ር መብራቱ ኪሮስ ገብሩ
የመጽሐፉ የገጽ ብዛት፦ 367
የመጽሐፉ ዋጋ፦ 230 ብር
የኅትመት ዘመን፦ 2012 ዓ.ም
የመጽሐፋ ዋና ዓለማ፦
1, የኢትዮጵያዊውን ሥርዓተ ቅዳሴ ውበቱን መግለጽና ጣዕሙን ማስረዳትና
2, ኢትዮጵያዊውን ቅዳሴ ላዘጋጁልን ቀደምት ቅዱሳን አባቶች እውቅና እንድንሰጥ ጥሪ ማቅረብና እውቅና መስጠት ነው።
መጽሐፉ እነዚህን ወርቃማ አላማዎች ይዞ በአራት ታላላቅ ምዕራፎች የተዘጋጀ፥ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሥርዓተ ቅዳሴ መሠረቱን፥ ታሪካዊ እድገቱን እና ይዘቱን የሚያሳይ በመረጃ የዳበረ፥ ጥልቅ ጥናት የተደረገበት ዳጎስ ያለ መጽሐፍ ነው።
ምዕራፍ አንድ፦ ቅዳሴ ምንድነው? በሚል ዐቢይ ርዕስ በመጀመር በአንድ ወቅት (1960ዎቹ) የሩሲያ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ አሌክሲ ለአንድ ጋዜጠኛ ቤተክርስቲያናቸውን "ቅዳሴ የምትቀድስ ቤተክርስቲያን" ብለው በገለጹበት ውብ አገላለጽ በመጀመር ቅዳሴ በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ከቃሉ እስከ ይዘቱ እንዴት እንደሚተረጎም፥ እንዲሁም ስያሜው በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ምን እንደሚመስል በአጭሩ በመግለጽ ይጀምራል። በቀጣይነትም በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የቅዳሴ መገለጫ ባሕርያት በሚል ንዑስ ርዕስ አማካኝነት አምስት የሚሆኑ ዋና ዋና የቅዳሴ ባሕርያት ተዳሰውበታል። በተጨማሪም የቅዳሴ ውበት በሚል ርእስ ሥር ቤተክርስቲያን በምድር ያለች ሰማይ መሆኗን፥ በውስጧም የሚከናወነው ሥርዓተ አምልኮም ሰማያዊ መሆኑን በመግለጽ ቅዳሴ በሥጋ፥ በነፍስና በመንፈስ የምንቀደስበት ውብ የሆነ የአምልኮ ሥርዓት ነው በማለት የቅዳሴውን ሰማያዊ ውበት በጥቂቱ ይገልጣል። በመጨረሻም የቅዳሴ መንፈሳዊ ዕሴቶች(ጥቅሞች) በሚል ሰማያዊ ውበት ባለው በቅዳሴው ተሳታፊ በመሆን ስለሚገኘው ጥቅምና ዋጋ፥ እንዲሁም ዘወትር የቅዳሴው ተሳታፊ እየሆንን ነገር ግን ምን መንፈሳዊ ለውጥ ለማይታይብን ደግሞ "ለምን ቅዳሴው አለወጠኝም?" በሚል መነሻ ጥያቄ ሰፊ ማብራሪያ በመስጠት ምዕራፉን በመደምደሚያ አሳብ ይቋጫል።
ምዕራፍ ሁለት፦ የጥንቷ ቤተክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ በሚል ዐቢይ ርዕስ በጥንቷ ቤተከርስቲያን የነበረው ሥርዓተ አምልኮና የቁርባን ምሥጋናና ጸሎታት ምን ይመስሉ እንደነበረ በመጠኑ ይዳስሳል። ይሄንንም ለማስረዳት የምሥጢረ ቁርባን አመሠራረት በሚል የጥንቷን ቤተክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ ለመረዳት የሚያግዙ የአይሁድ ሥርዓተ አምልኮ፥ ወንጌላትና ሐዋርያው ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች የላከው መልእክት(ስለ ቅዱስ ቁርባን የተጻፉ ምንባባት)፥ አጋፔ እና ቅዱስ ቁርባን፥ የቅዱስ አግናጥዮስ ዘአንጾክያ መልክታት የሚሉ የጥንቷን ቤተክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ ለመረዳት የሚያግዙ መንደርደሪያ አሳቦች ተነሥተውበታል። በመቀጠልም የጥንቷ ቤተክርስቲያን ቅዳሴያት በሚል ርዕስ የምዕራፉ ዋና አሳብ ይዘልቅና በአንደኛውና በሁለተኛው ክፍለ ዘመን መጻሕፍተ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን ምን እንደሚመስሉና ስለጥንቷ ቤተክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ ፍንጭ ይሰጣሉ የተባሉ ከጥንት እስከ አምስተኛው ክፍለ ዘመን የነበሩ መጻሕፍትና ጸሎታት በስፋት ተዳሰውበታል።
ምዕራፍ ሦስት፦ ይህ ምዕራፍ የመጽሐፉ ዋና ክፍል ነው። የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሥርዓተ ቅዳሴ መሠረት እና ታሪካዊ እድገት በሚል ርዕስ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሥርዓተ ቅዳሴ ዕድገቱ ምን እንደሚመስልና ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት የጥንቷን ቤተክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ መሠረት አድርገው በማስፋፋት ኢትዮጵያዊ መልክ ያለው ሥርዓተ ቅዳሴ እንደሠሩልን ይነግረናል። እንዲሁም የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሥርዓተ ቅዳሴ የዛሬውን መልክ ለመያዝ አራት የዘመናት ሂደቶችን እንዳለፈና እያንዳንዱን የዘመን ለውጥና እድገት በጥቂቱ በመዳሰስ ታሪካዊ እድገቱን ያስቃኘናል። እንዲሁም የግእዝ ሥነ ጽሑፍ ወርቃማ ዘመናት ማለት ከ15 እስከ 16ኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ድረስ ባሉ ዘመናት የተነሡ የነገረ መለኮት ክርክሮች ለግእዝ ሥነ ጽሑፍ መስፋፋትና ለሥርዓተ ቅዳሴ እድገት አይተኬ አስተዋጽኦ እንዳበረከተ በተለያዩ ማሳያዎች አስደግፎ ያስቃኘናል። በተጨማሪም በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ቅዳሴ ውስጥ ዓለማቀፍ ተቀባይነትን ባገኙ የቤተክርስቲያን አባቶች ስም የተሰየሙት ቅዳሴያት ስያሜው በተሰየመላቸው አባቶች የተደረሱ ሳይሆኑ የቀደሙት የኢትዮጵያ ቅዱሳን ሊቃውንት ከትሕትናና የድርሰቱን ተቀባይነት ከማጉላት አንጻር በሌሎች አባቶች ስም የተሰየሙ የኢትዮጵያ ሊቃውንት ሥራ መሆኑን የተለያዩ ማሳያዎችን በማስረጃ እያስደገፉ ጥናታዊ በሆነ መንገድ ድምዳሜ ላይ ይደርሳል።
በአጠቃላይ በዚህ ምዕራፍ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ ዕድገቱ ምን እንደሚመስል ከጥንት እስከ ዛሬ ያለውን ታሪካዊ እድገቱ የተቃኘበትና ቀደምት የኢትዮጵያ ቅዱሳን ሊቃውንት አባቶቻችን የነበራቸውን ዓለማቀፋዊ የቤተክርስቲያን ታሪክና የትምህርተ ሃይማኖት እውቀታቸው ምን ያህል ሰፊ እንደነበረና ያን እውቀታቸውን በመጠቀም ለሥርዓተ አምልኮ እድገት አስተዋጾ በማድረገ ዛሬ የሚገኘውን ውብ ሥርዓተ አምልኮ እንደሠሩልን ያስረዳል።
ምዕራፍ አራት፦ የቅዳሴ አጠቃላይ ይዘት በሚል ርዕስ የሚጀምር የመጽሐፉ የመጨረሻ ምዕራፍ ሲሆን በውስጡም ሦስቱን የቅዳሴ ክፍሎች ማለትም የዝግጅት ክፍል(preparatory service)፥ የትምህርት ክፍል(Lections) እና ፍሬ ቅዳሴ (anaphora) የተሰኙ ክፍሎችና በየክፍሉ የሚገኙ ጸሎታት፥ ዝማሬያት፥ ንባባትና ድርጊቶችን በጥንቷ ቤተክርስቲያን የነበራቸውን ቦታና ሥርዓት እንዲሁም በሌሎች አብያተክርስቲያናት (በኮፕቲክና ሶርያ) ጋር ያለውን ተመሳሳይነትና ልዩነት በማሳየት የጸሎታቱንና የዝማሬያቱን የትመጣነታቸውን በመጠቆምና የኢትዮጵያ ሊቃውንት ለጸሎታቱና ለዝማሬያቱ እንዴት ኢትዮጵያዊ መልክ እንደሰጧቸው በአባቶች መንፈሳዊ ጥበብ በመኩራትና በመደነቅ ከበቂ ማስረጃ ጋር አሰደግፎ ያሳየናል።
በተጨማሪም ቅዱስ ቁርባንን ከመቀበል በፊትና በኋላ ስለሚገኙ ጸሎታትና የጸሎታቱን ምንጮች ከየት እንደሆነ አጭር ዳሰሳ ያቀርባል። በመጨረሻም ስለ ቅድስት ቤተክርስቲያን ሕንጻና በውስጧ ስለሚገኙ ምሳሌያዊና መንፈሳዊ ትርጓሜ ስላላቸው ድርጊቶችና ምልክቶች እንዲሁም በሕንጻው የሚሣሉት ቅዱሳት ሥዕላት ሕንጻ ቤተክርስቲያንን እንዴት በምድር ያለች ሰማይ እንደሚያሰኛት ይነግረንና በቅዳሴው ውስጥ የምናያቸው የሥርዓተ አምልኮ ድርጊቶች የራሳቸው ትርጓሜ እንዳላቸውና ከእነዚህም ውስጥ የተወሰኑ ድርጊቶች በመዳሰስ በእነዚህ ድርጊቶች አማካኝነት በቅዳሴው የሚሳተፉ ምእመናን ሁለተናቸው የቅዳሴው ተሳታፊ በመሆን እንደሚቀደስ ይነግረንና በማጠቃላያ አሳብና መልእክት የምዕራፉና የመጽሐፉ ፍጻሜ ይሆናል።
በአጠቃላይ መጽሐፉ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያንን ቅዳሴ ውበቱንና ጣዕሙን፥ የአባቶቻችንን አስተዋጽኦ ከመጠቆም ባሻገር የቤተክርስቲያናችንን ሥርዓተ አምልኮ ታሪካዊ እድገቱ ምን እንደሚመስል ሰፊ ጥናት በማድረግ ለምእመናንና የነገረ መለኮት ደቀመዛሙርት በተለይም Liturgical Theology ውስጥ ላሉት ለተጨማሪ ጥናት በር የሚከፍትና የበለጠ የአባቶቻችን ድካም እንድንረዳና ዋጋ እንድንሰጥ የሚያደርግ በመረጃና በማስረጃ የበለጸገ ግዙፍ ጥናታዊ ሥራ ነው።
ይሄን የመሰለው ድንቅ መጽሐፍ ላበረከቱልን ለመምህራችንና ለአባታችን ለቀሲስ ዶ/ር መብራቱ ኪሮስ እግዚአብሔር ይስጥልን! ከእጅ ቁርጥማት ከደረት ውጋት ይሰውርዎት! ወርቃማ ብዕርዎት ትለምልም!
2.7K views£itsum, 14:36