Get Mystery Box with random crypto!

የስብዕና ልህቀት

የቴሌግራም ቻናል አርማ human_intelligence — የስብዕና ልህቀት
የቴሌግራም ቻናል አርማ human_intelligence — የስብዕና ልህቀት
የሰርጥ አድራሻ: @human_intelligence
ምድቦች: መዝናኛዎች
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 89.04K
የሰርጥ መግለጫ

በዚህ ቻናል
⚡ህይወትን የሚያንፁ የስነ-ልቦና ምክሮች
⚡መሳጭ የፍቅር ታሪኮች እና ወጎች
⚡ጥልቅ ማህበራዊ እና ፍልስፍናዊ እይታዎች
⚡ውብ የጥበብ ስራዎች
በፅሁፍ እና በድምፅ/Audio ይቀርባሉ።
#ሼር በማድረግ ወዶጅዎን የዚህ የእውቀት እና የጥበብ ድግስ ታዳሚ እንዲሆኑ ይጋብዙ።

Ratings & Reviews

4.00

2 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

2

3 stars

0

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 22

2022-05-01 20:55:34 ሽሽት
ከአሌክስ አብራሀም

@Human_Intelligence
9.8K viewsedited  17:55
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-05-01 19:44:04 እንኳን ኑሮ ተወደደ
መግቢያ መውጫ ስታጣ ትክክለኛ መፍተሄ ላይ ትደርሳለህ

ፍራሽ አዳሽ
ተስፋሁን ከበደ

@Human_Intelligence
@Human_Intelligence
9.9K viewsedited  16:44
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-30 21:18:34 #ይድረስ~ለእናቴ~ልጅ

ደምህ እና ደሜ
ከገነቱ ጠበል ከጊዮን ተቀድቶ
ስጋዬ እና ስጋህ
ከበረከት አፈር ከኤደን ተቦክቶ
ያውም በእግዜር ቃል
በተስፋዋ ምድር ሰው ሆኖ እነዳልኖረ
ያ ሁሉ ፍቅራችን
በትንሽ የዘር ክር ስለምን ታሰረ?
:
አንተ'ኮ ክብሬ ነህ
የመጎሴ ሚስጥር ህመሜን ታማሚ
እኔ'ኮ ደስታህ ነኝ
ከባድ ሀዘንህን ቀሎኝ ተሸካሚ፡፡

ያ'ንተ ዘር የኔ ዘር
ትሁፊቴ ትሁፍትህ ባህልህ ባህሌ
ዘመናት ስንኖር
ሳቄ ሳቅህ ነበር በደልህ በደሌ፡፡

ግሸን ስታስቀድስ
ለዱኒያ ዱአ ነጃሽ ካድሜአለሁ
እዛ'ና እዚህ ሆነን
በቁልቢ ስትምል በፂሆን ምያለሁ፡፡

ባ'ክሱም ስመፃደቅ
በ'ላሊበላ አለት ኩራት ተሰምቶሀል
በጀጎል ሳቅራራ
በፋሲለደስ ጌጥ አምረህ ሸልለሀል፡፡

ታዲያ ምነው ዛሬ
ዘመን ባጎደፈው በማይድን ነቀርሳ
በዘር አቅላሚዎች
አንድነትን ጠልተን ተለየን በጎሳ?
:
እባክህ ወንድሜ
ለባለቀን ብለህ ከፍቶህ አታስከፋኝ
አንተ ነህ ደስታዬ
ሲረግጡን ተረግጠህ ሲገፉን አትግፋኝ፡፡

ባይሆን ከረገጠን
ከገፋን ባለቀን ደም እየጨለጠ ከሰከረ ነፍሱ
በአንድነት ጠበል
ተጠምቀን እንዳን
ለለከፈን ሴጣን ፋቅራችን ነው ምሱ፡፡

[ልብ አልባው ገጣሚ]

@Human_Intelligence
@Human_Intelligence
11.9K views18:18
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-27 23:01:14 ኢትዮጵያውያን ምን ሆነን ነው ?
---------------------------------------

አንድ ገብረ ጉንዳን ከሌላ ገብረ ጉንዳን ጋር በቅንጣቢ ሥጋ ወይንም አጥንት “እኔ ልብላ፤ እኔ ልብላ” በማለት ቡድን ለይተው አይጫረሱም። ወይንም በአንድ ቀፎ የሚኖሩ የንብ መንጋዎች ከሌላ ቀፎ ከሚኖሩ የንብ መንጋ ጋር በሚቀስሙት አበባ ወይንም በሚቀዱት ውሃ ተጣልተው ተቧድነው ሲጠፋፉ አናይም።

ለዚህም ዋንኛው ምክንያት ከሰው ልጅ በስተቀር የተቀረው ሥነ ፍጥረት በሥርዓት የሚመራበት ሕገ ህላዌ በዘረመሉ (DNA)ውስጥ ተቀርጾበት መገኘቱ ነው። በዘረመላቸው በታተመባቸው ቅመም (DNA code) መሠረት አለቃ እና ምንዝሩ፣ ንጉሡ እና ሠራተኛው ተናበው እና ተሳስበው እንዲሁም ተባብረው ይኖራሉ።

የሰው ልጅ ግን እንደ ደማዊ ፍጥረታት በሕገ ተፈጥሮ ሳይሆን በሕገ አእምሮ የሚመራ ነፃ ፈቃድ ያለው ልዕለ ፍጡራን ነው። የሰው ልጅ ከአንድ ዝርያ (Homo Sapiens) ግንድ የተገኘ ፍጥረት ሆኖ ሳለ እርስ በእርሱ እንዳይናከስ እና እንዳይጠፋፋ የሚከለክለው ተፈጥአዊ ቅመም (DNA code) በተፈጥሮው የለውም፡፡

ከዚህም የተነሳ ይህንን ከመሰለ ማኅበራዊ ምስቅልቅል እንዲጠበቀው ለዘመናት ሰዋዊ እሴቶችን በተረክ (Myth) እና በታሪክ (History) መገንባት አስፈልጎታል። እነኚህም ክፉውን ለመኮነን በጎ የሆነውን ደግሞ ለማመስገን የምንገለገልባቸው በተለያዩ ማኅበረሰቦች ውስጥ ሥር ሰድደው የምናገኛቸው በትምህርት፣ በታሪክ፣ በሃይማኖት እና በባህል ውስጥ የሚገኙ ወግ እና ልማዶች ናቸው።

የሰው ልጅን ሞራል ለመግራት አነኚህ ማኅበራዊ እሴቶች ብቻቸውን በቂ ሆነው ስላልተገኙ የጥንታዊቷ ባቢሎን ንጉሥ ከነበረው ንጉሥ ሐሙራቢ ዘመን (ቅልክ 1792- 1750) ጀምሮ ደግሞ የተለያዩ የሲቪል ሕጎችን መደንገግ አስፈልጓል። እስከዛሬም ድረስ በዓለማችን የሀገሮችን ሕገመንግሥታት ጨምሮ በሺህ የሚቆጠሩ ሕጎች የሰውን ጠባይ ለመግራት እና ለማስገደድ የወጡ ናቸው፡፡

ከዚህ ሀተታ የምንገነዘበው የሰው ልጅ በትምህርት፣ በታሪክ፣ በሃይማኖት፣ በባህል ወዘተ ባዳበራቸው የሞራል ወግ እና በልማዶች የፈቃድ ሕጎች ብቻ ሳይሆን በሲቪል አስገዳጅ ሕጎች የማይመራ እና የማይገዛ ከሆነ እርስ በእርሱ ለመጫረስ አንድ ጀንበር ብቻ የሚበቃው አደገኛ አውሬ መሆኑን ነው።

ከላይ ባነሳሁት የማኅበረ ሰብእ ሳይንስ እውነት ላይ ተመሥርተን በሀገራችን ኢትዮጵያ ያለፍንበትንም ሆነ አሁን ያለንበት ማኅበራዊ ምስቅልቅል ምክንያት ስንጠይቅ እንደ አንድ ማኅበረ ሰብእ ያለፍንባቸውን የግማሽ ምእተ ዓመታት የቁልቁለት ጉዞ ብናጤነው ያጎደልነው ነገር ፍንትው ብሎ የሚታየን ይመስለኛል።

በተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪ ነገዶችም ይሁን እንደ ሀገር በጋራ ለዘመናት የገመድናቸውን ማኅበራዊ እሴቶች እና ውሎች በአብዮት ሰበብ በጣጥሰን ጥለናቸዋል። በነፃ ፈቃድ እንተዳደርባቸው የነበሩትን ልዩ ልዩ የትምህርት፣ የባህል፣ የሃይማኖት ወዘተ ወግ እና ልማዶቻችንን "ኋላ ቀር" የሚል ታርጋ ለጥፈንባቸው ነቃቅለን ጥለናቸዋል።

ፈላስፋው ዶ/ር ዕጓለ ገብረዮሐንስን የመሰሉ የሀገራችን ሊቃውንት አንደተነተኑት እንደ ሀገር ዘመናዊነትን ስንጀምረው ለዘመናት የቆየናቸውን ሀገራዊ አሴቶቻችንን ነቅለን ጥለን የአውሮፓውን ሥርዓተ ትምህርት ተከልን። ይህም ሀገሪቷን ከዐለት መሠረትዋ ነቅሎ አሸዋ ላይ እንደማቆም የሚቆጠር ነበር፡፡

በታሪክ አጥኚዎች ስምምነት መሠረት የዘመናዊት ኢትዮጵያ ታሪክ ከተጠነሰሰበት ዐፄ ቴዎድሮስ እስከ ዶ/ር ዐብይ ዘመን ድረስ ብናጠና አምስት ምድብ ሀገራዊ "ልኂቃን" ለየብቻ ሀገራዊ አበርክቶአቸውን ማየት ይቻላል።

ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ (Pioneers of Chenge in Ethiopia) በሚለው ድንቅ ጥናታቸው እንደሚገልጡት ኢትዮጵያን ከድንቁርና እና ከኋላ ቀርነት ለማውጣት የዐፄ ምኒልክ ዘመን ሊቃውንት ሀገራዊ ምዴል በማፈላለግ የደከሙ ሲሆን የዐፄ ኃይለሥላሴ ዘመን የነበሩት ደግሞ ዓለም አቀፍ ምዴል ፍለጋ ላይ ደክመው ነበር። (ጃፓን እንዴት ሰለጠነችን ያስታውሷል)

በደርግ ወታደራዊ አገዛዝ ዘመን ጉልበተኞች፣ በህወሓት ኢህአዴግ ዘመን ብሔርተኞች (ዘውጌ ልኂቃን) በመሰላቸው መንገድ "ሀገር ለማቅናት የሞከሩ" ሲሆን አሁን ያለንበት አምስተኛው ምድብ በብልጽግና (ኒዎ ኢህአዴግ) ዘመን ደግሞ የግጭት ጠማቂ (War lords) እና ብልጣ ብልጦች መንበረ ሥልጣኑን በመጨበጣቸው እንደ ማኅበረሰብ የምንፈወስበትን ሀገራዊ መድኃኒት ለማግኘት ሀሰሣው እስካሁን አልተሳካም።

ወደፊትስ ምን ይበጀን ይሆን ???

ዮሐንስ መኮነን

@Human_Intelligence
@Human_Intelligence
14.2K views20:01
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-25 21:38:43 እውነታን የመቀበል ምርጫ

አንደኛው ምርጫህ በየጊዜው በመንገድህ ላይ የሚደነቀሩ በፍጹም ልታስወግዳቸው የማትችላቸውን እንቅፋቶች ሲታገሉ መኖር ነው፡፡ ሌላኛው ምርጫህ ግን እውነታን ተቀብለህ፣ ዝንባሌህንና መንገድህን በመቀየር መገስገስ ነው፡፡

ታሪኩ ከተከሰተ ትንሽ ሰንበት ብሏል፡፡ በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ1989 ዓ/ም በጸሐፊነቱና በቀስቃሽ ተናጋሪነቱ የታወቀው ዴኒስ (Dennis Waitley) ከሺካጎ ከተማ ወደ ሎስ አንጀለስ የሚሄደውን የበረራ መስመር ቁጥር 191 ለመያዝ በመንገድ ላይ እንዳለ ትንሽ በመዘግየቱ ምክንያት በረራው ለጥቂት ያመልጠዋል፡፡ በአየር ማረፊያው ደርሶ ለመግባት ሲጣደፍ አይኑ እያየ የመቀበያውን ደጆች ሲዘጉት ተመለከተ፡፡ የዘገየው ለጥቂት በመሆኑ ምክንያት ወደ በረራው ለመግባት እንዲፈቀድለት ቢማጸንም እንኳን ስላልተፈቀደለት በጣም ይበሳጫል፡፡ በዚያው ቀን ከምሳ በኋላ ዋና ተናጋሪ ሆኖ ሊቀርብበት የሚገባው ስብሰባ ቀጠሮ በዚህ ምክንያት ተበላሸበት፡፡

ከአካባቢው ዘወር በማለት በመነጫነጭ ላይ እያለ፣ ከሃያ ደቂቃዎች በኋላ አንድ ሰበር ዜና ቀልቡን ይስበዋል፡፡ ለጥቂት ያመለጠው በረራ ገና በመነሳት ላይ አያለ በመከስከሱ በውስጡ ያሉት ሰዎች በሙሉ መሞታቸውን ተመለከተ፡፡ ንዴቱና ቅሬታው ወደ ድንጋጤ፣ ወደ ኃዘንና በኋላም “በረራው እንኳን አመለጠኝ” ወደሚል ሃሳብ ተለወጠ፡፡

ከአየር ማረፊያው ወትቶ ሆቴል በመያዝ ወደ ክፍሉ ገብቶ አረፍ ለማለት ሞከረ፡፡ በእጁ ላይ ያለውን የበረራ ትኬት በመመለስ ገንዘቡን ከመቀበል ይልቅ ትኬቱን ለማስታወሻነት ለማስቀመጥ ወሰነ፡፡ ይህ ትኬት የዘወትር አስታዋሹ ሆነለት፡፡ በአንድ ነገር በሚበሳጭበት ጊዜ ሁሉ ባለቤቱ እጁት ትይዘውና ወደዚያ ለማስታወሻነት ወደተቀመጠ የበረራ መስመር ቁጥት 191 ትኬት በመውሰድ ሁሉም ነገር ለመልካም እንደሆነ ታስታውሰዋለች፡፡

ዴኒስ፣ “እያንዳንዱ ቀን በሙሉ ኃይላችን ልንኖረው የሚገባን ስጦታ ነው” ሲል ይደመጣል፡፡ በዚህም መልእክቱ፣ መለወጥ የማንችለውን እውነታ ከመታገል ይልቅ ለመኖር ስለተፈቀደልን ደስተኞች ልንሆን እንደሚገባን ያስታውሰናል፡፡

ልክ እንደ ዴኒስ ምንም ብታደርግ ልትለውጣቸው የማትችላቸው “አናዳጅ” ገጠመኞች ዘወትር ከመንገድህ ላይ አይጠፉም፡፡ እነዚህ በየጊዜው መንገድህ ላይ የሚደነቀሩና ካሰብከው ሩጫ የሚገቱህ ገጠመኞች የሚሰጡህ ያለመመቸት ስሜት ወደ ስሜታዊነትና በዚያም ስሜታዊነት ተነድቶ ውሳኔን ወደመቀያየር ቀጠና የሚያስገባህ ከሆነ የጥሩ ምርጫ ሰው አይደለህም፡፡ ይህ አይነቱ የየእለት ገጠመኝና “እንቅፋት” በተገቢው ሁኔታ ካልተያዘ ለዋና ዋና የሕይወት አቅጣጫዎችህ እንቅፋት የሚሆንን ምላሽ እንድትሰጥ ሊጋብዝህ ይችላል፡፡

አንተ ከተረጋጋህና ከአቅምህ በላይ የሆኑትን ነገሮች ለፈጣሪ መልቀቅ ከተማርክ አንዳንድ እድል እንኳን አመለጠኝ . . . አንዳንድ ሰው እንኳን ከድቶኝ ሄደ . . . አንዳንድ የጀመርኩት ነገር እንኳን አልተሳካ . . . አንዳንድ ፍቅረኛ እንኳን እምቢ ብሎኝ ሄደ . . . የምትልበት ቀን ሊመጣ እንደሚችል ላስታውስህ!

“ምርጫና ውሳኔ” ከተሰኘው የዶ/ር
ኢዮብ ማሞ መጽሐፍ የተወሰደ

በቅንነት ሼር ያድርጉ

Join: @Human_Intelligence
Join: @Human_Intelligence
13.9K views18:38
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-25 21:14:30 መንጋነትን ተፀየፍ

ሲግመን ፍሮይድ፣ አርኪመድስ፣ ኒቼ፣ ቻርለስ ዳርዊን፣ ጋሊሊዮ፣ ሶቅራጥስ፣ ቡድሃ፣ ቶማስ ኤዲሰን፣ ቫን ጎ፣ የእኛው ሀገር ፈላስፋ ዘርዓያዕቆብ ... ሌሎችም ሌሎችም በየስርቻው በየጉራንጉሩ በእኛም ሀገር ጭምር አሉልህ፡፡ አብዛኞቹ በዘመናቸው የተወገዙ ወይ አድማጭ ያጡ ነበሩ፡፡ ዛሬ እግርህን በጀብደኝነት አንፈራጠህ ቆመህ ሰልፊ (ራስ በራስ ፎቶ) የምትነሳበትን ስልጣኔ የመሰረቱት ግን እኔው ዘመንን የቀደሙ የትናንት መሰሎችህ ነበሩ፡፡ ካምቤል ኢጁጋርጁክ የተሰኘ የካናዳ ካሪቦ ኢስኪሞ ጎሳዎችን መንፈሳዊ መሪ አባባል ይጠቅሳል፡፡ ኢጁጋርጁክ እንዲህ አለ....

"እውነተኛ ጥበብ ከሰው ልጅ ተሰውራ ትገኛለች፡፡ በታላቅ ሕመምና የብቻ አርምሞ ካልሆነ የሚደረስባት አይደለችም፡፡ ፈተናን መጋፈጥና ብቻነት ግን ወደዚህ ድብቅ ዕውቀት መገኛ ስውር ቦታ አዕምሮን ይመራሉ፡፡"

የምንኖረው ግን በጅምላ በሚመለክበት፣ በጅምላ በሚወገዝበት፣ በጅምላ በሚኮነንበት፣ ሽያጩም፣ ዘረፋውም፣ ግድያውም፣ ቀብሩም ጅምላ ሆኖ ተነጥሎ መቆም ወንጀል በሆነበት ማኅበረሰብ ውስጥ ነው፡፡

እናስ በዚህ ሂደት ከመንጋው የመነጠል፣ ከዘመን የመጣላት፣ ከትውልድ የመኳረፍ አዝማሚያ የሌለው ጠቢብ የመንጋውን መፈክር በውብ ቃላት ሸላልሞ ከማተም በስተቀር ረብ ያለው ሀቲት ሊወጣው ይችላልን? ምንኖረውን የሆነውን ለመጻፍ፣ ለመዝፈን፣ ለማቅለም፣ ለማሰማመር ብዙ መጣር አርቲስት መሆን ያስፈልጋል እንዴ? በየትኛውም ዘመን ተወለድ (በእኛም ዘመን ይሁን) ብዙዎች ከሚስማሙበት ከተለየህ፣ ብዙዎች የሚያደንቁት ካልመሰጠህ፣ ብዙዎች በጅምላ የሚጠሉትን ካልጠላህ ውግዘት ውርደት፣ ግዞት ይደርስብሃል፡፡ ምክንያቱም አንተ የሚቀጥለው ትውልድ አባል ነህ፡፡

የእኛን ነገር እንኳን ተውት፣ ተውት አዲስ አተያይ ማመንጨቱን፣ የሚቀጥለውን ትውልድ ትልም የማርቀቅ ቅብጠቱን ተውት... ተውት፡፡ እኛ ከዘመንና ከትውልድ መኳረፍ ያቃተን፣ ዘልማዳዊ የነተበ ሕይወት የማይሰለቸን፣ አንሰን አንሰን የምናሳንስ፣ በአጥንት እንደሚጣሉ የተራቡ ውሾች እርስ በእርስ የምንናከስ ሕዝቦች ነን፡፡

ለብቻ መቆም መቻል ግን ውበት ነው፡፡ ፅናት ነው፡፡ ጥንካሬ ነው፡፡ ለብቻ መቆም(solitude) መሟላት እንጂ መነጠል (isolate) አይደለም፡፡ መነጠል ብሎ ነገር የለም፡፡ የምትነጠለው ጉልህ ስብዕና አጥተህ ተጀምለህ የተቆጠርክ ዕለት ነው፡፡ እንደ ጉሬዛ ከዛፍ ዛፍ እየዘለልክ ብትኖር እንኳን ከሰው እንጂ ከምልዓተ ዓለሙ መነጠል አትችልም፡፡ ማንም ሁን ከየትም ና አንተ የምልዓተ ዓለሙ የልብ ትርታ ነህ። አንተ አንተን መሆን ከቻልክ ያለ አንተ ዓለሙ ይጎድላል፡፡

ተደርቦ ተጀምሎ መቆጠርን ተፀየፍ፡፡ በስብዕናህ ራስህን ችለህ ስትር ብለህ መቆምን ቻልበት፡፡ ሰዎችን በሙሉ ልብህ ተቀበል፡፡ ለመሸኘትም ግን ምንጊዜም ዝግጁ ሁን፡፡ በጊዜ ውስጥ አስቀድሞ ያልሆነ ምንም ነገር የለም፡፡ መወለድህም፣ መሸለም መጋዝም በጊዜ ውስጥ ቀድሞውኑ የታሰበ ነው፡፡ ይኼንን ማሰብ መቀበል ስለማትፈልግ ዘወትር ለእያንዳንዷ የሕይወት እርምጃ እንግዳ ትሆናለህ፡፡ ቀላል እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡

ይኼንን የምነግርህ እኔ እንኳን ዘወትር እንደ ተማሪ ነኝ፡፡ ከሰው ልትደበቅ ትችላለህ፡፡ ማንም ግን ከራሱ መደበቅ አይችልም፡፡ በራስህ ምላስ መቅመስ ካልቻልክ አንተ ጣዕምን አታውቃትም፡፡ ብቻህን መቆም ከቻልክ አንተ ነፃ ወጥተሃል፣ ክንፎችህን ሰርተሃል፡፡ ነፃ በወጣህ ጊዜ ሕይወትን በምልዓት ትኖራታለህ፡፡ ሁልጊዜ ከራሳቸው መታረቅ ተስኗቸው ቀላሉን መንገድ በመሻት እንደሚማስኑ ደካሞች አትሆንም፡፡

ግለሰቦች ሲሳሳቱ ስህተቱ ከራሳቸው ወይም በጣም ከጥቂቶች የተሻገረ ጥፋትን አያስከትልም፡፡ መንጋው ከተሳሳተ ግን አያድርስ ነው፡፡ የመንጋው፣ የጅምላው ስህተት የሚያደርሰውን የጥፋት መጠን ለማወቅ ሩዋንዳን መጥቀሱ ብቻ ይበቃል፡፡ መንጋው እንዲያውም ልክ ሆኖ አያውቅም ማለት ይቻላል፡፡ አንተ የዚህ የጅምላ ስህተት አካል መሆንን ተጸየፍ፡፡


አስቀድሜ እንዳወጋሁህ ዛሬ ዘመናዊው ዓለም የደረሰበትን የኑረት ቅኝት የቀረጹት ሺኅ እንኳን የማይሞሉ በራሳቸው መሻት ወይም በመንጋው ግፊት ተገልለው ማሰብ የቻሉ ጥቂቶች ናቸው፡፡ ሌላው ግብስብሱ ለድምቀት ለጭብጫባ ብቻ የሚፈለግ የቤተሙከራ አይጥ ሆኖ አልፏል፡፡ ያልፍማል፡፡ አንተም በፊናህ ጥቂት ስንኝ ቋጥረህ በብዙ የምታቧትር፣ በርካታ የግል አድናቂዎችን ቤት ለቤት እየዞርክ ለመፍጠር የምትማስን ሆነህ ባየሁ ጊዜ ግን አዘንኩልህ፡፡ አንተ ግን ከሰው ይልቅ ሰዎች በልጠውብህ ተቧድነህ ባሩድ ስታሸት ስትወራወር ባየሁህ ጊዜ አነባሁ፡፡

አንተ እኮ አንተ ነህ፡፡ በሰዎች መካከል ስትሆን ደቃቅ አሸዋ ላይ እንደወደቀች አንዲት የጤፍ ዘር ታንሣለህ፡፡ ምርጫህ በሌሎች ምርጫ ይወሰናል፡፡ ድምጽህ በሌሎች ጩኸት ይሸፈናል፡፡ ቁጣህ በሌሎች ግድየለሾች ፌዝ ይከለላል፡፡ ሕማም፣ ሕመምህ በሌሎች ለዛየለሾች ሁካታ ይጨፈለቃል...

ግለሰባዊነት ይለምልም!

ምንጭ-ከባዶ ላይ መዝገን
ደራሲ- ያዕቆብ ብርሀኑ

@Zephilosophy
@Zephilosophy
10.8K views18:14
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-25 10:18:23 የህይወት ልጓም

(Samuel Geda)

አንድ የሥነ-ሕይወት (Biology) መምህር ለተማሪዎቹ፤ 'አባጨጓሬ ወደ ቢራቢሮ የሚለወጥበትን ዑደት' እያስተማራቸው ነው። ለጥቆም፤ "በሚቀጥሉት ሰዓታት ከአባጨጓሬ ወደ ቢራቢሮ የተቀየረው አካል፡ ከዕጭ-ሽፋኑ (cocoon) ውስጥ ለመውጣት ትግል የሚያደርግበት ጊዜ ነው፤ ሂደቱን ከመመልከት ውጪ ታዲያ ማንም ቢራቢሮውን ለመርዳት እንዳይሞክር!" ብሎ በማስጠንቀቅ፡ ተማሪዎቹን ጥሎ ከቤተ-ሙከራው ይወጣል።

ተማሪዎቹም የሚሆነውን ለማየት በጉጉት ይጠባበቁ ጀመር፤ ልክ መምህሩ እንዳላቸውም ቢራቢሮው ከእጭ-ሽፋኑ (cocoon) ውስጥ ለመውጣት ይታገል ጀመር። ይሁንና ከተማሪዎቹ አንደኛው ልጅ የቢራቢሮውን ትግል ዐይቶ ያዝንና ከመምህሩ ትእዛዝ በተቃራኒ- ብራቢሮውን ከእጭ-ሽፋኑ ሊያወጣው ይወስናል። 'ትግሉን ባቀልለት' ሲልም የእጭ-ሽፋኑን ይሰብረዋል፤ ይሁንና እንደጠበቀው ሳይሆን ቀርቶ ከደቂቃዎች በኋላ ቢራቢሮው ይሞታል።

መምህሩም የተማሪዎቹን ሁኔታ ሊያይ ሲመለስ የተፈጠረውን ነገር ይነግሩታል። ይህን ጊዜ መምህሩ የእጭ- ሽፋኑን ለሰበረው ተማሪ፡ ሁኔታውን ያስረዳው ጀመር፤ "ቢራቢሮውን የገደልከው እርሱን ለመርዳት በማሰብህ ነው፤ ምክንያቱም ከእጭ-ሽፋኑ ለመውጣት ትግል ማድረጉ፡ አንተ እንዳሰብከው ቢራቢሮውን የሚጎዳ ሳይሆን ለክንፉ ጥንካሬና እድገት የሚረዳው ነበር። ይህ የተፈጥሮ ህግ ነውና። አንተ ግን ትግሉን በማቋረጥህ ወይንም በመከልከልህ ምክንያት ቢራቢሮው ሊሞት ችሏል።"

* * *
ይህ ህግ በህይወታችንም ይሠራል። ከትግል ውጪ ወደ ህይወታችን የሚመጣ (ምንም ዐይነት) ስኬት የለም። አንዳንዴ ወላጆቻችን ከሃዘኔታ ስሜት ተነስተው የትግል ህይወትን ከኛ በማራቃቸው ጎድተውናል፡ እንዳንጠነክርና እንዳናድግም አድርገውናል። ብዙውን ጊዜ ትግል ምቹ ሜዳን ስለማይፈጥርልን አንወደውም። የምንፈልገው ስኬት ሁሉ ያለ ትግል ሰተት ብሎ እንዲመጣ ነው። ስኬቱን እንፈልጋለን ትግሉን ግን አንፈልገውም።

አንድ ቢራቢሮ ቢራቢሮ ለመሆን-- ከእንቁላል ወደ እጭ (larva)፤ ከእጭ ወደ ሙሽሬ (pupa)፤ ከሙሽሬ ወደ አባጨጓሬ፤ ከአባጨጓሬ ወደ ቢራቢሮ፤ ከቢራቢሮነት መብረር እስከቻለባት ደቂቃና ሰአት ድረስ ያለውን *ትግል* ማለፍ የግድ ብሎታል። ልክ እንዲሁ፤ በህይወት ለማደግ/ለመለወጥ (ምንጊዜም) በትግል ውስጥ ማለፍን ይጠይቃል። ስኬት መፈለግህ ጤነኛና ብሩህ አእምሮ የመያዝህ ምልክት ነው። ይሁንና ስኬታማ ለመሆን ጥንካሬና እድገት የግድ ይሉሃል፤ እነርሱ የሚገኙት ደግሞ በትግል ውስጥ ነው።

ይኸውልህ፤ የህይወት ትልቁ ልጓም ምንድነው ካልን- ትግል ነው። ነጻነት ያለው ሰው ለመሆን እንጂ ነጻ ለመሆን መፈለግ የለብንም። ፈጣሪም ቅርፅ የሚሰጠን በትግል ውስጥ እያቀለጠ ነው። ምናልባት ልጓም- እርምጃን የሚገታ፣ እረፍት የሚያሳጣ፣ ምቾት የሚነሳ፣ ገደብ የሚጥል፣ ከመንገድ የሚያስቀር፣... ሊመስል ይችላል። ይሁን እንጂ፤ ልጓሙ- ከግብ የሚያደርስ፣ የተገራ ማንነትን የሚያላብስ፤ ብቁና ስልጡን የሚያደርግ፣ ወደ ዓላማ-መርና መርኽ-ገዝ ህይወት (Self actualization/realization) የሚያሳድግ፣ ጥንካሬን የሚሰጥ፣ ከሁሉ በላይ፡ ከራስ አልፎ ለሌላው የሚቆረስ ስብእና ባለቤት የሚያደርግ--ነው። ስለዚህ ትግል ማለት የስኬት ተቃራኒ ሳይሆን የስኬት አካል ነውና- ትልቁን የህይወት ልጓም- ትግልን አንጥላው!

መልካም ቀን

ሌሎችንም ያስተምር ዘንድ በቅንነት #ሼር ያድርጉ

Join: @Human_Intelligence
Join: @Human_Intelligence
11.9K views07:18
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-24 16:41:12 የሚያሳስበኝ
(በእውቀቱ ስዩም)

ይሄ ጨዋታ አይደለም፥
በቀደም ከሜክስኮ ወደ ፒያሳ የሚያወጣውን የቸርቺል አቀበት ስወጣ ሁለት ጎረምሶች ከግራ ቀኝ አጀቡኝ፤ አንዱ ናፕኪን እንድገዛው ጠየቀኝ ፤ ቸል ብየው ተራመድሁ፤ ከቀኘ ያለው ጎረምሳ ክንዴን አፈፍ አድርጎ ይዞ “ ብራዘር ርቦኛል የዳቦ መግዣ ስጠኝ “ አለኝ፤ ጣቶቹ ክንዴን ላይ የካቴና ያክል ከበዱኝ፤ ልመና ሳይሆን ልዝብ እገታ ይመስላል፥ በተቻለኝ መጠን ኮስተር ብየ ክንዴን እንዲለቀኝ ወተወትኩት፥ አለቀቀኝም፤ ናፕኪን የሚሸጠው ጉዋደኛውን ‘ ልቀቀው ፤ “ ብሎ ከገሰጸው በሁዋላ “ ግን ርቦን ነው “ የሚል ቃል ጨመረ፤ ድርድር መጀመሩ ነው፥ አስራ አምስት ብር መጽውቸ ተገላገልሁ፤ ወይም ለጊዜው የተገላገልሁ መሰለኝ።
ከጥቂት ቀናት በፊት ደግሞ ከፒያሳ ወደ ቀበና ስረማመድ ቱሪስት ሆቴል አካባቢ አንዲት ትንሽየ ልጅ እየሮጠች መጣችና ሱሪየን ይዛ ጎተተችኝ፤ ዝምብየ ተጎተትኩላት፥ ትንሽ ጎን ለጎን እንደተራመድን እግረኛው መንገድ ላይ አንድ የግድግዳ ሰአት የሚመስል ሚዛን የተዘረጋበት ቦታ ደረስን፤ ጩጨዋ ወደ ሚዛኑ ገፋችኝ፤
ሚዛኑ ላይ ወጣሁና “ ስንት ኪሎ ነኝ ?” ብየ ጠየቅሁዋት ፥
ሚዛኑን ቸል ብላ አይን አይኔን እያየች “ አንድ “ አለችኝና ገራም ፈገግታ አሳየችኝ፥
ሚዛኑ በምን መንገድ እንደሚሰራ እምታውቅ አይመስለኝም። ሚዛኑም ሰበብ ነው፤ ያልፎ ሂያጁን አንጀት በልታም ይሁን አስቸግራ ትንሽ ገንዘብ ሰርታ እንድትመለስ ከወላጆቹዋ የተሰጣት ተልኮ ወይም የተጣለ እዳ መሆኑ ገባኝ፥ ለተመዘነኩበት የሚጠበቅብኝ ክፍያ አንድ ብር ቢሆንም ከቦርሳየ አስር ብር አውጥቸ ከፈልኩ፥
“ አመስግኚው’ የሚል ድምጽ ሰማሁ፤ ዞር አልሁ አንዲት ሌላ መንገደኛ ልትመዘን ከሁዋላየ ወረፋ ይዛለች፥ ብላቴናይቱ ግን የሰጠሁዋትን ብር በትንንሽ እጆቸዋ አጣጥፋ ይዛ ፈገግ ብላ ከመቁለጭለጭ ውጭ የምስጋና ቃል አልወጣትም፤
መንገዴን ስቀጥል “ ግን እኮ አምሳ ብር ልሰጣት እችል ነበር “ ፤ የሚል ጸጸት እንደ አሜኬላ ጠቅ አደረገኝ፥ ብሰጣት ምን ዋጋ አለው፤ ማዶ ተቀምጦ በአይኔ ቁራኛ የሚከታተለን ሊስትሮ ሊቀማት ይችላል የሚል ማመኻኛ ፈጥሬ ራሴን ለማጽናናት ሞከርሁ፤ ከጥቂት ደቂቃ በሁዋላ ራሴን ለማጽናናት ያፈለቅሁት ሀሳብ የበለጠ ድብርት ለቀቀብኝ ፤
ድሮ ፥ በገርነቴ ዘመን ፥ የቅዱሳንን ገድል ሳገላብጥ ለንስሀ ሲሉ ራሳቸውን እየገረፉ የሚያሰቃዩ መነኮሳትን ታሪክ ማንበቤ ትዝ ይለኛል፤ በሸገር መንገድ ላይ ስረማመድ የሚሰማኝን ሀዘን ራስን እንደ መግረፍ ነው የምቆጥረው፥ አንድ የዘነጠ ካፌ ገብተህ በጣም አሪፍ ቁርስ ከበላህ ጸጋ ነው ፤ ግን በዙርያህ የከበበህን ድህነት እና ችጋር ስታስብ ንጹህና የሚጥም ቁርስ መብላትን ብቻ እንደ ትልቅ በደል እና መተላለፍ ትቆጥረዋለህ፥ ባዲሳባ መንገድ ላይ እየሄድኩ የምጋፈጠው ድብርት፥ ሳላውቀው፥ ይሄን በደል ለማስተረይ በራሴ ላይ የምጭነው ቅጣት ይሆን?
እየለመለመ የነበረው ያገራችን ኢኮኖሚ ይህ ነው የሚባል ፋይዳ በሌለው ጦርነት ምክንያት ደካክሟል፥
የተረፈው ያገራችን ሀብት በጥቂት ባለሀብቶች፥ ባለስልጣኖች እና የሀይማኖት ተቋሞች እጅ ተጠራቅሟል፥ አብዛኛው ህዝብ የሚኖረው የቀን ገደብ በሌለው ህማማት ውስጥ ነው፥ ሀብት የላቸው በሀብታቸው ስራ ይፍጠሩ፤ ባለጸጋ ላደረጓቸው ሰራተኞች ደመወዝ ይጨምሩ፤ ህዝብም መንግስትም ምርት የሚደረጀበትን እና በፍትህ የሚዳረስበትን መንገድ ይተልሙ፤ ሰው ሰራሽ ችግር ሰው ሰራሽ መፍትሄ አያጣም። ምኞቴ ነው፥

@Human_Intelligence
11.1K views13:41
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-24 16:00:07 ወንፊት ነፊ አትሁኑ

የእግዜር ቃል ሁሉን አቃፊ ነው። አጥርና መገደቢያ በዚያ የሉም። እና ለምን ይሆን የእናንተው በአጥር መከበቡ?

ምንጭ ፦ መጽሀፈ ሚርዳድ
ፀሀፊ፦ ሚካኤል ኔይሚ
ተርጓሚ፦ ግሩም ተበጀ

የእግዜር ቃል ማቅለጫ ነው። የቱንም አክብሮ የቱንም ሳያቀል፣ የፈጠረውን ሁሉ አቅልጦ አንድ ያደርጋል። የመረዳት መንፈስ አለውና፣ እርሱና ፈጠራው አንድ መሆናቸውን ሙሉ ለሙሉ ይረዳል-አንዱን ለይቶ አለመቀበል ሙሉውን አለመቀበል፣ ሙሉውን አለመቀበል ደግሞ ራሱን አለመቀበል መሆኑን ጭምር! ስለዚህም ዓላማና ትርጉሙ ለዘለዓለሙ አንድ ነው።

የሰው ልጅ ቃል ግን ወንፊት ነው። ከፈጠረው ውስጥ ገሚሱን አቅፎ ገሚሱን ይገፋል። ዘለዓለሙን፣ ይሄን ወዳጅ ብሎ እንዳቀረበ ያንን ጠላት ብሎ እንዳራቀ ነው - ነገር ግን ዘወትር የትናንት ወዳጁ የዛሬ ጠላት፣ የዛሬ ጠላቱ የነገ ወዳጅ እየሆነው

እናም፣ የሰው ልጅ ከራሱ ጋር በገጠመው ጨካኝ እና ፍሬ አልባ ጦርነት ሳቢያ ውስጡ በንዴት ፍሟል።

የዚህ ምክንያቱ ደግሞ፣ የሰው ልጅ፣ እሱና ፈጠራው ሌላም ሳይሆን አንድ መሆናቸውን፣ ጠላትን ማባረር ወዳጅን ማባረር፣ ጠላት ላይ በር መዝጋት ወዳጅ ላይ በር መዝጋት መሆኑን እንዲረዳ የሚያደርገውን ቅዱስ መንፈስ ስላጣ ነው። “ጠላት” እና “ወዳጅ" የሚሰኙት ሁለቱ ቃላትም የእርሱ ቃል፣ የእርሱ "እኔ" ፈጠራዎች ናቸው::

የጠላኸው እና መጥፎ ነው ብለህ የወረወርከውን ያለምንም ጥርጥር ሌላው ወድዶ እና ጥሩ ነው ብሎ ያነሳዋል። እውን አንድ ነገር በአንዴ ሁለት ተፃራሪ ነገሮችን መሆን ይችላልን? እውነታው ግን፣ ይሄኛውንም ያኛውንም አይደለም - ያንተው “እኔ” መጥፎ ሲያደርገው ሌላው “እኔ” ጥሩ እድርጎት እንጂ!

መፍጠር የሚችል፣ የፈጠረውን መልሶ እንዳልተፈጠረ ማድረግ እንደማይሳነው አልነገርኳችሁምን? ጠላታችሁን ራሳችሁ እንደፈጠራችሁት ሁሉ ራሳችሁ ጠላትነቱን ልታጠፉ ወይም ዳግም ወዳጅ አድርጋችሁ ልትፈጥሩትም ትችላላችሁ። ለዚያ ደግሞ የእናንተ “እኔ” ማቅለጫ ሊሆን ግድ ይለዋል። ለዚያ የመረዳት መንፈስ ያስፈልጋችኋል።

ስለዚህም ... እንዲህ እላችኋለሁ - ከጸለያችሁ ለመጀመሪያም ለመጨረሻም መረዳትን በመሻት ጸልዩ። ባልደረቦቼ ሆይ ... ወንፊት ነፊ አትሁኑ።

የእግዜር ቃል ሕይወት ነውና፤ ሕይወትም ሁሉም አንድ እና የማይከፋፈል ሆኖ የሚሰራበት ማቅለጫ ነች - ሁሉም በፍጽም ሚዛን፣ ሁሉም በደራሲው ቅድስት ሥላሴ ፊት ክብር የተቸረው ሆኖ! ባንተስ ፊት ምን ያህል የገነነ ክብር ይኖረው ይሆን?

መቼም ቢሆን በወንፊት አንገዋላዮች አትሁኑ ወዳጆቼ፤ ያኔ ሁሉን አቅፋችሁ፣ ሁሉን አልፋችሁ በገዘፈ ቁመና ትቆማላችሁ - ሊይዛችሁ የሚችል ወንፊትም አይኖርም።

አዎን ... ፈጽሞ በወንፊት አንገዋላዮች አትሁኑ ወዳጆቼ፡፡ የራሳችሁን ቃል ታውቁ ዘንድ፣ መጀመሪያ ነገር የቃሉን ዕውቀት እሹ። ቃላችሁን ስታውቁ ደግሞ፣ ወንፊታችሁን ለእሳት ትዳርጉታላችሁ። የእናንተ ቃል ገና መሸፈኛውን ያልገለጠ ቢሆን እንጂ የእያንዳንዳችሁ እና የእግዜር ቃል እንደሁ እንድ ነው!

ሚርዳድ መሸፈኛዎቹን ትጥሉ ዘንድ ይሻል...

የእግዜር ቃል፣ መቁጠር ያልጀመረ ጊዜ እና ያልተስፋፋ ቦታ ነው። እውን ከእግዜር ጋር ያልነበራችሁበት ጊዜ ነበረን? እግዜር ውስጥ ያልሆናችሁበት ቦታስ አለ? እና ታዲያ ዘላለምን በሰዓታት እና ወቅቶች የጠፈራችሁት ለምን ይሆን? ለምንስ ይሆን ቦታን በጋት እና ክንድ ለክታችሁ የገደባችሁት?

የእግዜር ቃል የማይወለድ ሕይወት ነው፤ ስለዚህም አይሞትም። እና ለምን ይሆን በልደት እና ሞት መከበባችሁ? በእግዜር ሕይወት ብቻስ አይደል የምትኖሩ? ሞት አልባውስ የሞት ሰበብ መሆን ይችላልን?

የእግዜር ቃል ሁሉን አቃፊ ነው። አጥርና መገደቢያ በዚያ የሉም። እና ለምን ይሆን የእናንተው በአጥርና መገደቢያ መከበቡ?

እኔም እላችኋለሁ፣ ሥጋ እና አጥንታችሁ እንኳ የእናንተ ብቻ ሥጋ እና አጥንት አይደለም። ሥጋ እና አጥንታችሁን እወሰዳችሁበት፣ መልሳችሁም የምትመልሱበት፣ ከዚያው ከምድር እና ሰማይ ገንቦ ውስጥ ስፍር ቁጥር የሌላቸው እጆች አብረዋችሁ ጠልቀዋል።

በዓይኖቻችሁ ውስጥ ያለው ብርሃንም የእናንተ ብርሃን ብቻ አይደለም። ፀሐይን አብረዋችሁ የሚጋሩት ሁሉ ጭምር እንጂ። ውስጤ ያለው ብርሃን ቢሆን እንጂ፣ ዓይናችሁ ከእኔ ምን ያይ ነበር? በዓይናችሁ ውስጥ ሆኖ የሚያየኝ የእኔው ብርሃን ነው። በዓይኔ ውስጥ ሆኖ የሚያያችሁ የእናንተው ብርሃን ነው፡፡ እኔ ድቅድቅ ጨለማ ብሆን፣ ዓይናችሁ፣ እኔን ሲያይ፣ ድቅድቅ ጨለማ ያይ!!!

በደረቶቻችሁ ውስጥ ያለው ትንፋሽም የእናንት ብቻ አይደለም። ዓየር የሚተነፍሱና፣ ተንፍሰው የሚያውቁ ሁሉ በደረቶቻችሁ ውስጥ እየተነፈሱ ነው። አሁን ድረስ ሳንባዎቻችሁን የሚሞላው የአዳም ትንፍሽ አይደለምን? አሁን ድረስ ልቦቻችሁ ውስጥ የሚመታው የአዳም ልብስ አይደል?

ሐሳቦቻችሁም የእናንተ ብቻ ሐሳቦች አይደሉም። የጋራ ሐሳብ ባሕር የእኔ ትላቸዋለች፤ እናም ደግሞ ያንን ባሕር ከእናንተ ጋር የሚጋሩ አሳቢ ፍጡራን ሁሉ..

ሕልሞቻችሁም ቢሆኑ የእናንተ ሕልሞች ብቻ አይደሉም። መላው ሁለንተና በሕልሞቻችሁ ውስጥ ያልማል...

ቤቶቻችሁስ ቢሆኑ - የእናንተ ብቻ አይደሉም። የእንግዶቻችሁ ማረፊያ፣ ቤቱን የሚጋሯቸሁ ፍጡራን ሁሉ የዝንቦች፣ የአይጥ የድመቱ ሁሉ ማደሪያ ናቸው።

ስለዚህም፣ አጥሮችን ተጠንቀቁ። ስታጥሩ በማጭበርበር ነው፣ እውነትንም ከአጥሩ ውጪ ታገልሏታላችሁ። አጥሩ ውስጥ ፊታችሁን ለማየት ስትዞሩ ደግሞ፣ ሌላው ስሙ ማጭበርበር ከሆነው ሞት ጋር ፊት ለፊት ግጥም!

መነኩሴዎች ሆይ፣ ሰውን ከእግዜር መለየት አይቻል ነገር! ሰውን፣ ከእግዜር ቃል ከወጡት ከብጤዎቹ የሰው ዘርና ከመላው ፍጡራን መለየትም እንዲሁ...

ቃሉ ውቅያኖስ ነው፤ እናንተ፣ ደመናዎችን! እና .... እውን ውቅያኖስን በውስጡ ባይይዝ ደመና ደመና ይሆን ነበር? ቢሆንም ግን፣ ቅርፅና ማንነቱን በሕዋው ላይ ቀርፆ ለዘለአለም ለማኖር ደፋ ቀና ሲል ሕይወቱን የሚያባከን ደመና ጅል ነው። ከተንኮታኮተ ተስፋ እና ከመሪር ከንቱነት በቀር ከዚህ የጅል ልፋቱስ ምን ያጭድ ይሆን?

ራሱን ካላጣ በቀር ራሱን አያገኝም። እንደ ደመና ሞቶ ካልጠፋ በቀር፣ ብቸኛ እኔነቱ የሆንውን፣ ውስጡ ያለውን ውቅያኖስ ሊያገኝ አይችልም።

ሰው፥ እግዜርን ያረገዘ ደመና ነወ። ከራሱ ባዶ ካልሆነ ራሱን የማያገኝ! አህ .... ባዶ የመሆን ደስታ- አህ፣ ባዶ የመሆን ሐሴት!

በቃሉ ውስጥ ለዘለዓለሙ ካልጠፋህ፣ አንተን ... እንዲያውም አንተነትህን የሆነውን ቃል መቼም አትረዳው! አህ ... የመጥፋት ደስታ፣ አህ ... የመጥፋት ሐሴት!

ደግሜ እላችኋለሁ ... መረዳትን በመሻት ጸልዩ። ቅዱሱ መረዳት ልቦቻችሁን ሲያገኘው፣ “እኔ” ባላችሁ ቁጥር በፈጣሪ ታላቅነት ውስጥ የደስታ ምላሽ የማይደውልላቸው አንዳችም ነገር የለም።

@Zephilosophy
@Zephilosophy
11.3K views13:00
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-04-24 11:07:16 ለመላው የክርስትና እምነት ተከታይ የቻናላችን ቤተሰቦች በሙሉ እንኳን ለብርሃነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ!!
መልካም በዓል!!
11.0K viewsedited  08:07
ክፈት / አስተያየት ይስጡ