2023-02-19 22:25:52
. ሰሙነ ሕርቃል “Heraclius Week”
⊙∗⊕━━✦༒ ༒✦━━⊕∗⊙
(መንደርደርያ ሐሳብ)
ሀገር ለቀው፣ ባህር ጠልቀው፣ ገደል ወድቀው የሚሰደዱትን መከራ ጸንቶባቸው የሚቸገሩትን በዓለም ሁሉ ያሉ ምእመናን ለስዱዳኑ ተስፋ፣ ለምንዱባኑ ረዳኤ፣ ለሕዙናን ናዛዜ፣ ለግዱፋን ዐቃቤ ፣ ለጽዑራን መጽንዔ የሆናቸው ክርስቶስ በቸርነት ይድረስላቸው
እንኳን ለዐቢይ ጾም ቀዳሜ ሳምንት (ዘወረደ፣ ሙሴኒ፣ ሰሙነ ሕርቃል…) በሠላም አደረሳችሁ!
☞ «መገለጫውን ሲያይ ነው እንጂ የጾሙትስ ሐዋርያት ናቸው»
☞ «ምንም አንድ አካል ሁለት ባሕርይ በማለት ብንለያይ ወረደ ተወለደ በማለት አንድ ነንና መጥተህ አጥፋልን»
☞ «ሰሙነ ሕርቃል ዘትከውን እምቅድመ ጾም ዐቢይ …»
#ሰሙነ_ሕርቃል ለጾመ እግዚእ የመሰናዶ ሳምንት [Preparation Weekinitial week] ተብሎ ተገልጧል። ከስምንቱ የዐቢይ ጾም ሳምንታት ከቅድስት ቀድሞ ለሚጾመው የዘወረደ ሳምንት አንዱ ምክንያት ሕርቃል ንጉሠ ሮም እንደሆነ ይታወቃል።
፲፪ኛው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ቅዱስ ዲሜጥሮስ ድኅረ አስተርእዮ ያለውን ፵ ዕለት ዐቢይ ጾም (A 40 day fast post Theophany) በ250 ዓ.ም. አውጆ በሮም በኢየሩሳሌምና በአንጾክያ በነበረችው አሐቲ ቤተክርስቲያን ቅቡልነት አግኝቶ ጸንቷል። ይህ ህርቃል ግን የተጨመረ በ616 እንደሆነ ይነገራል። ነገር ግን መጠሪያው የመሰናዶ ሳምንት ቀድሞ የነበረ እንጂ ሕርቃል በሚል እንዳልነበር መረጃ በማቅረብ የሚሞግቱ ቅብጣውያን አሉ። ኋላ ከ13ኛው ምዕተ ዓመት ወዲህ በኢብን አል አሰል በኩል ጾመ ሕርቃል (ሰሙነ ሕርቃል) በሚል ተለይቶ እንደተጠራ አስረጂ ጠቅሰው ይገልጻሉ።
(We find mention, of this week being referred to as “Hercules Week” as late as AD 1245 by Al-Safawy Le Ibn Al-Assal as being a fast distinct from the Great Fast proper )
በእኛም ዘንድ የጾሙን ምክንያት ሊቃውንቱም መጻሕፍቱም በተለያየ መንገድ ገልጠውታል።
፩) ጥንቱን ሐዋርያት ዐቢይ ጾምን ከእሑድ በቀር ቆጥረው ቢጎድልባቸው ቀድሞ ያለውን አምስት ቀን ከቁጥር ጨምረውታል።
፪) በኢየሩሳሌም የበራንጥያው ንጉሥ ፎቃ [Flavius Phocas Byzantine emperor ] ያደረሰባቸውን መከራ እና ጥፋት ያራቀላቸው ንጉሠ ሮም ሕርቃልን ምክንያት አድርገው ምዕመናነ ኢየሩሳሌም ስለጦሙት።
፫) የፋርስ ንጉሥ ክስራ [Kessra the king of Persia] በግብፃውያን ላይ ያደረሰውን መከራ ለማቅለል ንጉሥ ሕርቃል ዘምቶ ድል ቢነሳላቸው ሊቀ ጳጳሳቱ አባ እንድራኒቆስ በአዋጅ ከአጽዋማቱ ገብቶ እንዲቆጠር አድርገውታል።
፬) ንጉሥ ሕርቃል ግዙራን መንግሥቴን ይወስዳሉ ብሎ ቢሰጋ አይሁድን ዘምቶ ለመውጋት መሐላውን ቢያፈርስ የሮም ሊቃነ ጳጳሳት ቀሳውስት ዲያቆናት ምእመናን አንድነት ጹመውለታል። …
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምዕላድ የሆነው መጽሐፈ ስንክሳር በመጋቢት ፲ ምንባብ ሥር ነገረ መስቀሉ የሚከብርባቸውን ሁለት ምክንያቶች እንዳሉ ይነግረናል። አንደኛ ዕፀ መስቀሉ በኢየሩሳሌም ተቆፍሮ የተገኘበት ሲኾን ኹለተኛው ደግሞ ዕፀ መስቀሉ በፋርስ ንጉሥ በምርኮ ከወረደበት በሮሙ ንጉሥ ሕርቃል አማካኝነት ወደ ቆስጠንጥንያ የተመለሰበት ነው ይለናል። በአርኬውም የመጨረሻ አንጓ ላይ
"… መስቀል ተረክበ እምዘተኀብዐ ወገብረ መድምመ
በኢየሩሳሌም ቅድመ ወበፋርስ ዳግመ።" ይላል።
ከምርኮ የተመለሰበትን መንገድ በሚተርከው ክፍል ጥንተ ነገሩ እንዲህ ተቀምጧል።
✧ በሮሜ ንጉሥ በሕርቃል ዘመን የፋርስ ሰዎች በግብጽ አገር በበላይነት ኖረው ወደ አገራቸው ሊመለሱ ወደዱ። ከሹማምንቶቻቸው አንዱ የጦር መኰንን ተነጥሎ ወደ ኢየሩሳሌም አልፎ ደረሰ ወደ ከበረ መስቀል ቤተ ክርስቲያንም ገባ። መስቀሉም በላዩ በተተከለበት ግንድ ፊት ታላቅ ብርሃን ሲበራ አይቶ ሊያነሣው እጁን ዘረጋ። እሳትም ወጥታ እጁን አቃጠለችው። ከክርስቲያን በቀር ማንም ሊነካው እንማይችል የመስቀልን የክብሩን ነገር ሰዎች ነገሩት። ሁለት ዲያቆናትንም ይዞ የከበረ መስቀልን እንዲሸከሙ አዘዛቸው። ከኢየሩሳሌምም ብዙ ሰዎችን ማርኮ ወደ አገሩ ተመለሰ። የፋርስ ሰዎች ኢየሩሳሌምን እንዳጠፏት ብዙዎች ሰዎችንም እንደማረኩና የከበረ የክርስቶስንም መስቀሉን እንደ ወሰዱ የሮም ንጉሥ ሕርቃል በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ። ስለርሱም #እንዲጾሙ_ምእመናንን_አዝዞ ወደ ፋርስ ዘምቶ ወጋቸው ብዙዎችንም ገደላቸው የከበረ ዕፀ መስቀልንም እየፈለገ በአገራቸው ሁሉ ዞረ ግን አላገኘውም። ያ ዲያቆናቱንና መስቀሉን የወሰደ መኰንን ከቦታዎች በቤቱ አንጻር ባለ በአንድ ቦታ ላይ ወስዷቸው ጥልቅ ጉድጓድ እንዲቆፍሩ አዝዞ በዚያ የከበረ መስቀልን አስቀበረ እነዚያንም ዲያቆናት ገደላቸው። ነገር ግን ያ መኰንን የማረካት የካህናት ወገን የሆነች በእርሱ ቤት የምትኖር አንዲት ብላቴና ነበረች። እርሷ የከበረ መስቀልን ሲያስቀብርና ሁለቱን ዲያቆናት ሲገድላቸው በቤቱ ውስጥ ሁና በመስኮት ትመለከት ነበር ወደ ንጉሥ ሕርቃልም ሒዳ መኰንኑ ያደረገውን ሁሉ ነገረችው። ይህንም ንጉሥ ሰምቶ እጅግ ደስ አለው ያቺ ብላቴናም መራችው ከእርሱም ጋር ብዙ ሠራዊት ሁኖ ኤጲስቆጶሳትና ካህናትም ነበሩ። ወደ ቦታውም እስከምታደርሳቸው ያቺን ልጅ ተከተሏት ቆፍረውም የከበረ ዕፀ መስቀልን አገኙ ከዐዘቅቱም አወጡት ንጉሡና ሠራዊቱም ሰገዱለት። በልብስ መንግሥቱም አጐናጸፈው ታላቅ ክብርንም አከበረው ከሠራዊቱ ጋር እጅግም ደስ አለው ።
ይህንኑ በሚደግፍ ተወዳጁ ሊቅ የእስሙናዩ ቅዱስ ሳዊሮስ (Severus of El Ashmunein ﺳﺎﻭﻳﺮﺱ ﺍﻷﺷﻤﻮﻧﻴﻦ ) በድርሳኑ "ንሕነሰ ንጸውማ ንሥሓ በእንተ ሕርቃል ንጉሥ ሶበ ቀተሎሙ ለአይሁድ ወበልዐ ኪዳነ ዘተካየዶሙ ወዝንቱ ዕውቅ በዜና ሕርቃል ንጉሥ " ሲል ከነምክንያቱ አስረድቷል።
(እኛስ የምንጾመው ስለ ንጉሡ ሕርቃል ንስሐ ነው፤ አይሁድን በገደለ ጊዜ መኃላውን አፍርሷልና (ቃሉን በልቷልና) ይኽም በንጉሥ ሕርቃል ዜና የተነገረ ነው)
የመጽሐፈ ሕግ ወሥርዓት [ፍትሐ ነገሥት] ሐተታ ደግሞ መነሻው ከጥንት ሐዋርያት እንደሆነ በማውሳት ሌሎች እንደ ምክንያት የሚጠቀሱ ሁለት አጋዥ ታሪኮች አክሎ ያስቀምጥልናል።
በማከልም ከዐቢይ ጾምና ከረቡዕ ዓርብ (ጾመ ድኅነት) ውጪ የተጨመሩት አጽዋማት መነሻቸው የግብፃውያን ቀኖና እንደሆነም ፍትሐ ነገሥቱ ይጠቁማል።
«ወአጽዋምሰ አካልዓን እለ ተወስኩ ላዕለ ዝንቱ ወተሠርዑ በቤተ ክርስቲያን ቅብጣዊት። ወእምኔሆሙ ዘይከውን በአምሳለ ጾም ዐባይ በተጠናቅቆ። ወይእቲ ስሙነ ሕርቃል ዘትከውን እምቅድመ ፆም ዐቢይ»
(በዚህ ላይ የተጨመሩ ሌሎች ጾሞች ግን በግብፃውያኑ ቤተክርስቲያን የተሠሩ ናቸው፤ ከእነርሱም እንደ ዐቢይ ጾም በመጠንቀቅ የሚሆን አለ። ይህችውም ከዐቢይ ጾም ቀድማ የምትሆን የሕርቃል ጾም ናት)
በተለየ የሕርቃልን ጾም ሲያብራራ ደግሞ
⇨ ይህችውም ከዓቢይ ጾም አስቀድማ የምትሆን ስሙን ህርቃል ናት መገለጫውን ሲያይ ነው እንጂ የጾሙትስ ሐዋርያት ናቸው ሕልሙን ያየ ናቡደነፆር ሲሆን “ራእየ ዳንኤል” እንዲል
584 viewsተεพ๑δr๑ร (አግናጥዮስ)𝕿𝖊𝖜𝖔𝖉𝖗𝖔𝖘 𝕭𝖊𝖑𝖊𝖙𝖊 𝕸𝖊𝖓𝖌𝖎𝖘𝖙𝖚 Ignatius Theophoros (Ἰγνάτιος Θεοφόρος), 19:25