2021-12-26 21:46:39
የአብዮት ፍሬ ነኝ!
ብዙ ነገሮች ይናፍቁኛል። ብዙ ነገሮች በትዝታ ይመልሱኛል። በዚህች አጭር የእድሜ ልዩነት ይሄን ሁሉ ለውጥ ካየው በኔ ልጅ ዘመን ነገሮች ምን ያህል እንደሚለወጡ ሳስብ እንደ መደንገጥም እላለሁ።
ለውጥ 1
የድሮ መምህራኖች ማለት ...
አብዮት ፍሬ ነው የተማርኩት ። ይቅርታ አብዮት ፍሬ ነው ያደግሁት ...ሰላሳ አባትና ሰላሳ እናቶች ነበሩኝ።
የድሮ መምህራን እንደ ልጅ ይሳሱልሀል...እግር በእግር ይከታተሉሀል...ያፎካክሩሀል...ይመክሩሀል።
አይረሳኝም
መምህርት ብርቱኬ እኛ ከበናቸው.. .ግርማ ሞገሳቸው መቼም የእቴጌ መነን ነው። ኩርት ያሉ ቀብራራ...ሲኮሳተሩ ምድር ሆይ መቼ ነው የምትውጭኝ እንላላን....ሲንከባከቡን ደግሞ የእናታችንን ስም ለጊዜው እንዘነጋለን።
ታሪክ ሲተርኩልን በምናባችን እንጋልባላን...ከሚኒልክ ጋር እንዘምታላን...ጥልያንን አሳሩን እናበላዋለን መቼም !
የአድዋን ታሪክ ያፅፉናል...(ንግስታችንን ከበናል ... የባህርዛፉ ውዝዋዜ ራሱን የቻለ ዜማ ነው) .... አጤ ሚኒልክም...
አጤ ሚኒልክም (እንፅፋለን)...በመሀል የመምህራችን ንግግር አምልጧት የነበረችው ማርቲ ጔደኛችን ኤጭ! አለች ጮክ ብላ ።
ኤጭ?????!
በስመአብ !
መብረቅ የወረደብን ያህል ክው አልን። ማርቲ በቃ ዛሬ እንደበርበሬ ልትደለዝ ነው ብለን ስናስብ መምህራችን ነገሩን ወደ ቀልድ ቀየሩት
"በባዶ ቤት ያንጫጫሽ! "
አጤ ምኒልክ አልኩሽ እኮ.. ..ሳቅ ተጥለቀለቀ....
አሁን ያሉትን መምህራን አሰብኳቸው።
ኤጭ ለማለት አትሳቀቅም...አብረውህ ይቅማሉ...አብረውህ ይጠጣሉ...ፌስቡክ ቲክቶክ ላይ አብረውህ ይለፋደዳሉ...ግርማ ሞገስ የላቸውም።
ለውጥ 2
አምስተኛ ክፍል ስገባ አብዮት ፍሬ ውስጥ እናቴ የለሽም። ከ 1-4 ክፍል ነበር ያኔ የምታስታምር...ዛሬ ሀይስኩሉን ትሾፍረዋለች።
መንጠራ ትምህርት ቤት ሳለው የመምህር ልጅ የሚል አክብሮት ይቸረኛል። በእረፍት ሰዓት እንደ ንጉስ ከቆምኩበት ሆኜ ጮርናቄና ብርቱካን ይመጣልኛል። የትኛውም ልብ አለኝ የሚል ውሪ ቀና ብሎ አያየኝም።
አብዮት ፍሬ ስገባ ብቸኛ ነበርኩና በአይን ከማውቃቸው የምዳሰ ሰፈር ጀለሶቼ ጋር ተቀላቀልኩ።
አንዳንድ ግብረ ገብ ያልሆነ ነገራቸው ግን አማረረኝ። አንዱ ደህና ኩርኩም አልሶኝ ዞር ስል ከየት መጣ ያልተባለ ሌላ ኩርኩም አናቴን ይፈልሰኛል።
ጭራሽ ደግሞ የሆነች ጌምህን ካላመጣህ ብለው ወጠሩኝ።
ያቺ ጌም ያን ጊዜ ከ I phone 13 በላይ ክብር ነበራት ።
26 ነፍስን የሚያስቱ ጨዋታዎች ነበሯት። በተለይ የአውሮፕላን ውድድሩ ይምጣብኝ
ያቺን ጌም ይዣት ክፍል መጣሁ (ይዣት ባልመጣ እንደ ፊኛ ነፍተው ይጠልዙኛላ)
ምድረ ውሪ ከሌላ ፕላኔት እንደመጣ ፍጥረት ከበቡኝ።
ጭዌው ተጀመረ.. .ጌሟ ስትከፈት የሆነ ሰቅጣጭ ድምፅ ደግሞ አላት ...
ዲምዲሪሪሪንንንንንን...
ደግሞ ለክፋቱ ሂሳብ መምህራችን ጋሽ በሌ ከተፍ !
ጋሽ በሌ አበዱ ...
ጭራሽ ጌም ይዛችሁ ክፍል ውስጥ? (ይታያችሁ የዛሬ ተማሪ እኮ ብሉቱዝ ኤርፎኑን ሰክቶ ፖርን ፊልሙን ይለባልባል )
ጌሙ የማነው?
ከዚህች ጥያቄ በኋላ ውሪው ሀዋሪያት ጌታን በከዱበት ፍጥነት ከዱኝ። በተለይ ዮሀንስ ሶስት ጊዜ ጮሆ ሸመጠጠኝ። ይሁዳው ቦጌ በጣቱ ጠቆመኝ።
ቲቸር ወላጅ ካላመጣህ አትገባም አሉኝ።
አቤት ድንጋጤ!
አባቴ ተጠርቶ ጌም ይዤ ክፍል እንደገባሁ ሲነገረው አሰብኩት ። አንበርክኮ በዛ የአዞ ቆዳ ቀበቶው ሲያርገፈግፈኝ ሳልሁት (ቀበቶዋ ደግሞ አስጨናቂ ሳህለ ሚካኤል የሚል ጥሁፍ ተነቅሶባታል ።) እውነትም አስጨናቂ...
ያኔ እኔ ታማሚ ነኝ ብዬ አወጅኩ። ትምህርት ቤት ቅርት!
ሀኪም ዘንድ ሂድ እንቢ
ፀበል ሂድ ኸረ ምን በወጣኝ! ...እናቴ ተሸበረች...
ከሶስት ቀን በኋላ በራችን ተቆረቆረ ።
ጋሼ ሄዶ ሲከፍተው ጋሽ በሌ!
የኔ እየሱስ የጠፋሁባቸውን በግ ለመፈለግ መጡ።
ሚኪ ትንሽ አጥፍቶ ተቆጥቼው ነበር አሉ...
አስቡት ጌምን ለዛውም ጩኸቱ ከመድፍ የሚልቅ ጌም ይዤ ክፍል መግባት ትንሽ ጥፋት ሲሆን
ደንግጦ ቀርቶ ነው ብለው ቤተሰቦቼን አረጋጉልኝ ። ጥፋቴን እንኳ ሹክ አላሉም እኮ.. .ነገሮች ተድበሰበሱልኝ።
ከቀበቶ ውርጅብኝ አርነት ወጣሁ። በነጋታው ክፍል ስደርስ ከነዛ ቦዘኔ ውሪዎች አርቀው እዮብ የሚባል ጎበዝ ተማሪ ዘንድ አስቀመጡኝ።
ተመልከት የድሮ መምህር ጓደኛ ሰውን ምን ያህል ሊቀይር እንደሚችል የገባቸው ነበሩ።
እጅ ፅሁፌ ሲታይ ደብተሬ ላይ ዶሮዎች ፓርቲ ያዘጋጁ ይመስል ነበር ። እዮቤን እያየሁ እጄን ገራሁ !
የደብተሬ ልባድ የእብድ ቡትቶ ይመስላል ።
በጊዜ ሂደት ደብተሬን በወጉ መሸከፍ ጀመርኩ። ጭራሽ የመጀመርያው ገፅ ላይ ያለ ተሰጦዬ አበባ ሳልኩበት። አሁን ላይ ሆኜ ያን አበባ ሳየው ሳማም እንደመምሰል ይላል
የዛሬን ተማሪ አሰብኩት.. .
ወላጅ ሲባል ገና ሪሲኒንግ አስቦ ይዞ ከተፍ ይላል
የዛሬን ወላጅ አሰብኩት ...
የተማሪ ነፃነት...መብት ምናምን በሚል ማልያ መምህሩን ለመክሰስ ሲሯሯጥ...
የዛሬን መምህር አሰብኩት ...
የበደለውን ተማሪ ከማስተማር ይልቅ ለመጣል ሲጋጋጥ.. .
ይቀጥላል!
@wegoch
@wegoch
@wegoch
781 viewsDAVE / PAPI, 18:46