2023-01-01 17:20:29
እረሳለሁ እንጂ ባልረሳ ኖሮ ብዙ መርሳት የማልፈልገው ነገር ነበር!
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
የሃይስኩል ተማሪ እያለሁ በአጥር የመግባት ሱስ ነበረብኝ፡፡ጎበዝ ተማሪ ስለኾንኩ ብዙ ጊዜ ሽልማት አግኝቻለሁ፡፡ግን ምን ያደርጋል? ሽልማቴንም ልቀበል ስሔድ በአጥር ዘልዬ ካልገባሁ የተሸለምኩ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱን አላውቅም ግን በአጥር መግባት ያስደስተኝ ነበር፡፡ ምናልባት ትምህርት ቤቱ መግቢያ በር እንዳለው ስለምረሳ ይኾናል፡፡
.
አንድ ቀን እንደ ልማዴ የትምህርት ቤቱ በር ክፍት ሳለ በአጥር ዘልዬ ልገባ ስል ከአጥሩ ሥር የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተር ሁለት እጁን ዘርግቶ ተቀበለኝ፡፡ ተሸክሞ ካወረደኝ በኋላ ወላጅ ሳታምጣ እንዳትመጣ ብሎ አሰናበተኝ፡፡
.
ቤት ሔጄ ወላጅ አምጣ እንደተባልኩ እንዴት ብዬ ልናገር? ምክንያቱም ወደ ቤቴም የምገባው በአጥር ዘልዬ ነው፡፡ ትምህርት ቤት በዛ ከተባለ ወላጅ አምጣ ነው ሚለው. . .ወላጆቼስ ምን አምጣ ይሉኛል? ብዬ ፈራሁ፡፡ በርግጠኝነት አባቴ ‹‹ቀበቶዬን አምጣ!›› ነው ሚለኝ፡፡
.
ስለዚህ አንድ ወጣት አጎት አለኝ… እሱን ወላጅ ሁነኝ ብዬ ለሱ ነገርኩት፡፡ ወደ ሥራ ስሔድ በዛው እመጣለሁ ብሎኝ ቃል ገባልኝ፡፡ ሰኞ ሲደርስ ዳይሬክተሩ ቢሮ ቁጭ ብዬ አጎቴን መጠበቅ ጀመርኩ፡፡ ትንሽ አርፍዶ መጣ፡፡ ዳይሬክተሩ ንግግር ጀመረ፡፡
‹‹ልጁ ጎበዝ ተማሪ ነው…ግን ጋጠ-ወጥ የኾነ ተግባር ሲፈፅም ነው እጅ ከፍንጅ ወይም በሱ ኬዝ እጅ ከግንብ የያዝኩት፡፡ሁሌ በአጥር የሚገባ ስለኾነ ነው የጠራንዎት….ከዚህ በኋላ በአጥር ቢገባ ከትምህርት ቤት ነው እንደ ምናባርረው ልንነግርዎት እንወዳለን!››
አጎቴ በጣም ተቆጣ፡፡ ‹‹አንተ ስድ! ያምሃል? አንተ ትልቅ ሰው ነህ እኮ እንዴት እንደዚህ ታደርጋለህ? አጥሩ እኮ አርጅቷል…እኔ ራሱ አሁን በዚያ በኩል ነው ዘልዬ የገባሁት….ቢደረመስ እኮ ትጎዳለህ! ከአሁን በኋላ በጓሮ በኩል ሌላ አጥር ካለ ዳይሬክተሩ ያሣይህና በዛ ትገባለህ!››
.
ዳይሬክተሩ የመርሳት ችግሬን ከግምት ሳያስገባ "በአጥር እየዘለልክ ሕልምህን አታሳካም!" ብሎ እያፌዘ መከረኝ።
.
እውነት ለመናገር…..እዚህ ሐገር ውስጥ አጥር ዘለልክም አልዘለልክም ሕልምህን ማሳካት ቀላል ነገር ነው እንዴ? እኛ ሐገር ውስጥ በቀላሉ ሕልምህን ምታሳካው አጥሩ አንተ ከኾንክ ብቻ ነው፡፡
በዚህ ሰዓት እንኳን ሕልምህን ማሳካት ሕልምህን ማስፈታት ራሱ ከባድ ኾኗል፡፡
በፊት እንደዋዛ ቡና እየጠጡ ሕልማችንን የሚፈቱ ሰዎች አሁን የኾነ ሕንፃ ላይ ቢሮ ተከራይተው ‹‹ሕልምህን ኑር!›› የሚል የማነቃቂያ ቪድዮ እየቀረፁ ነው፡፡ በዚህ ዘመን ምንም ነገር በነፃ የለም፡፡ እንደውም አንዳንዴ ‹‹ነፃነት›› ያጣነው ‹‹ነፃነት›› የሚለው ቃል ላይ ‹‹ነፃ›› የሚል ነገር ስላለ ይመስለኛል፡፡ ምንም ነገር ለማድረግ ወይ ገንዘብ ወይ ሰው ሊኖርህ ይገባል፡፡ እስር ቤት ራሱ በሰው በሰው ነው ምትገባው፡፡ እስር ቤት ገብተው ዝነኛ ኾነው የወጡ ሰዎችን አላያችሁም? እንደውም ሮናልዶ ራሱ ሳዑዲ የገባው ሳዑዲ ውስጥ ሰው ስላለው ነው፡፡
.
እኔ ሕልሜ ትልቅ ነበር፡፡ቤተሰቦቼ የዘይት ሥራ ላይ ስለተሠማሩ በአፍሪካ ትልቁን የዘይት ፋብሪካ ለመመሥረት ሕልም ነበረኝ፡፡ ለሕልሜ ሚበቃ ጥሩ ውጤትም ነበረኝ፡፡ ‹‹እና ለሕልምህ ምን ያህል ቅርብ ነህ?›› ብላችሁ ከጠየቃችሁኝ ‹‹በወር አንድ ጊዜ ዘይት እንዳያመልጠኝ ሸማቾች እሰለፋለሁ!›› የሚል ነው መልሴ። ይኼን ያህል ብቻ ነው ለሕልሜ የቀረብኩት፡፡
.
አሁን ሌላ አዲስ ሕልም አለኝ፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ››የሁሉም ነገር ሥያሜ ከእኛ ነው የተወሰደው›› የምንለውን ዐመል አቁመን ማየት ነው ሕልሜ፡፡ ዛሬ ታክሲ ውስጥ አንድ መሸምገላቸውን ካላመኑ አንድ አዛውንት አጠገብ ተቀመጥኩ፡፡ገና ከመቀመጤ ‹‹እንኳን አደረሰህ ልጄ!›› አሉኝ፡፡ ‹‹ለምኑ?›› ስላቸው ‹‹ዛሬ እኮ ጃንዋሪ 1 ነው! አዲስ ዓመት ነው…ለአዲሱ ዓመት እንኳን አደረሰህ!›› ትንሽ ፈገግ ብዬ ‹‹አይ! እኔ በፈረንጅ አቆጣጠር አልቆጥርም›› ብዬ ዞር ልል ስል…..‹‹የለም! የለም! የፈረንጆች አይደለም፡፡ ጃንዋሪ የሚለው ሥያሜ ከእኛ ከኢትዮጵያውያን እንደተወሰደ አታውቅም?››(ጭራሽ ተቆጥተው ነው እንዲህ ሚሉኝ)፡፡
።
"በጥንት ጊዜ ሐበሾች ምንጠራራው ‹ጃል›› እየተባባልን ነው፡፡ እና በጣም ዝነኛ የነበረ አንድ ጦር ወርዋሪ ነበር፡፡ታዲያ ይኼ ሰው ሥሙ በጣም ረዥም ስለነበር ሰው ሁሉ ‹‹ወርዋሪ! ወርዋሪዬ!›› እያለ ነበር የሚጠራው፡፡ በሙሉ ሥሙ ሲጠራ ‹‹ጃል ወርዋሪ!›› ኾነ አትለኝም?! ከዚያ ንግሥት ኤልዛቤት ይኼን ሰው ወደ ኢንግሊዝ ጋብዘውት ከፈረንጅ ወርዋሪዎች ጋር ያወዳድሩታል፡፡ በውድድሩ ወቅት የፈረንጅ ኮሜንታተሮች ‹‹ጃል ወርዋሪ!›› ማለት ከብዷቸው ‹‹ጃን ዋሪ!›› አሉት፡፡ ከዚያ ጊዜ አንሥቶ በየዓመቱ ይኼ ውድድር የሚካሔድበት ወቅት ‹‹ጃንዋሪ›› ተባለ፡፡ የኛ ነው! ያለፈው ወር ‹‹ዲሴምበር›› ራሱ ‹‹ደሴ በር›› ከሚል አማርኛ የተወሰደ ነው፡፡
.
ራሳቸው የፈጠሩትን ተረት እውነት አድርገው ማውራታቸው ስላበሳጨኝ ስልኬ ላይ ተደፍቼ ጆሮ ነፈግኳቸው፡፡ ሰውዬው ግን ኮሮና ኾኑብኝ…‹‹አልተውህም!›› በሚል ዓይነት ወደ ስልኬ ስክሪን ተጠግተው ምን እያየህ ነው አሉኝ፡፡‹‹ክርስቲያኖ ሮናልዶ አል ናስር ለሚባል ክለብ መፈረሙን እያነበብኩ ነው›› አልኳቸው፡፡ ‹‹በነገራችን ላይ…›› ብለው ተረታቸውን ጀመሩ፡፡ ‹‹በነገራችን ላይ አል ናስር የሚባለው ሥም ከእኛ ከኢትዮጵያውያን የተወሰደ ነው! በድሮ ጊዜ ናስር የሚባል አንድ ወጣት ነበር፡፡ይኼ ቡናን ያገኘው ካሊድ ሚባለው ሰው አለ አይደል…የእሱ ታናሽ ወንድም ነው!››
.
ታሪክ መፍጠራቸው ብቻ አይደለም የገረመኝ፡፡ ‹‹የጃል ወርዋሪ አድናቂዎች ሕብረት›› ብለው ማኅበር እያቋቋሙ ነው፡፡ በዚህ ግርምቴ መሐል ሰውዬው ተሰናብተውኝ ከታክሲ ወረዱ፡፡ ከወረዱ ከደቂቃዎች በኋላ ስልኬ እንደሌለ ዐወቅኩ፡፡ ለ‹‹ጃል ወርዋሪ አድናቂዎች ሕብረት›› መቋቋሚያ ስልኬን አዋጣሁ ማለት ነው፡፡
.
የመርሳት በሽታዬን ለአሜሪካና ለቻይና እመኛለሁ፡፡ ዕዳችንን እንዲረሱልን፡፡በርግጥ ለአከራዬም እመኛለሁ፡፡ግን ለሐገሬ በደንብ እመኛለሁ፡፡ሐገሬን ይኼን ያህል ነው የምወዳት፡፡ ግን በሚያሳዝን ሁኔታ ሐገሬ እንደኔ የመርሳት ችግር ላለባቸው ዜጎች አትመችም፡፡ ልክ ለዓይነ ሥውራን መንገድ እንደማይስተካከለው ሁሉ፣ ለዊልቸር ተጠቃሚዎች መግቢያ እንደማይሠራው ሁሉ የመርሳት ችግር ያለባቸውም ዜጎች ይጉላላሉ፡፡
ለምሳሌ እያንዳንዱ ሕንፃዎች ላይ ስክሪን ተገጥሞ መርሳት የሚያጠቃቸው ሰዎች ለምን ወደ ሕንፃው እንደመጡ ቢያስታውስ…..ቀበሌ ላይ ‹‹ወዴት መሔድ ይፈልጋሉ?›› ከሚለው ጽሑፍ አጠገብ ‹‹ወዴት እንደሚሔዱ ማስታወስ ይፈልጋሉ?›› የሚል ጽሑፍ ቢኖር!...ለነገሩ መጀመሪያ ለቀበሌው ሠራተኞች ነው ምን ሊሠሩ እንደመጡ ማስታወስ ያለበት፡፡
.
@huluezih
@huluezih
577 viewsFa, 14:20