2022-09-11 13:42:06
መስከረምን እወዳታለሁ 4
.
(በየዓመቱ መስከረም 1 ላይ ብቻ የሚነበበው ታሪክ ክፍል 4 ቀጥሏል)
.
ልክፍት አለብኝ፡፡የማይለቅ የልብ ምች አግኝቶኛል መሰለኝ፡፡ ታዲያ ሰው በጤናው ያለ መስከረም ሴት የሌለ እስኪመስል ይኼን ሁሉ ዓመት ለሷ ይመንናል? ልጅነቴን በሙሉ ቃል አልባ አድናቆት ስችራት እንደ ልጅ ሳልጫወት አፍላነቴ አመለጠኝ፡፡ የትምህርት ዘመኔን እሷን ሳጠና ሰዋሁት፡፡ ደብተሬ ላይ ተጻፈች፣ ብዕሬ በሷ የመልክ፣የአረማመድ፣የአሣሣቅ ቀለም ተቀለመ፡፡ እነሆ ወጣትነቴና መስከረም ፊት ለፊት ተጋፍጠዋል፡፡ በወጣትነቴ ወደ ልጅነት እየመለሰችኝ፤ እንደ እምቦቀቅላ ልጅ ከዓይኔ ሥር ሳጣት እናቱ የሔደች ያህል እየተነፋረቅኩ አለሁ፡፡
.
ለእናንተ እንኳ ታሪኬን ማካፈል ከጀመርኩ አራት ዓመታት ተቆጠሩ፡፡ እነዚህ አራት ዓመታት ለእናንተ ይብዙ እንጂ ለእኔ በፀሐይ መግቢያ እና መውጫ መኻከል እንዳሉት ማለዳ እና ምሽት የተቀራረቡ ናቸው፡፡ ታዲያ ይኼ ‹‹ልክፍት›› ካልተባለ ልክፍት ምን ሊኾን ትርጉሙ? ይኼን ‹‹የልብ ምች›› ብዬ ካልጠራሁት ምን አቻ ሥያሜ ይገኝለታል?
.
በፊት ‹‹ብልሕ፣አርቆ አሳቢ፣ የበሰለ ልጅ፣ አስተዋይ›› የሚለኝ ሁሉ በመስከረም ምክንያት ‹‹ሞኝ፣ ጅል፣ ቂላቂል›› ማለት ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ስትጠራኝ ‹‹አቤት!›› ስትልከኝ ‹‹ወዴት?›› ስላልኩ ብቻ አድናቆታቸው ወደ ንቀት ተቀይሯል፡፡
.
በርግጥ ሞኝ ኾኜ አይደለም፡፡ መድረሻዋ ላይ ደርሳ መጨረሻዋን እስካላየሁ ድረስ በሷ ተስፋ አልቆርጥም፡፡ የአንድ ዕድለኛ ሰው ኃብት እስካልኾነች ድረስ የእኔ አይደለችም ብዬ አልተዋትም፡፡ ደግሞ ተስፋ እንድቆርጥ እሷም አትፈልግም፡፡ ስርቅ ትከተለኛለች፣ ስደክም የተስፋ ክብሪቷን ጭራ ወደ ነበርኩበት ትመልሰኛለች፡፡
.
መስከረም ምድር ላይ የምፈተንባት ብቸኛዋ ፈተናዬ ሳትኾን አትቀርም፡፡ ዝቅታዬን የእሷን መኖር ዐይቼ እጽናናባታለሁ፡፡ከፍታዬ በእሷ እርግጠኛ ስላልኾንኩ አላጣጥመውም፡፡ የምድር ላይ ግዞቴ ናት፡፡ ወዴትም መንቀሳቀስ አቅቶኛል፤ነፃነቴ ሙሉ አይደለም፡፡
.
እሷን መልዓክ አድርጌ ሳወራላቸው፣ ከአድናቆት በቀር ከአፌ ሲወጣ ባያዩ ‹‹እንዴት ከሰው ጉድፍ ጠፍቶ መልካም ጎኗን ብቻ ትተርካለህ? አይደክምህም ወይ?›› ይሉኛል ወዳጆቼ፡፡ መስከረም እንከን እንዳላት ዐውቃለሁ፡፡ አንድና ብቸኛዋ እንከን ኾኖ ሚታየኝ አባቷ ናቸው፡፡
አባቷ ከወዳደቀ ትራፊ ጭቃ የተፈጠሩ ይመስሉኛል፡፡ ትልቅ ሰው ስለኾኑ እርሳቸውን የሚመጥን ትልቅ ስድብ ያጣሁላቸው የትልቅ ቀላል ናቸው፡፡ ልጃቸውን ለመዳር ሳይኾን ለመሸጥ የሚማስኑ፣ ደስታዋን ሳይኾን ኪሷን ለማደለብ የሚጥሩ ቀላል ሽማግሌ፡፡አባት ለልጁ ዓሣ ማጥመድን ያሣያል እንጂ እንዴት የገነት ባሕር ውስጥ ዓሣ አጥምዶ ማምጣት የሚችል ሰው ይመለምላል?
.
የመስከረም ብቸኛው እንከን ስለመኾናቸው ሥማቸው ብቻውን ምስክር ኾኖ ይቆማል፡፡ ‹‹ጣሰው›› ይባላሉ፡፡ ‹‹መስከረም ጣሰው!›› ሲባል እንከን መኾኑ ዐይታይም? ሥማቸው የእኔን የአፍቃሪነት መብት እንደሚጥሱ አያሣይም? የተፈጥሮን ሕግ ጥሰው የፈካችን መስከረም ጥላሸት እንደሚያከናንቡ አይናገርም? ሥምን መላዕክ ያወጣል ይላል የሐገሬው ሰው…የእርሳቸውን ግን ራሱ የፈጠራቸው አምላክ ያወጣላቸው መኾን አለበት፡፡ ‹‹ሒድና! የዚህን አፍቃሪ ልብ ጣስ!›› ብሎ ሳይፈጥራቸው አይቀርም፡፡
.
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የመስከረም ልብ በአባቷ መርዛማ ምክሮች መጥቆር ጀምሯል፡፡ የነበራት የዋህነት በአባቷ መሰሪነት እየተሸረፈ መንምኗል፡፡ ወደ እናት የሚቀርበው ርህራሄዋ የአውሬነት ቆፈን እየወረረው ነው፡፡ ይታወቀኛል፡፡ቃሏ፣ እንቅስቃሴዋ፣ የከንፈሯ የሽሙጥ ሣቆች ጭካኔን እንደ መዝናኛ እየቆጠረች ስለመኾኑ ምስክር ናቸው፡፡
.
ከትዝታችን ይልቅ ዛሬ በማደርግላት ነገር ትተምነኛለች፡፡ በገዛሁላት ቁስ ልክ አብራኝ ትቆያለች፡፡ መግዛት ካልቻልኩ ‹‹መቆየት አልችልም!›› ብላ ሰበብ ከምራ ትሰለባች፡፡
ዐውቃለሁ፡፡እንደ ዘመኑ ሴት አማራጮቿን ሁሉ እኩል ዕድል እንደምትሠጣቸው፡፡ የተጠጋትን ሁሉ ክፍተት አበጅታ እንደምታስገባቸው፡፡ ደስታ ትልቅ ቦታ፣ትልቅ ኪስና ትልቅ ቤት ውስጥ ብቻ እንዳለ እንደምታስብ ሳትነግረኝ ይገባኛል፡፡ ርዝመቴና ስፋቴ በልቧ ሳይኾን ዙሪያዋ በሚያንዣብቡት መጤዎች መጠን እንደሚታያት ግልጽ ነው፡፡
.
የዛሬ ዓመት የአስተናጋጅነት ሥራዋን እየሠራች ነበር ይኼ ሁሉ የተገለጠልኝ፡፡ ተገልጦልኝ ገሸሽ ማለት አልቻልኩም፡፡ምክንያቱም ‹‹ልክፍቴ›› ናት፤‹‹የልብ ምቼም!!›› ተስተናጋጅ መስሎ የሚመላለሰው ያ ፓይለት አንካሳ ልቧን ሰብሮ፣የማይከርም ተስፋ ሠጥቷት፣ የሌለውን አለኝ ብሎ፣ ያላንቺ ሰው አይታየኝም ብሏት ልቧን ከወረሰው ወዲያ እዚህ ነኝ እዚያ ነኝ ሳይል ተሰወረ፡፡ የኋላ ጉዱን ቆይታ ሰማች፡፡ ልጆቹን በትኖ፣ ፓይለት ሳይኾን ቤት እያከራየ የሚኖር የዚሁ መንደር ሰው ነበር፡፡ እንባዋ ሲፈስ ከረመ፡፡ ያኔ እኔ ብቻ ነበርኩ ከጎኗ፡፡ እንባዋን ማበስ እንኳ ባልችል እንባዋ ሲፈስ ታዘብኩ፡፡ ከዚያ ያ ፓይለት ነኝ ባይ የሥራውን አገኘ፡፡ ፈጣሪ አሳድዶ ያፈሰሰውን እንባ አስከፈለው፡፡ ፈጣሪን አመሥግና እንደ ድሮ ትኾናለች ብዬ ማሰብ ስጀምር የአባቷ መርዝ ተጨምሮበት ያገኘችውን ሁሉ መበቀል ጀመረች፡፡ እኔም የፓይለቱን ግፍ ከፋይ ኾኜ ተሾምኩ፡፡ ያን ግዛልኝ፣ ይኼን አምጣልኝ አበዛች፡፡
.
አሁን ገባኝ፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ ‹‹መስከረም ጠባ›› የሚባለው፡፡ መስከረም የምትጠባው ኪስ ነው ለካ፡፡
.
ልብ እና ዘመን ለምን እንደማይጣጣም አይገባኝም፡፡ የተሠጠኝ ልብ በዚህ ዘመን ቦታ የለውም፡፡ የማንም መፈንጫ፣ የማንም መቀመጫ ኾኖ ቀረ፡፡ የደግ ዘመን ልብ በክፉዎች መሐል ዛፍ ላይ ኑር ተብሎ እንደተፈረደበት ዓሣ ነው፡፡ ልቤ እስኪሞት በመስከረም ተስፋ አልቆርጥም፡፡ መቼም ይኼን ሁሉ ስቃ ለምታበላኝ መስከረም የደረሰ ጌታ ለእኔ ሲኾን መርጦ ዝም ሚልበት ምክንያት አይኖርም አይደል?
.
(#ፈይሠል_አሚን)
.
@huluezih
@huluezih
757 viewsFeYsel Amin, 10:42