2022-10-02 11:59:23
በመተሐራ እና አካባቢዋ በታጣቂዎች ጥቃት መድረሱ ተሰማ
መስከረም 20/2015 ዓ/ም ከሰዓት በኋላ በመተሐራ አባድር 2ኛ ካምፕ ተብሎ በሚጠራ ቦታ በተፈጸመ የታጣቂዎች ጥቃት የ12 ሰዎች ህይወት ማለፉ የአካባቢው ኗሪዎች ገለጹ።
በትናንትናው እለት ጥቃት የፈጸሙት ታጣቂዎች በቁጥር 20 እንደሚሆኑ የገለጹት ኗሪዎች የተለያዩ መሳሪያዎችንም መታጠቃቸውን ገልጸዋል።
በጥቃቱ ህይወታቸው እንዳለፈ የአካባቢው ሰዎች ካረጋገጡልን 12 ሰዎች በተጨማሪ 8 ሰዎች ቀላል እና ከባድ አደጋ ደርሶባቸው በመተሐራ ሆስፒታል የህክምና እርዳታ እየተደረገላቸው ይገኛል። ከጥቃቱ የተረፉ የአካባቢው ኗሪዎች ከአባድር 2ኛ ካምፕ በመሸሽ የመኖሪያ ቦታቸውን ለቀው በመርቲ 1ኛ ደረጃ ት/ቤት መጠለላቸውን ይናገራሉ።
ህይወታቸው ያለፈ ሰዎች ዛሬ በመድሐኒዓለም ቤ/ክ የቀብር ስርዓታቸው ከቀኑ 9:00 ሰዓት እንደሚፈጸም ታውቋል።
በመተሐራ እና ዙሪያው የፈንታሌ ወረዳ አካባቢዎች የሚደርስ ተደጋጋሚ ጥቃት ቁጥሩ እየጨመረ መጥቷል የሚሉት ነዋሪዎቹ ከጥቃቶች በፊት የስልክ፣ የኢንተርኔት እና የመብራት አገልግሎቶችም በተደጋጋሚ እንደሚቋረጡ ይናገራሉ።
ከመስከረም 16 ጀምሮ እስከ መስከረም 18/2015 ዓ/ም ለተከታታይ 3 ቀናት የስልክ እና የኢንተርኔት ግንኙነት መቋረጡን ገልጸው መስከረም 19 ቀን አገልግሎቶቹ ቢመለሱም መስከረም 20 ቀን ከሰዓት ሙሉ ለሙሉ የመብራት፣ የስልክ እና የኢንተርኔት አገልግሎት መቋረጡን ይናገራሉ።
ትናንት የተቋረጡ ግንኙነቶች ዛሬ ጠዋት 2:00 ሰዓት ዳግም መመለሳቸውንም ነዋሪዎች ገልጸዋል።
በኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መስመር ላይም የተለያዪ ጥቃቶች መድረሳቸውን ለአዲስ ዘይቤ የተናገሩት ተጓዦች አሪቦና የተባለ አካባቢ የተቃጠለ የነዳጅ አመላላሽ ቦቲ መመልከታቸውንም ገልጸዋል።
37.9K viewsAyu, 08:59