2023-03-28 17:44:35
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዓለም ዐቀፍ የሴቶች ታሪክ ወርን አከበረ
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዛሬ መጋቢት 19 ቀን 2015 ዓ.ም. ዓለም ዐቀፍ የሴቶች ታሪክ ወርን አከበረ። የቦርዱ አመራር አባላትን ጨምሮ የቦርዱ ሠራተኞች የተገኙበትን መድረክ በንግግር የከፈቱት የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ ሲሆኑ፤ በንግግራቸውም ቦርዱ የሴቶችን ተሣትፎ ለማረጋገጥ በሕጎቹ ላይ ካኖራቸው አስገዳጅ ድንጋጌዎች በተጨማሪ፤ በተግባር በ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ተግባራት ላይ የቦርዱ ሴት አመራሮችና ባለሞያዎች በቁጥጥር እንዲሁም በአመራር ሰጪነት ያሳዩት የአፈጻጸም ብቃት ዕኩል ነን ከማለት ባለፈ ዐቅማቸውን በተግባር ያረጋገጠ ጭምር እንደነበር አስታውሰዋል።
የዕለቱ የክብር እንግዳ ከሆኑት ዘውዴ አበጋዝና አምባሳደር ታደለች ኃይለሚካዔል ጋር የፓናል ውይይት የተደረገ ሲሆን፤ በውይይቱም በሴቶች መብት ተሟጋችነትና ባለሞያነት ያካበቱትን የሕይወት ልምዳቸውን፣ የሴቶች ትግል በዘመናት ውስጥ የነበረውን ዓይነተኛ ባህሪያት፣ የተደረጉ ጥረቶች፣ የተገኙ ስኬቶችና የታለፉት ተግዳሮቶችን አስመልክቶ በዝርዝር ሃሳባቸውን አካፍለዋል።
የፓናል ውይይቱን ተከትሎ ቦርዱን ከሦስት ዓሥርት ዓመታት በላይ ላገለገሉ ሴት ባለሞያዎች የዕውቅና ሠርተፍኬት በዋና ሰብሳቢዋ አማካኝነት የተሰጠ ሲሆን፤ የሕይወት ልምዳቸውንም እንዲሁ እንዲያጋሩ ተደርጓል። በመጨረሻም የቦርዱ የሥርዓተ ፆታና ማኅበራዊ አካታችነት የሥራ ክፍል ቀደም ሲል ይህን መድረክ ታሳቢ አድርጎ ባካሄደው ውድድር አሸናፊ ለሆኑት ሴት የቦርዱ ባለሞያዎች የአጭር ጊዜ ነፃ የትምህርት ዕድል እንዳመቻቸላቸው አስታውቆ የመድረኩ ማብቂያ ሆኗል።
133 views14:44