Get Mystery Box with random crypto!

ኢ.ዜ.አ

የቴሌግራም ቻናል አርማ ethiopianewsagency — ኢ.ዜ.አ
የቴሌግራም ቻናል አርማ ethiopianewsagency — ኢ.ዜ.አ
የሰርጥ አድራሻ: @ethiopianewsagency
ምድቦች: ያልተመደበ
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 434
የሰርጥ መግለጫ

The Ethiopian News Agency dispatches text news, audio and video stories about local and international events to media enterprises and the public.
www.ena.et
facebook.com/ethiopianewsagency
Call
1(202) 205-9932 Ext 13

Ratings & Reviews

3.00

2 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

0

3 stars

2

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች

2022-08-03 19:23:38 ረቡዕ ሐምሌ 27/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ አዲሱ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል አራት ዋና ከተሞች እንዲኖሩት ረቂቅ አዋጅ ማዘጋጀቱን የክልሉ ኮምንኬሽን ቢሮ አስታውቋል። በብዝሃ ዋና ከተሞች ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ ላይ፣ ቦንጋ፣ ተርጫ፣ ሚዛን አማን፣ ቴፒ ከተሞች እኩል የክልሉ መቀመጫ እንዲሆኑ ተደንግጓል። በረቂቅ አዋጁ መሠረት፣ ቦንጋ የክልሉ የፖለቲካና የርዕሰ መስተዳድሩ ጽሕፈት ቤት፣ ተርጫ የክልሉ ምክር ቤት፣ ሚዛን አማን የዳኝነት አካሉ እንዲሁም ቴፒ የብሄረሰቦች ምክር ቤት መቀመጫዎች ይሆናሉ።

2፤ በኦሮሚያና ሱማሌ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ካንድ ወር ወዲህ በተቀሰቀሰ ግጭት ከ8 ሺህ በላይ ነዋሪዎች መፈናቀላቸውን ሰምተናል። አብዛኞቹ ተፈናቃዮች ከኦሮሚያው ባሌ ዞን ደሎ መና ወረዳ በአምስት ቀበሌዎች መጠለላቸውን ዘገባው አመልክቷል። የግጭቱ ምክንያት የመሬት ሽሚያ፣ ወሰን ዘለል እርሻ እና የኢንቨስትመንት መስፋፋት የፈጥፕረው የመሬት እጥረት ናቸው ተብሏል። በአካባቢው ግጭቱ እና መፈናቀሉ ብዙ ዓመታት ያስቆጠረ ነው። ባለፈው አንድ ወር ውስጥ በክልሎቹ አዋሳኝ አካባቢዎች በተፈጠረው ግጭት፣ የሰዎች ሕይወት መጥፋቱን ተፈናቃዮች ተናግረዋል።

3፤ በአፍሪካ ቀንድ የአፍሪካ ኅብረት ልዩ መልዕክተኛ ኦሊሴጎን ኦባሳንጆ የሰሜን ኢትዮጵያውን ጦርነት በድርድር ለመፍታት እየተደረገ ስላለው ጥረት ነገ ለኅብረቱ ሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት ማብራሪያ እንደሚሰጡ ከኅብረቱ የወጡ ሪፖርቶች አመልክተዋል። ኦባሳንጆ ባለፉት ሁለት ወራት ከኢትዮጵያ መንግሥት እና ሕወሃት ጋር ባደረጓቸው ውይይቶች ዙሪያ ለምክር ቤቱ ሪፖርት ያደርጋሉ። በመድረኩ ላይ የኢትዮጵያ መንግሥትና የኢጋድ ተወካዮች መግለጫ ያቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል። ኦባሳንጆ ለምክር ቤቱ በጉዳዩ ላይ የመጨረሻውን ማብራሪያ የሰጡት በየካቲት ወር ነበር።

4፤ በተመድ የአሜሪካ ቋሚ መልዕክተኛ አምባሳደር ሊንዳ ቶማስ ግሪንፊልድ ዛሬ በአፍሪካ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ይጀምራሉ። ግሪንፊልድ በአራት ቀናት የአፍሪካ ቆይታቸው፣ ኡጋንዳን፣ ጋናን እና ኬፕቨርድን እንደሚጎበኙ ተናግረዋል። ግሪንፊልድ ጉብኝታቸው የሩሲያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌ ላቭሮቭ በቅርቡ በአፍሪካ ያደረጉትን ጉብኝት ዒላማ ያደረገ እንዳልሆነ ተናግረዋል። አፍሪካዊያን ከአሜሪካና ከሩሲያ አንዱን እንዲመርጡ አንገፋፋም በማለት ትናንት የተናገሩት ግሪንፊልድ፣ ሆኖም ሩሲያ ስለ ዩክሬኑ ጦርነት የምትነዛውን የሐሰት ትርክት እንዲያምኑ አንፈልግም ብለዋል።

6፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 52 ብር ከ1698 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 53 ብር ከ2132 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 60 ብር ከ9973 ሳንቲም፣ መሸጫው 62 ብር ከ2172 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ53 ብር ከ4688 ሳንቲም ሲገዛ እና በ54 ብር ከ5382 ሳንቲም ሲሸጥ ውሏል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
36 viewsedited  16:23
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-01 21:13:15 ሰኞ ሐምሌ 25/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ ገንዘብ ሚንስቴር ክልሎች ከሚሰበስቡት የንብረት ታክስ ገቢ ውስጥ 25 በመቶውን ፌደራሉ መንግሥቱ እንዲወስድ የሚያዝ ረቂቅ ሕግ ለፌደሬሽን እና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤቶች መምራቱን ገለፀ። ሆኖም ሕጉ ከመጽደቁ በፊት፣ ፌደሬሽን ምክር ቤት እና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የክልሎች የንብረት ቀረጥ ገቢ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ክሎች እና ፌደራል መንግሥቱ የሚጋሩት የጋራ ገቢ ስለመሆን አለመሆኑ በቅድሚያ መወሰን አለባቸው። ክልሎች በዋናነት የንብረት ቀረጥ ገቢ የሚሰበስቡት ከከመሬት መጠቀሚያ፣ ከሕንጻዎች እና ሌሎች የግል ንብረቶች ነው።

2፤ በደቡብ ክልል የስልጤ ዞን ምክር ቤት ዞኑ ከደቡብ ክልል ተነጥሎ ከሌሎች መሰል የአስተዳደር መዋቅሮች ጋር አዲስ ክልል ለመመስረት የቀረበለትን የውሳኔ ሃሳብ በአብላጫ ድምጽ ማጽደቁን አስታውቋል። የዞኑ ምክር ቤት ውሳኔውን ያሳለፈው፣ ከሀዲያ፣ ከምባታ ጠምባሮ እና ሀላባ ዞኖች እና ከየም ልዩ ወረዳ ጋር በሕዝበ ውሳኔ በሚመሰረት አዲስ ክልል ስር ለመዋቀር ነው። የጉራጌ ዞን ምክር ቤትም ተመሳሳይ ውሳኔ ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል። ሌሎቹ የአስተዳደር መዋቅሮች በአዲስ ክልል ስር ለመዋቀር ውሳኔ ያሳለፉት ትናንት ነው።

3፤ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የደቡብ ክልል ምክር ቤት ተወካዮች ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ርዕስቱ ይርዳው ጋር በዚህ ሳምንት ሊወያዩ መሆኑን ገለፀ። የመወያያ አጀንዳው በክልሉ ውስጥ በርካታ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ያነሱት የክልልነት አደረጃጀት ጥያቄ እንደሚሆኑ ምንጮች መናገራቸውን ዘገባው ጠቁሟል። ባለፉት ጥቂት ቀናት በርካታ የክልሉ አስተዳደራዊ መዋቅሮች በሁለት አዲስ ክልሎች ለመዋቀር ያሳለፉት ውሳኔ ተግባራዊ ከሆነ፣ የደቡብ ክልል ሕልውና ያከትማል።

4፤ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ብዙኀን መገናኛ የሳተላይት ሥርጭቱን መጀመሩን የክልሉ ኮምንኬሽን ቢሮ አስታውቋል። ብዙኅን መገናኛው በሬዲዮ በአምስት ቋንቋዎች እንዲሁም በቴሌቪዥን በሰባት ቋንቋዎች ፕሮግራሞቹን እንደሚያሰራጭ ተገልጧል። የክልሉ መንግሥት በሳተላይት ለሚሰራጨው ጣቢያ ግንባታ 200 ሚሊዮን ብር ማውጣቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሐሰን ተናግረዋል። ቤንሻንጉል ጉሙዝ ሜዲያ በሚል ስያሜ ሥርጭት ለሚጀምረው ጣቢያ፣፣ የክልሉ ምክር ቤት የአዋጅ ማሻሻያ አድርጓል።

5፤ በአፍሪካ ቀንድ የአውሮፓ ኅብረት ልዩ መልዕክተኛ አን ዌበር ወደ መቀሌ ሊጓዙ መሆኑን በትዊተር ሰሌዳቸው ላይ ጽፈዋል። ልዩ መልዕክተኛ ዌበር ወደ መቀሌ የሚጓዙት፣ አፍሪካ ኅብረት የሰሜን ኢትዮጵያውን ጦርነት በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሚያደርገውን ጥረት ለማገዝ እንደሆነ አስታውቀዋል። ሆኖም ዌበር መቼ ወደ መቀሌ እንደሚጓዙ፣ ስንት ቀናት እንደሚቆዩና በቆይታቸው ወቅት ምን ዓይነት መርሃ ግብሮች እንደያዙ አላብራሩም።

6፤ በኢትዮጵያ በቴሌኮም አገልግሎት የተሠማራው ሳፋሪኮም ኩባንያን ከፍተኛ የማኔጅመንት ሃላፊነቶች ለመጀመሪያ ጊዜ ኬንያዊያን መቆጣጠራቸውን ደይሊ ኔሽን ዘግቧል። ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኬንያዊ ሲሆኑ፣ የቦርዱ ሰብሳቢዎች ግን ከጅምሩ ጀምሮ የውጭ ዜጎች ነበሩ። ሆኖም ቦርዱ በቅዳሜለት ጉባዔው፣ አንድን ኬንያዊ ሊቀመንበሩ አድርጎ መርጧል። ሳፋሪኮም ስረ መሠረቱ የኬንያ ኩባንያ ሲሆን፣ የብሪታኒያው ቮዳፎም እና የደቡብ አፍሪካው ቮዳኮን ግን ከፍተኛ ድርሻ አላቸው።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
93 viewsedited  18:13
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-31 11:44:47
ከአማራ ክልል ወደ አዲስ አበባ የሚጓዙ በርካታ ሰዎች ወደ አዲስአበባ እንዳይገቡ በፖሊስ መከልከላቸውን ገለጹ

ከአማራ ክልል በተለይም ከሰሜን ወሎና ደቡብ ወሎ በደብረ ብርሃን አቋርጠው ወደ አዲስ አበባ ለመግባት በአገር አቋራጭ ተሽከርካሪ የሚጓዙ ተሳፋሪዎች፣ ወደ አዲስ አበባ እንዳይገቡና ወደ መጡበት እንዲመለሱ መደረጋቸውን ተሳፋሪዎች ተናግረዋል፡፡

የሰሜን ሸዋ ዋና ከተማ ደብረ ብርሃንን አልፈው ከብዙ እንግልትና ፍተሻ በኋላ ወደ አዲስ አበባ ለመግባት የአዲስ አበባ የመጨረሻዋ መዳረሻ የሆነችው ለገዳዲ ከተማ ሲደርሱ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መታወቂያ የላችሁም ተብለው ወደ መጡበት እንዲመለሱ መደረጋቸውንና የሚደረገው ፍተሻም የተሳፋሪዎች ማንነት ላይ ያነጣጠረ መሆኑን በርካታ ተሳፋሪዎች አስረድተዋል፡፡

የተሳፋሪዎችን ቅሬታ አስመልክቶ የሚመለከታቸውን አካላት ብናናግርም የሕወሓት ሠርጎ ገቦችን ለመያዝ ነው ከሚል ምክንያት ውጭ ዝርዝርና ግልጽ ምላሽ ማግኘት አልቻለም።
ተሳፋሪዎች ግን ማንነትን መሠረት ያደረገ ክልከላ ነው በማለት ገልፀዋል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
135 viewsedited  08:44
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-30 21:43:42 ቅዳሜ ሐምሌ 23/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ የተመድ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች መርማሪ ኮሚሽን በሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ዙሪያ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ማስረጃ ያላቸው ቡድኖችና ተቋማት ሁሉ እስከ ሐምሌ 24 ድረስ በእጃቸው ያሉ ማስረጃዎችን እንዲያቀርቡለት ጥሪ አድርጓል። ማስረጃዎች በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸሙ ዓለማቀፍ ወንጀሎች፣ የጦርነት ወንጀሎችና በስደተኛ ዓለማቀፍ መብቶች ላይ የተፈጸሙ ወንጀሎችን የሚያስረዱ እንዲሆኑ እና የጥፋተኞችን ማንነት እንዲሁም የመፍትሄ ሃሳቦችን ያካተቱ እንዲሆኑ ኮሚሽኑ ጠይቋል። ማስረጃ አቅራቢዎች ማስረጃዎችን የሚያስገቡት፣ በተመድ ሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት ድረገጽ ላይ የተቀመጠውን ቅጽ በመሙላት እንደሆነ ተገልጧል። ቅፁን እዚህ ይመልከቱ- https://www.ohchr.org/en/hr-bodies/hrc/ichre-ethiopa/call-for-submissions

2፤ በደቡብ ክልል ሀድያ ዞን፣ ሀላባ ዞን፣ ከምባታ ጠምባሮ ዞን እና የም ልዩ ወረዳ በአዲስ ክልል ሥር ባንድ ላይ ለመዋቀር በየምክር ቤቶቻቸው ዛሬ ውሳኔ መወሰናቸውን የክልሉ ቴሌቪዥን ዘግቧል። የጉራጌ ዞን እና ስልጤ ዞን ምክር ቤቶችም በዚሁ መዋቅር ስር ለመካተት ሊወስኑ እንደሚችሉ ይጠበቃል። ባለፉት ሦስት ዓመታት የደቡብ ክልል አካል የነበሩት ሲዳማ ዞን እና የክልሉ ምዕራባዊ የአስተዳደር መዋቅሮች ከደቡብ ክልል በመውጣት፣ ሲዳማ ክልልን እና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልልን ማቋቋማቸው ይታወሳል።

3፤ በተመሳሳይ በደቡብ ክልል የወላይታ ዞንን ጨምሮ 11 ዞኖች እና ልዩ ወረዳዎች ከደቡብ ክልል ወጥተው አንድ አዲስ ክልል ለማቋቋም በየምክር ቤቶቻቸው ውሳኔ የክልሉ ቴሌቪዥን ዘግቧል። ከደቡብ ክልል ወጥተው ባንድ አዲስ ክልል ስለ ለመዋቀር የወሰኑት፣ ወላይታ ዞን፣ ጋሞ ዞን፣ ጎፋ ዞን፣ ጌዲዖ ዞን፣ ኮንሶ ዞን፣ ደቡብ ኦሞ ዞን፣ ቡርጅ ልዩ ወረዳ፣ ባስኬቶ ልዩ ወረዳ፣ አማሮ ልዩ ወረዳ፣ አሌ ልዩ ወረዳ እና ደራሼ ልዩ ወረዳ ናቸው። የደቡብ ክልል መንግሥት የክልልነት ጥያቄ ያነሱ የአስተዳደር መዋቅሮች ዛሬ ያሳለፉትን ውሳኔ አድንቋል።

4፤ ኢትዮ ቴሌኮም አፍሪካ ውስጥ በቴሌኮም ዘርፍ ከተሠማሩ ኩባንያዎች የባለቤትነት ድርሻ ለመግዛት የሚያስችሉትን ሥራዎች እያጠናቀቀ መሆኑን ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ገለፁ ። ኩባንያው ሙዓለ ንዋይ የሚያፈስባቸውን አገራት መርጦ በቴሌኮም ዘርፋቸው ላይ ጥናት ያደረገ ሲሆን፣ ሆኖም ፍሬሕይወት የአገራቱን ስም ከመጥቅስ ተቆጥበዋል። ኢትዮ ቴሌኮም ቴሌኮማቸውን ጠቅልሎ እንዲገዛላቸው የጠየቁ አገራት መኖራቸውንም ፍሬሕይወት ተናግረዋል። ፍሬሕይወት ለጊዜው ዕቅዳችን ድርሻ መግዛትና የሌሎችን ቴሌኮሞች ማኔጅመንት መረከብ ነው ብለዋል።

5፤ ዓለማቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ በአፋር ክልል በኩል ወደ ትግራይ አስፈላጊ መድኻኒቶችን በሚያጓጉዝ የኪራይ ካሚዮኑ ውስጥ "ሰርዶ" በተባለ ፍተሻ ኬላ ላይ ከተገኙት ያልተፈቀዱ ጥሬ ገንዘቦችና የተለያዩ ዕቃዎች ጋር ምንም ግንኙነት የለኝም ሲል ዛሬ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል። የካሚዮኑ ሹፌሩም ወዲያውኑ በጸጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ስር መዋሉን ድርጅቱ አክሎ ገልጧል። የሹፌሩን ያልተገባ ድርጊት ያወገዘው ቀይ መስቀል፣ ክስተቱ ሰብዓዊ ዕርዳታ በማጓጓዝ ተልዕኮዬ ላይ ተጽዕኖ እንዳይፈጥር ጥረት እያደረግሁ ነው ብሏል።

6፤ ግብጽ በሕዳሴ ግድብ ላይ የሦስትዮሽ አስገዳጅ ስምምነት ላይ ሳይደርስ ኢትዮጵያ በተናጥል የግድቡን ሦስተኛ ዙር ውሃ ሙሌት ለማከናወን የምታደርገውን እንቅስቃሴ እንደምትቃወም አስታውቃለች። ግብጽ ይህንኑ ተቃውሞዋን የገለጸችው፣ ለተመድ ጸጥታው ምክር ቤት በላከችው አዲስ ደብዳቤ ነው። የኢትዮጵያ መንግሥት ሦስተኛውን ዙር የግድቡን ውሃ ሙሌት በተያዘው ሐምሌ እና ነሐሴ ወር እንደሚያካሂድ መግለጹ ይታወሳል። ኢትዮጵያ ዘንድሮ ግድቡን እንደምትሞላ ከ5 ቀናት በፊት እንዳሳወቀቻት የገለጸችው ግብጽ፣ የግድቡ የተናጥል ሙሌት ሊፈጥርብኝ የሚችለውን ተጽዕኖ ጨምሮ ብሄራዊ ደኅንነቴን ለማስጠበቅ ሁሉንም ዓይነት ርምጃዎች እወስዳለሁ ስትል በደብዳቤዋ አስጠንቅቃለች።

7፤ የዓለም ጤና ድርጅት የዝንጀሮ ፈንጣጣ በሽታን ለመቆጣጠር ከፍተኛ ዓለማቀፍ ጥረት እንደሚያስፈልግ አሳስቧል። የዝንጀሮ ፈንጣጣ ቫይረስ እስካሁን በ78 አገራት ከ16 ሺህ በላይ በሚሆኑ ሰዎች ላይ ተገኝቷል። በሽታው ባለፉት ጥቂት ወራት በዓለም ላይ በስፋት መሰራጨት ከጀመረ ወዲህ፣ እስከ ትናንት ድረስ በበሽታው የተያዙ ሰዎች የሞቱት አፍሪካ ውስጥ ብቻ ነበር። ሆኖም ትናንት ከአፍሪካ ውጭ ለመጀመሪያ ጊዜ ስፔን እና ብራዚል በበሽታው የተያዙ ሰዎች እንደሞቱባቸው ሪፖርት አድርገዋል። አፍሪካ እስካሁን የበሽታው መከላከያ ክትባቶች በእጇ የሏትም።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
125 viewsedited  18:43
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-29 20:02:36 ዓርብ ሐምሌ 22/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ የሱማሌ ክልል ልዩ ኃይሎች በሱማሊያዋ ባኮል ግዛት ውስጥ "አቶ" በተባለ ወረዳ ዛሬ ከአልሸባብ ታጣቂዎች ጋር በድጋሚ እንደተዋጉ የሱማሊያ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። የአልሸባብ ታጣቂዎች በክልሉ ልዩ ኃይል ላይ ዛሬ ጧት ሞርታሮችን በመተኮስ ውጊያውን እንደጀመሩ ዘገባዎች አመልክተዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ማምሻውን ለመንግሥት ዜና አውታሮች በሰጠው መረጃ፣ ቡድኑ ትናንት ሌሊት በከፈተው አዲስ ውጊያ በድጋሚ ተመቶ መመለሱን እና ከ150 በላይ ታጣቂዎቹ መገደላቸውን ተናግሯል።

2፤ ፍርድ ቤት በሙስና ወንጀል ተጠርጣሪው የቀድሞ የብሄራዊ አደጋ ስጋት ሥር አመራር ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ 14 ተጨማሪ ቀናት መፍቀዱ ተገለፀ። ችሎቱ በተመሳሳይ ወንጀል ተጠርጥሮ በታሰረው ልጃቸው እያሱ ምትኩ ላይ ደሞ 10 ቀን ፈቅዷል። ምትኩ እና ልጃቸው ችሎቱን በአካል ተከታትለዋል። ኤልሻዳይ ከተባለ ግብረ ሰናይ ድርጅት ጋር በመመሳጠር ከኮሚሽኑ በተመዘበረ ገንዘብ ራሳቸውን፣ ቤተሰባቸውን እና ድርጅቱን ጠቅመዋል ተብለው ነው። ፖሊስ ተጠርጣሪው ሕጋዊ ያልሆነ ገንዘብን ሕጋዊ አስመስለው በማቅረብ ወንጀል ጭምር ጠርጥሯቸዋል።

3፤ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአዲስ አበባ ከተማ የጋራ መኖሪያ ቤቶች እጣ አወጣጥ ማጭበርበር ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር የዋሉ ግለሰቦች ላይ ዛሬ የ14 ቀናት ተጨማሪ ምርመራ ጊዜ መፍቀዱን የአገር ውስጥ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ችሎቱ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ የፈቀድኩት ወንጀሉ ውስብስብ በመሆኑ ነው ብሏል። ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ የተፈቀደባቸው የከተማዋ የቴክኒክ ሥልጠናና የቴክኖሎጂ ልማት እንዲሁም የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮዎች ሠራተኞች እና ሃላፊዎች ናቸው።

4፤ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ደመቀ መኮንን በአፍሪካ ቀንድ የአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ የሆኑትን ማይክ ሐመርን ዛሬ በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው ማነጋገራቸውን ሚንስቴሩ አስታውቋል። በውይይቱ ላይ የአሜሪካ ጉዳይ አስፈጻሚ ትሬሲ ጃኮብሰን ጭምር ተገኝተዋል። የጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ የብሄራዊ ደኅንነት አማካሪ ሬድዋን ሁሴን፣ መንግሥት የምዕራባዊያን አምባሳደሮችና ልዩ መልዕክተኞች ወደ መቀሌ እንዲሄዱ መፍቀዱን ትናንት በትዊተር ገጻቸው ገልጸዋል።

5፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የመጀመሪያውን ኤ350- 1000 ሞዴል ኤርባስ የመንገደኞችን አውሮፕላን ለመግዛት ማዘዙን አስታውቋል። አየር መንገዱ ግዙፉን የአውሮፓዊያኑን ኤ350- 1000 ኤርባስ የመንገደኞች አውሮፕላንን በመግዛት በአፍሪካ የመጀመሪያው ይሆናል። አየር መንገዱ አሁን ሊገዛቸው ያቀዳቸው አውሮፕላኖች፣ አራት ኤ350-1000 ሞዴል እና ሁለት ኤ350-900 ሞዴል ኤርባስ አውሮፕላኖች ናቸው።

6፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 52 ብር ከ1427 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 53 ብር ከ1856 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 60 ብር ከ4377 ሳንቲም፣ መሸጫው 61 ብር ከ6465 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ52 ብር ከ9666 ሳንቲም ሲገዛ እና በ54 ብር ከ0259 ሳንቲም ሲሸጥ ውሏል። የቻይና ዩዋን ደሞ 6 ብር ከ9944 ሳንቲም ተገዝቶ፣ በ7 ብር ከ1343 ሳንቲም ተሽጧል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
131 viewsedited  17:02
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-28 22:57:30 ሐሙስ ሐምሌ 21/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ እና በማናቸውም ጊዜ እና ቦታ ከሕወሃት ጋር ድርድር ለመጀመር ዝግጁ መሆኑን የጠቅላይ ሚንስትሩ የብሄራዊ ደኅንነት አማካሪ ሬድዋን ሁሴን አስታውቀዋል። መንግሥት ይህንኑ አቋሙን የገለጸው፣ ራሳቸው ሬድዋን እና ፍትህ ሚንስትር ጌዲዮን ዛሬ ከተመድ እና ከአውሮፓ ኅብረት ቋሚ መልዕክተኞች እንዲሁም ከአሜሪካ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጣሊያንና ብሪታኒያ አምባሳደሮች ጋር በተወያዩበት ወቅት ነው።

2፤ የኢትዮጵያና ሩሲያ የጋራ ኮሚሽን በቀጣዩ ዓመት እንዲሰበሰብ እና አዳዲስ ስምምነቶች ላይ እንዲደርስ ከሩሲያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌ ላቭሮቭ ጋር ስምምነት ላይ እንደተደረሰ የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ቃል አቀባይ መለስ ዓለም ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል። ላቭሮቭ ሩሲያ ኢትዮጵያ ከቀድሞዋ ሶቪየት ኅብረት ያለባትን እዳ ወደ ልማት መርሃ ግብር ለመለወጥ መወሰኗን ማስታወቃቸውንም መለስ ገልጸዋል። ላቭሮቭ ከፕሬዝዳንት ሳሕለወርቅ ጋር ባደረጉት ውይይት ደሞ፣ አፍሪካ በተመድ ጸጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ ለማግኘት የምታደርገውን ጥረት ሩሲያ ትደግፋለች ብለዋል። 

3፤ ኢትዮ ቴሌኮም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 61.3 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘቱን አስታውቋል። የኩባንያው ገቢ የእቅዱ 87.6 በመቶ እንደሆነ የኩባንያው ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተናግረዋል። ኩባንያው በ2013 ዓ፣ም ያገኘው ገቢ 56.5 ቢሊዮን ብር ነበር። ኩባንያው ይህን ስኬት ያገኘው፣ በኃይል አቅርቦት እጥረት፣ በቴሌኮም አገልግሎት መቋረጥ፣ በነዳጅ እጥረት፣ በዋጋ ግሽበት፣ በውጭ ምንዛሬ አቅርቦት እጥረት እና በጸጥታ ችግሮች ውስጥ አልፎ መሆኑን ፍሬሕይወት ተናግረዋል።

4፤ ንግድ ባንክ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከታክስ በፊት 27.5 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን ዛሬ አስታውቋል። የባንኩ ጥቅል ትርፍ ከእቅዱ የ17.5 በመቶ ብልጫ አለው። የዘንድሮው የባንኩ ትርፍ ባለፈው ዓመት ካገኘው ጥቅል ትርፍ የ7.5 ቢሊዮን ብር ብልጫ ማለትም የ43 በመቶ እድገት ማሳየቱንም ባንኩ ገልጧል። ባንኩ ተቀማጭ ገንዘቡንም 890 ቢሊዮን ብር ማድረሱንና ጠቅላላ ሃብቱን ወደ 1.2 ትሪሊዮን ብር ከፍ አድርጌዋለሁ ብሏል።

5፤ የአማራ ክልል ምክር ቤት ለቀጣዩ ዓመት 95 ቢሊዮን 320 ሚሊዮን ብር በጀት ማጽደቁን የክልሉ ቴሌቪዥን ዘግቧል። ከዚሁ የክልሉ ዓመታዊ ጠቅላላ በጀት ውስጥ፣ 44 ቢሊዮኑ ከፌደራል መንግሥት ድጎማ እንደሚሸፈን ተገልጧል። ክልሉ ለቀጣዩ ዓመት ያጸደቀው በጀት፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት መድቦት ከነበረው በጀት የ15 ቢሊዮን ብር ብልጫ አለው። ከበጀቱ ውስጥ ለድንገተኛ አደጋዎችና ክስተቶች 3 ቢሊዮን 499 ሚሊዮን ብሩ ለመጠባበቂያነት እንዲያዝ ምክር ቤቱ ወስኗል።

6፤ በአሜሪካ በተካሄደው 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና አስደናቂ ውጤቶችን በማስመዝገብ ኢትዮጵያ ከዓለም ሁለተኛ ደረጃ እንድታገኝ ያስቻሉት ጀግኖቹ የኢትዮጵያ አትሌቶች ዛሬ በአዲስ አበባ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል። በብሄራዊ ቤተ መንግሥት ፕሬዝዳንት ሳሕለ ወርቅ ዘውዴ በተገኙበት በተካሄደ ልዩ መንግሥታዊ ስነ ሥርዓት፣ መንግሥት ሜዳሊያ ላስገኙ አትሌቶች ለእያንዳንዳቸው ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ሰጥቷል።

7፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 52 ብር ከ1338 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 53 ብር ከ1765 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 60 ብር ከ0540 ሳንቲም፣ መሸጫው 61 ብር ከ2551 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ52 ብር ከ8532 ሳንቲም ሲገዛ እና በ53 ብር ከ9103 ሳንቲም ሲሸጥ ውሏል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
130 viewsedited  19:57
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-26 21:41:55 ማክሰኞ ሐምሌ 19/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ ግብርና ሚንስቴር ባለፈው ሰኔ 3 ምንነቱ ያልታወቀ የዶሮ በሽታ ገብቷል በማለት በዶሮና እንቁላል ላይ የጣለውን ክልከላ ሰኔ 27 ላይ ለክልሎች በከፊል ማንሳቱን ሰምተናል። በሽታው ባልታየባቸው አካባቢዎች ዶሮ አርቢዎች የዶሮ ስጋና እንቁላል እንዲሸጡ የተፈቀደላቸው ሲሆን፣ በሽታው በታየባቸው አካባቢዎች ግን የዶሮ ስጋና እንቁላል ለገበያ የሚያቀርቡ ድርጅቶች በቅድሚያ በሚንስቴሩ ላቦራቶሪ ማስመርመር አለባቸው። ሚንስቴሩ እስካሁን የበሽታውን ምንነት አላወቅንም በማለት ለዋዜማ ተናግሯል። አንድ የሚንስቴሩ ባለሙያ ግን በሽታው በጣም ተላላፊ መሆኑን አረጋግጠዋል።

2፤ የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዛሬ ባዋለው ችሎት በባሕርዳር ከተማ ቦምቦችን አፈንድተዋል ተብለው በእነ ቴዎድሮስ ጌታቸው መዝገብ በሽብር የተጠረጠሩ ተጠርጣሪዎችን የጊዜ ቀጠሮ ጉዳይ መዝጋቱ ተገለፀ። መርማሪ ፖሊስ ተጨማሪ ማስረጃዎችን ለመሰብሰብ ተጨማሪ 14 ቀናት እንዲሰጠው ጠይቆ ነበር። ችሎቱ ግን የእስካሁኑ 24 ቀን በቂ መሆኑንና ማስረጃዎቹ ከመንግሥት ተቋማት የሚገኙ መሆኑን በመጥቀስ፣ ጥያቄውን ውድቅ አድርጓል። ፖሊስ ተጠርጣሪዎቹን ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በመናድ ወንጀል ጠርጥሬያቸዋለሁ ብሏል።

3፤ አምና በትግራዩ ጦርነት ሦስት ሠራተኞቹ ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ መቀሌ አቅራቢያ የተገደሉበት የስፔኑ ድንበር የለሽ ሐኪሞች ቡድን ሃላፊ ፓውላ ጊል ወደ ትግራይ ክልል ለመጓዝ ከመንግሥት ፍቃድ እንዳላገኙ ድርጅቱ አስታውቋል። ሃላፊዋ ወደ መቀሌ ሂደው ድርጅታቸው በግድያው ላይ እስካሁን የደረሰበትን የውስጥ ግምገማ ለሁለቱ ሟቾች ቤተሰቦች ለማጋራት አቅደው ነበር። ሃላፊዋ በጉዳዩ ዙሪያ ከመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር ለመነጋገር ላቀረቡት ጥያቄም ምላሽ እንዳላገኙ ገልጸዋል። ለነፍስ አድን በድርጅቱ ተሽከርካሪ ሲጓዙ የተገደሉት፣ ዮሃንስ ሐለፎም፣ ቴዎድሮስ ገ/ማርያም እና ስፔናዊቷ ማሪያ ኸርናንዴዝ ነበሩ።

4፤ የሩሲያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌ ላቭሮቭ የኡጋንዳ ጉብኝታቸውን አጠናቀው ማምሻውን አዲስ አበባ ገብተዋል። ላቭሮቭ በአዲስ አበባ ቆይታቸው፣ በሁለትዮሽና ዓለማቀፋዊ ጉዳዮች ዙሪያ ከመንግሥት ባለሥልጣናትና ኮአፍሪካ ኅብረት ሃላፊዎች ጋር ይወያያሉ። ላቭሮቭ በአፍሪካ ኅብረት ጽሕፈት ቤት የበርካታ አፍሪካ አገራት ዲፕሎማቶችን በዝግ ለማነጋገር መጋበዛቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። ላቭሮቭ ይህንኑ ውይይት የሚያደርጉት፣ በአፍሪካ ቀንድ የአሜሪካ ልዩ ልዑክ ማይክ ሐመር ወደ ኢትዮጵያ በሚጓዙበት ዋዜማ ላይ ነው።

5፤ የአፍሪካ በሽታዎች መከላከያ ማዕከል የዓለም ጤና ድርጅት የዝንጀሮ ፈንጣጣን "አጣዳፊ ዓለማቀፍ የጤና ስጋት" በማለት መፈረጁን እንደሚያደንቅ አስታውቋል። በዓለም ዙሪያ እስካሁን የዝንጀሮ ፈንጣጣ ቫይረስ ከተገኘባቸው 75 አገራት መካከል፣ 11ዱ የአፍሪካ አገራት ናቸው። በዓለም ላይ ከ16 ሺህ 500 በላይ ሰዎች ቫይረሱ ተገኝቶባቸዋል። የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድኻኖም ባለፈው ሳምንት በሽታውን "የዓለም አጣዳፊ የጤና ስጋት" በማለት ያወጁት፣ የድርጅቱ ከፍተኛ ባለሙያዎች በጉዳዩ ሙሉ ስምምነት ላይ ሳይደርሱ ነበር።

6፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 52 ብር ከ1213 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 53 ብር ከ1637 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 59 ብር ከ8853 ሳንቲም፣ መሸጫው 61 ብር ከ0830 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ53 ብር ከ2680 ሳንቲም ሲገዛ እና በ54 ብር ከ3334 ሳንቲም ሲሸጥ ውሏል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
151 viewsedited  18:41
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-26 18:21:23
ከጠቅላይ ቤተክህነት የተሰጠ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ለሕክምና ወደ ሰሜን አሜሪካ እንደሚሄዱ መገለፁን ተከትሎ ትናንት ምሽት ቅዱስነታቸው የአሜሪካ ጉዟቸውን መጀመራቸው ተገልጿል።

ቅዱስነታቸው ለሕክምና የሚሄዱ ቢሆንም በአዲስ አበባ ኤርፖርት በተገኙበት ወቅት ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት እና ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት ተፈቅደው በአድራሻ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት የተጻፈ ሕጋዊ ደብዳቤ እንደሚያመለክተው

ቅዱስ ፓትርያርኩ ለአገልግሎት ይዘዋቸው የሚጓዙት ንዋያተ ቅድሳት

— ሁለት ጽላቶችን ፣
— 3 የወርቅ የእጅ መስቀሎችን (የግል ንብረታቸውንና ስማቸው የተፃፈባቸውን) ፣
— 5 አዲስ እትም የግእዝ መጽሐፍ ቅዱስ እና
— አንድ ሊትር ቅብዓ ሜሮን

መሆናቸውን ለቦሌ ኤርፖርት ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የተጻፈ ደብዳቤ ያሳያል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
127 viewsedited  15:21
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-26 08:02:57 ማክሰኞ ሐምሌ 19/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ የሱማሌ ክልል ልዩ ኃይል በድጋሚ የኢትዮ-ሱማሊያን ድንበር አቋርጠው ከገቡ የአልሸባብ ተዋጊዎች ጋር ትናንት መፋለማቸውን የክልሉ ኮምንኬሽን ቢሮ አስታውቋል። ታጣቂዎቹ ከሱማሊያዋ ሂራን ግዛት በመነሳት ወደ ሸበሌ ዞን ፌርፌር ወረዳ እንደገቡ የጠቀሰው ቢሮው፣ ልዩ ስሟ "ኤል ቀዱን" በተባለች ቦታ ላይ ተመተዋል ብሏል። የክልሉ መንግሥት ከአልሸባብ ጋር በድጋሚ ውጊያ እንደተደረገ የገለጠው፣ መከላከያ ሠራዊት ወደ አካባቢው መዝመቱን ከገለጸ ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ነው።

2፤ የፌደራል ገቢዎች ሚንስቴር በትግራይ ክልል የተመዘገቡና ባሁኑ ወቅት ከክልሉ ውጭ ከሚገኙ የክልልና የፌደራል ግብር ከፋዮች ግብር ሊሰበስብ መሆኑን ገለፀ። ሚንስቴሩ ለክልሉ ገቢ መሆን ያለበትን ግብር በአደራ ባንክ ለማስቀመጥ አቅዷል። በጦርነቱን ሳቢያ ግብር ከፋዮች ብድር ለማግኘትና በጨረታ ለመወዳደር ተቸግረው ቆይተዋል። ግብር ከፋዮቹ ትግራይ ውስጥ ያለባቸው ዕዳ ስለማይታወቅ፣ ሚንስቴሩ ከፋዮቹ የሚያሳውቁትን ግብር ብቻ ይሰበስባል።

3፤ ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ደመቀ መኮንን ተመድ የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን እንዲመረምር ላቋቋመው ገለልተኛ መርማሪ ኮሚሽን የሾማቸውን ኮሚሽነሮች ትናንት በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው እንዳነጋገሩ ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር አስታውቋል። ለስድስት ቀናት ጉብኝት ትናንት ኢትዮጵያ የገቡት መርማሪ ኮሚሽነሮች፣ የኮሚሽኑ ሰብሳቢ ኬንያዊቷ ካሪ ቤቲ ሙሩንጊ፣ አሜሪካዊው ስቲቨን ራትነር እና ሽሪላንካዊቷ ኩማራስዋሚ ናቸው።

4፤ የሱማሊያ ፓርላማ ጠቅላይ ሚንስትር ሐምዛ ባሬ አዲሱን ካቢኔያቸውን እንዲያቋቁሙ 10 ተጨማሪ ቀናት እንደሰጣቸው የአገሪቱ ዜና ምንጮች ዘግበዋል። ጠቅላይ ሚንስትሩ ተጨማሪ ቀናት የተሰጣቸው፣ ቃለ መሃላ በፈጸሙ በ30 ቀናት ውስጥ ካቢኔ ማቋቋም ባለመቻላቸው ነው። በሱማሊያ ታሪክ አንድ ጠቅላይ ሚንስትር ባንድ ወር ውስጥ ካቢኔ ባለማቋቋም የአሁኑ የመጀመሪያ ጊዜ ነው ተብሏል። ባሁኗ ሱማሊያ የተለያዩ ጎሳዎች የካቢኔ ሥልጣን ለማግኘት ከፍተኛ ጥረቶችን እንደሚያደርጉ ይታወቃል።

5፤ ዩክሬን በተያዘው ሳምንት ወደቧ ላይ የተሰማቸውን የጥራጥሬ ምርቷን ለውጭ ገበያ እንደምታቀርብ መግለጧን ዓለማቀፍ የዜና ወኪሎች ዘግበዋል። ከኦዴሳ እና ሌሎች ወደቦች ከ20 ሚሊዮን ቶን በላይ የምግብ እህል እንደተከማቸ ይገመታል። የዓለም ምግብ ድርጅት ግን፣ የዩክሬን እህል ምርት ለገበያ እንዲቀርብ ሩሲያና ዩክሬን በቅርቡ የደረሱበት ስምምነት ብቻውን በዓለም ላይ የተከሰተውን የምግብ ዋጋ ውድነት አይቀርፍም ብሏል።

6፤ የሩሲያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌ ላቭሮቭ ዛሬ በኡጋንዳ በሚያደርጉት ጉብኝት ከፕሬዝዳንት ዮዌሪ ሙሴቪኒ ጋር እንደሚወያዩ ዓለማቀፍ የዜና ወኪሎች ዘግበዋል። የኡጋንዳ መንግሥታዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ የሩሲያውን "አርቲ" ቴሌቪዥን ዝግጅቶች በቀን ሁለት ጊዜ ለማሰራጨት ቀደም ሲል ተስማምቷል። ላቭሮቭ በግብጽ፣ ኮንጎ፣ ኡጋንዳና ኢትዮጵያ ጉብኝት የሚያደርጉት፣ በዩክሬኑ ጦርነት ሳቢያ የምዕራባዊያን ማዕቀብ ሰለባ ለሆነችው አገራቸው የአፍሪካ አገራትን ድጋፍ ለማግኘት እንደሆነ ተገምቷል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
124 viewsedited  05:02
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-25 20:14:31 ሰኞ ሐምሌ 18/2014 ዓ.ም ዐበይት ዜናዎች

1፤ የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት በሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት የተፈጸሙ ዓለማቀፍ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን እንዲመረምር ባለፈው ታኅሳስ ያቋቋመው መርማሪ ኮሚሲዮን ኮሚሽነሮች ከዛሬ እስከ ቅዳሜ በኢትዮጵያ ጉብኝት ላይ መሆናቸውን ምክር ቤቱ አስታውቋል። ሦስቱ ኮሚሽነሮች በመጭው ቅዳሜ የጉብኝታቸውን ውጤት አስመልክተው ከተለያዩ አካላት ጋር ይወያያሉ። ሦስት ኮሚሽነሮች ያሉት ኮሚሲዮን ምርመራውን በቅርበት እንዲያከናውን ካምፓላ ላይ ጽሕፈት ቤት ተቋቁሞለታል።

2፤ መከላከያ ሠራዊት የሱማሊያውን አልሸባብ ለመፋለም ወደ ኢትዮ-ሱማሊያ ድንበር መሠማራቱን የሱማሌ ክልል ኮምንኬሽን ቢሮ አስታውቋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፋ ኡመር ባካባቢው ከክልሉ ልዩ ኃይል ጋር የተቀላቀሉትን የሠራዊቱ አባላት ጎብኝተዋል። ባለፉት ቀናት የክልሉ ልዩ ኃይል በአፍዴር ዞን በኩል ወደ ሱማሌ ክልል በገቡት የአልሸባብ ተዋጊዎች ላይ ልዩ ስሙ ሁልሁል በተባለ ቦታ ላይ፣ በርካታ የቡድኑን ታጣቂዎች መግደላቸውና ጦር መሳሪያዎችን መማረካቸውን የክልሉ መንግሥት መግለጡ ይታወሳል።

3፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት በመጭው ዓመት 30 ሚሊዮን ብር በጀት ያስፈልገኛል ሲል ዛሬ ባካሄደው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ገለጠ። ምክር ቤቱ በጀቱን የፈለገው፣ የአባል ፖለቲካ ፓርቲዎችን አቅም ለመገንባት እና በአገራዊ ምክክሩና በአካባቢያዊ ምርጫዎች ዓይነተኛ ተሳትፎ ለማድረግ እንዲችል መሆኑን ተናግሯል። ምክር ቤቱ አብዛኛውን ገንዘብ ለማግኘት ያቀደው ከዓለማቀፍ ለጋሾች ነው።

4፤ ሳፋሪኮም ኩባንያ በኢትዮጵያ ቴሌኮም ዘርፍ ለመሠማራት ከአሜሪካው ፋይናንስ ኮርፖሬሽን ላገኘው አገልግሎት 4 ሚሊዮን ዶላር እንደከፈለ ቢዝነስ ደይሊ ዘግቧል። ኮርፖሬሽኑ ምን አገልግሎት እንደሰጠ ኩባንያው ባይገልጽም፣ በኢትዮጵያው የቴሌኮም ጨረታ የምክር አገልግሎት መስጠት ወይም ዓለማቀፍ ብድሮችን ማስገኘት ሊሆን እንደሚችል ዘገባው ጠቁሟል። የናይሮቢው ስታንዳርድ ቻርተርድ ባንክ ብቻ ለኩባንያው 400 ሚሊዮን ዶላር አበድሯል። ሳፋሪኮም በነሐሴ በድሬዳዋ ሥራውን ይጀምራል።

5፤ የሱማሊያው ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐመድ ዛሬ ከግብጹ አቻቸው አብዱል ፈታህ አል ሲሲ ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውን ቤተ መንግሥታቸው አስታውቋል። ሁለቱ መሪዎች በጋራ በሰጡት መግለጫ፣ በሁለትዮሽ እና የቀይ ባሕር አካባቢ ደኅንነትን ጨምሮ በቀጠናዊ ጸጥታና ልማት ዙሪያ መወያየታቸውን ተናግረዋል። ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ሥልጣን ከያዙ ወዲህ፣ ከግብጽ ቀደም ብሎ በኤርትራ፣ ጅቡቲና ኬንያ ኦፊሴላዊ ጉብኝት አድርገዋል።

6፤ የሩሲያው ውጭ ጉዳይ ሚንስትር ሰርጌ ላቭሮቭ የግብጽ ጉብኝታቸውን አጠናቀው ዛሬ ኮንጎ ብራዛቪል እንደገቡ ዓለማቀፍ የዜና ምንጮች ዘግበዋል። አገራቸው ከዩክሬን ጋር በገባችበት ጦርነት ሳቢያ ምዕራባዊያን ማዕቀብ ከጣሉባት ወዲህ፣ ላቭሮቭ በአፍሪካ ተከታታይ ጉብኝቶችን ሲያደርጉ የመጀመሪያቸው ነው። ላቭሮቭ ከኮንጎ ብራዛቪል ቀጥሎ ኡጋንዳንና ኢትዮጵያን የሚጎበኙ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ ቆይታቸው ከአፍሪካ ኅብረት ባለሥልጣናት ጋር ጭምር እንደሚነጋገሩ ይጠበቃል። ከወር በፊት የአፍሪካ ኅብረት ሊቀመንበር ፕሬዝዳንት ማኪ ሳል ሩሲያን መጎብኘታቸው ይታወሳል።

7፤ ንግድ ባንክ ዛሬ የአንድ ዶላር መግዣ ዋጋ 52 ብር ከ1166 ሳንቲም እና መሸጫ ዋጋው 53 ብር ከ1589 ሳንቲም ሆኖ እንደዋለ ገልጧል። የአንድ የእንግሊዝ ፓውንድ መግዣ ዋጋ ደሞ 59 ብር ከ4718 ሳንቲም፣ መሸጫው 60 ብር ከ6612 ሳንቲም ሆኗል። በተመሳሳይ አንድ ዩሮ በ52 ብር ከ9661 ሳንቲም ሲገዛ እና በ54 ብር ከ0254 ሳንቲም ሲሸጥ ውሏል።

@Ethiopianewsagency (ኢዜአ)
123 viewsedited  17:14
ክፈት / አስተያየት ይስጡ