2022-09-23 16:48:06
___ሕገጋተ ወንጌል ክፍል ፭__
የክርስትና ሕግ የወንጌል ሕግ የትሩፋት ሕግ ይባላል። አሁን አሁን በሕግ ሳይሆን በስሜት የሚመራው እየበዛብን ነው። ከሕጉ ይልቅ ስሜቱን የሚከተለው በዛ። የክርስትና ሕግ ትምህርት ጠላትን እስከ መውደድ ነው። ይህ ግን መተንተን አለበት። ጠላትን መውደድ ማለት ሲያጠፋ ዝም ማለት አይደለም። ሲያጠፋ ለሕግ ማቅረብ ነው። ጥፋተኛን ወደ ሕግ ማቅረብ ራሱ የመውደድ ምልክት ነውና። በጥፋተኛ ላይ መፍረድ የመውደድ ምልክት ነው። እግዚአብሔርኮ ስለሚወደን ነው ስናጠፋ የሚቀጣን። እግዚአብሔር ይጌሥጽ ዘአፍቀሮ እግዚአብሔር የወደደውን ይገሥጻል የሚባለውም ለዚያ ነው። ጠላትህን ውደድ ማለት ፍትሕን አጥፋ ማለት አይደለም። ፍትሕን አጠንክር ማለት ነው። ጥፋተኛ የሚቀጣው ጥፋቱን እንዲተውና እንዲታረም ነው። አንድ ሰው አጥፍቶ ጥፋቱን ማለባበስ እና ለሕግ እንዳይቀርብ ማድረግ ግን የጥላቻ ምልክት ነው። እንዲታረም እድል አልሰጠነውምና። ጠላትን የመውደድ ትርጓሜ ይህ ነው። ሲያጠፋ ተው ማለት መልካም ሲሰራ ማበረታታት ነው። እዚህ ላይ ውደዱ የተባለ ሰው ሆኖ እኛን የሚጠላንን ነው እንጂ ጥንተ ጠላት ዲያብሎስን ውደዱ ማለት አይደለም።
።
ማቴ. ፭፣፵፬_፵፰ "እኔ ግን እላችኋለሁ፥ በሰማያት ላለ አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፥ የሚረግሙአችሁንም መርቁ፥ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፥ ስለሚያሳድዱአችሁም ጸልዩ፤ እርሱ በክፎዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣልና፥ በጻድቃንና በኃጢአተኞችም ላይ ዝናቡን ያዘንባልና። የሚወዱአችሁን ብትወዱ ምን ዋጋ አላችሁ? ቀራጮችስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? ወንድሞቻችሁንም ብቻ እጅ ብትነሡ ምን ብልጫ ታደርጋላችሁ? አሕዛብስ ያንኑ ያደርጉ የለምን? እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተ ፍጹማን ሁኑ"።
።
ሲጠቃለል ስድስቱ ሕገጋተ ወንጌል የሚባሉት:-
፩) አትሳደብ/አትቆጣ
፪) ወደሴት አይቶ የተመኘ አመነዘረ (አታመንዝር)
፫) ያለዝሙት ምክንያት ሚስትህን አትፍታ
፬) ፈጽመህ አትማል
፭) ክፉን በክፉ አትቃወም
፮) ጠላትህን ውደድ
ናቸው። አነሳስቶ ላስጀመረን አስጀምሮ ላስፈጸመን ልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ይገባል።
።
1.0K views13:48