2023-02-25 20:04:08
ታሪካዊው ውህደት እውን ሆኗል።
አባት እና ልጅ ለእናት ዓለም ጎንደር ሠላምና ዕድገት ዘብ ቆመዋል።
በዛሬው ዕለት የካቲት 18/2015 በመናገሻ ጎንደር ከተማ፥ ጎንደር የሰላምና የዕድገት ማኀበር (ጎ-ሰ'ማ) ከአንጋፋው ጎንደር ልማት ማኀበር (ጎልማ) ጋር ውህደት ፈፅመዋል።
በ1955 ዓ.ም በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የበላይ ጠባቂነት የበጌምድር-ስሜን የጎንደር መረዳጃ ማኅበር በሚል ስያሜ ተመስርቶ በማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ሲንቀሳቀስ ቆይቶ፣ በአብዮቱ ዘመን ጠፍቶ እንደገና የጎንደር መልሶ ማቋቋምና ልማት ማኀበር (ጎልማ) በመባል በጥር ወር 1984 ዓ.ም ተቋቁሞ ላለፉት 31 ዓመታት ሰፊ የልማት ሥራዎችን በተለይም በትምህርታቸው ጠንካራ ሆነው ትምህርታቸውን ለመቀጠል ለሚቸገሩ ተማሪዎች የስኮላርሸፕ ዕድል በመስጠት ሰፊ የተማረ የሰው ኃይል በማፍራት የሚታወቀው፣ በጤናው፣ በመሠረተ ልማትና በተፈጥሮ ሃብት ልማት ዙሪያ ጉልህ ድጋፍ እንዲሁም በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ አደጋ ለተጎዱትም ድጋፍ በማድረግ ለሦስት አስርት ዓመታት ትልቅ አበርክቶ የተወጣው ጎልማ፣ በሌላ አንፀባራቂ ታሪኩ ወልቃይት-ጠገዴና ጠለምት በጉልበት ወደ ትግራይ መካለላቸውን ከመቃወም አልፎ፤ የማኀበሩ መተዳደሪያ ደንብ እና ደንቡ ላይ የሚታየው የጎንደር በጌ-ምድር ካርታ ተከዜ ምላሽ ያለውን ታሪካዊ ወሰን ያካተተ ሆኖ እንዲዘጋጅ ማድረጉና እስከዛሬው የውህደት ቀኑ ድረስ ያስቀጠለው ጎልማ እና
ጎ-ሰ'ማ በዛሬው ዕለት ውህደታቸውን በተሳካ ሁኔታ ፈፅመዋል።
አካባቢው ያለውን እምቅ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ሃብት በመለዬትና የማኅበረሰቡን ኑሮ ለማሻሻል ተግዳሮት እየሆኑ ያሉትን የሰላምና የልማት ችግሮችን ነቅሶ በማውጣት “ሰላሙን በማስፈን ልማቱን ማፋጠን ይቻላል” በሚል እሳቤና አዲስ ኃይል፣ አገር በቀል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት ሆኖ በኅዳር 10 ቀን 2014 ዓ.ም የተቋቋመው ጎ-ሰ'ማ፣ ይዞት ከተነሳው ዓላማ መካከል አንዱ በቅንጅትና በትብብር መስራት፣ በተለይም አካባቢውን ማዕከል ባደረገ መንገድ የተቋቋሙ ማኅበራትን በማሰባሰብ በጋራ እንዲንቀሳቀሱ ማስቻልን አልሞ የተነሳው፣ በአንድ ዓመት በመላ ጎንደር፣ ባህርዳርና አዲስ አበባ ከተሞች ከ 34 በላይ የውይይት መድረኮችን በመክፈት ህዝብን በሰላምና በልማት ዙሪያ ሰፊ አስተምህሮ ሰጥቷል፡፡ ትምህርት ከወደቀበት እንዲያገግም በሁሉም የጎንደር ዞኖችና ወረዳዎች ሥራዎችን ጀምሯል፡፡ የወልቃይት ጠገዴና ጠለምትን ጥያቄ በዘላቂነት ለመፍታት የቴክኒካል ሥራዎችን ሲሰራ ቆይቷል፡፡ ጎንደር እንደገና በሚል መነሻ ምልሰተ-ጎንደርን እውን ለማድረግ ዘመኑን የዋጀ የሀሳብ ምንጭ ለመሆን ስትራቴጂያዊ የአብሮነት ፍኖተ-ካርታ ቀይሶ በመስራት ላይ ይገኛል፡፡
እነዚህ ሁለት ተቋማት በዛሬው ዕለት በሙሉ ድምፅ ውህደት የፈፀሙ ሲሆን፤ አዲሱ የሲቪክ ማኀበር አንድ ትልቅ የሕዝብ አቅም እንደሚሆን ይጠበቃል። የሁለቱ ማኀበራት ውህደት አባት እና ልጅ ለእናት ዓለም ጎንደር ሠላምና ዕድገት ዘብ እንደቆሙ በተግባር የታየበት ሆኖ በታሪክ ተመዝግቧል።
ይህን በማስመልከት ነገ እሁድ የካቲት 19/2015 ዓ.ም. በማዕከላዊ ጎንደር ዞን አዳራሽ ከ2000 በላይ እንግዶች በተገኙበት የሰላምና ልማት ምክክር መድረክ ተዘጋጅቷል። በመድረኩም የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በእንግድነት ይታደማሉ።
አዲሱ የሲቪክ ማኀበርበሰላምና ልማት ዙሪያ ከሚሰሩ በዐማራ ክልልና በሌሎች አካባቢዎች ከተቋቋሙ አቻ ማኀበራት ልምድና ተሞክሮዎችን ለመቅሰም ሁሌም ዝግጁ መሆኑን የገለፀ ሲሆን፤ ከዚህ ቀደም በሁለቱ ማኀበራት አስተባባሪነት ጎንደር ከተማና በአዲስ አበባ ባደረጋቸው የምክክር መድረኮች የጎጃም፣ የሸዋና የወሎ አቻ ማኅበራትን በመጋበዝ የመማማርና አጋርነትን የማጠናከር ስራዎችን መስራት እንደተቻለው በቀጣይም ይህን የአቻ ማኀበራት አጋርነት አስፍቶና አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልፆል።
የጎንደር ሰላም፣ የዐማራ ሰላም፣ የኢትዮጵያ ሰላም፣ የጥቁር ሕዝቦች ሰላም ነው!
1.4K views17:04