Get Mystery Box with random crypto!

ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy

የሰርጥ አድራሻ: @zephilosophy
ምድቦች: ያልተመደበ
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 18.78K
የሰርጥ መግለጫ

"Strong minds discuss ideas, average minds discuss events, weak minds discuss people."
Rinu Ruzvelt

Ratings & Reviews

3.67

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

2

3 stars

1

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 7

2023-01-19 20:23:22 ተመለሱ(Return ye)-2
Osho comments on (Jesus of Nazareth )

ኢየሱስ እና ይሐንስ  "ተመለሱ (ተፀፀቱ)" ሲሉ እስካሁን ድረስ ከኖራችሁበት እና ከሆናችሁበት መላው መንገድ ተመለሱ ማለት ነው፡፡ ይህ ከአንድ ሰው ይቅርታ የመጠየቅ ጥያቄ አይደለም፡፡  "መፀፀት የሚለው ቃል ኦሪጅናል ትርጉሙ "መመለስ ነው፡፡ በአርመንኛ ኢየሱስ እና ዩሐንስ ቋንቋቸውን በመጠቀም "መፀፀት" ሲሉ "መመለስ" ማለታቸው ነው፡፡ እነርሱ "ወደ ምንጩ ወደ ኦሪጅናል ፍጥረታችሁ ተመለሱ" ነው የሚሏችሁ፡፡

እነርሱ እያሉዋችሁ ያሉት እንደ ዜኖች "ኦሪጅናል ፊታችሁን ፈልጉ" ነው...ይህ ነው ተፀፀቱ" የሚለው ትርጉም፡፡ ሁሉንም ጭንብሎቻቻሁን ጣሏቸው፡፡ ይህ በእናንተ እና በሌሎች መካከል ያለ ጥያቄ አይደለም ፡፡ ይህ በእናንተ እና በእግዚአብሄራችሁ መካከል ያለ ጥያቄ ነው ፡፡ "ተፀፀቱ" ማለት ሁሉንም ዓይነ - እርግቦቻችሁን በማስወገድ በኦሪጅናል ፊታችሁ እሱ እንደፈጠራችሁ ሆናችሁ በእግዚአብሄር ፊት ቁሙ ማለት ነው፡፡
ፊታችሁን ብቻ ሁኑ፡፡ እግዚአብሄር ትሆኑ ዘንዳ በሚፈልገው መንገድ ብቻ ሁኑ፡ ፡ ብቸኛ የሆነውን ፍጥረታችሁን ሁኑ፡፡ ወደ ኦሪጅናል ፊታችሁ ተመለሱ፡፡ ወደ ጥልቁ የፍጥረታችሁ ማዕከል ተመለሱ፡፡ መፀፀት መመለስ ነው፡፡ ይህ አንዱ እና ትልቁ መንፈሳዊ ምልሰት ነው፡፡

እነርሱ የሚሉት " ስታደርጉ የነበራችሁትን ለማየት ሞክሩ ፤ ለመረዳት ሞክሩ ፤ ወደ ውስጥ እና ውስጥ ተመልከቱ ፤ ወደ ዋናው ህልውናችሁ ፍጥረት ፣ ባህሪ ውስጥ ዝለቁ እናም ምን ስታደርጉ እንደነበረ ፣ ምን እንደሆናችሁ እዩ " ነው፡፡ ይህ የምትፀፀቱበትን አንድ የሆነ ነገር የመፈለግ ጥያቄ አይደለም፡፡
የምትፀፀቱት ስለ አንድ የተወሰነ ድርጊት ነው፡፡ ፀፀታችሁ ሁሌም የተወሰኑ ድርጊቶችን ያጣቅሳል፡፡ የኢየሡስ ፀፀት ስለተወሰኑ ድርጊቶች አይደለም፡፡ ይህ ኢየሱስ የሚለው መፀፀት (መመለስ) ስለ ፍጥረታችሁ ነው፡፡እናንተ የነበራችሁበት መንገድ ፍፁም የተሳሳተ ነበር፡፡ ምናልባትም አልተናደዳችሁ ይሆናል፡፡ እስካሁንም ግን የተሳሳታችሁ ሆናችኋል፡፡ ምናልባትም በጥላቻ የተሞላችሁ ላትሆኑ ትችሉ ይሆናል፡፡ እስካሁንም ግን የተሳሳታችሁ ነበራችሁ: ምናልባትም ብዙ ሃብት ላታከማቹ ትችሉ ይሆናል፡፡ እስካሁንም ግን የተሳሳታችሁ ናችሁ፡፡ "ይህ ምን አደረጋችሁ?" የሚለው ጥያቄ አይደለም፡፡ ይህ እንዴት ባለ መንገድ ሆናችሁ እንደነበር የሚለው ጥያቄ አይደለም፡፡ አንቀላፍታችሁ ነበር፡፡ ያልነቃችሁ ነበራችሁ፡፡ ከውስጣዊው ብርሃን ጋር አልኖራችሁም፡፡ የኖራችሁት በጨለማ ውስጥ ነው እንደ ማለት ነው።
አንድ ሰው ወደ መላው ፍጥረቱ መመለስ አለበት፡፡ ከዚያ በኋላ ብቻ ነው ሽግግር የሚቻለው

@Zephilosophy
@Zephilosophy
910 viewsedited  17:23
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-19 14:57:49 ተመለሱ(Return ye)
Osho comments on (Jesus of Nazareth )

IN THOSE DAYS CAME JOHN THE BAPTIST, PREACHING IN THE WILDERN OF JUDAEA, 1 በነዚያም ቀናት (ወራት) መጥምቁ ዩሐንስ በይሁዳ ምድረ- በዳ እየሰበከ መጣ

የዩሐንስ ስም "መጥምቁ ዩሐንስ" ሆነ፡፡ በመላው ዓለም ታሪክ ማንም ስሙ ከጥምቀት ጋር የተያያዘ የለም፡፡ እሱ በመቶ የሚቆጠሩ ሰዎችን አነሳስቷል፡፡ እናም እርሱ ሰዎቹን ያነቃቃበት የነበረው መንገድ በጣም ልዩ ነበር፡፡ እሱ ያነሳሳቸው የነበረው በዩርዳኖሥ ወንዝ ነበር፡፡ በመጀመሪያ ለጥቂት ቀናት ፣ ወራት አልያም ደግሞ ለጥቂት ዓመታት ይመሰጡ ነበር፡፡ ዝግጁ በሚሆኑበት ጊዜም ወደ ወንዙ ይወስዳቸው ነበር፡፡ በወንዙ ውስጥ እሱ በጭንቅላታቸው ላይ ውሃውን ያፈስባቸው ነበር፡፡ እናም አንድ የሆነ ነገር ወደ ብርሃን ይመጣል፡፡ በእነርሱ ጥልቀ - ፍጥረት ውስጥ አንድ የሆነ ነገር ይከሰታል፡፡ እናም እነርሱ በፊት የነበሩትን ዓይነት ሰዎች መሆናቸው ያበቃለታል፡፡ ይህ ሚሥጢራዊ ክብረ-በዓል ነበር፡፡ አንድ የሆነ ነገር ከማስተሩ ወደ ሃዋርያው ይሸጋገር ነበር፡፡ ውሃው እንደ ማስተላለፊያ ነው፡፡
በዓለም ላይ ሁለት ዓይነት መነሳሳቶች ነበሩ፡፡ በአንዱ መነሳሳት ውስጥ ሁሌም ውሃ ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ እናም በሌላኛው ዓይነት መነሳሳት እሳት ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ በህንድ ውስጥ ለምዕተ-ዓመት እሳት እንደ ማነሻሻነት ተላልፎት ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ ዛራቱስቱራ እሳትን እንደ ማነሻሻነት ተላልፎት ተጠቅሟል፡፡

መጥምቁ ዩሐንስ ውሃን ተጠቅሟል፡፡ ሁለቱም መጠቀም ይቻላል፡፡ እና ሁለቱም ጥቅም ላይ ሊውሉ ይገባል፡፡ ውሃ እና እሳት የተለያዩ ብቃቶች አይደሉም፡፡ እናም እስካሁንም ውሃ እና እሳት በጣም በጥልቀት የተያያዙ ናቸው፡፡ እነርሱ ተቃራኒዎች ናቸው፡፡ ዳሩ ግን እርስ በርሳቸውም መሙያዎች ናቸው፡፡ በእንስራ ውሃ በመሙላት እሳት ላይ ብትጥዱት ውሃው ተኖ ይጠፋል፡፡ ውሃውን እሳቱ ላይ ብትደፉት እሳቱ ይጠፋል፡፡
ውሃ እና እሳት ተቃራኒ ናቸው፡፡ ዳሩ ግን ውሃ እና እሳት ጥልቅ አንድነት አላቸው፡፡ ውሃ የሚፈሰው ወደ ታች ነው፡፡ ተፈጥሯዊ በሆነ መልኩ ውሃ ወደ ላይ በጭራሽ አይፈሥም፡፡ ተፈጥሯዊ በሆነ መልኩ እሳት ወደ ታች አይሄድም፡፡ እሳት እና ውሃ በተለያዩ ዳይሜንሽኖች እና አቅጣጫዎች ይንቀሳቀሳሉ፡፡ አንድ ነገር ወደ ታች ዘልቆ ሲገባባችሁ ውሃ እንደ ተላልፎት ጥቅም ላይ ይውላል፡፡ አንድ ነገር በውስጣችሁ ወደ ላይ ቢሄድ እሳት እንደ ተሸከርካሪጥቅም ላይ ውሏል፡፡

መጥምቁ ዩሐንስ ውሃ ያፈስ ነበር እናም በውሃ ፍሰቱም ..ከረዥም ዝግጁነት እና ምስጠት በኋላ መላው ትኩረታችሁ በውሃው ላይ እና በቅዝቃዜው ላይ ጥሞና የሚያደርግ ይሆናል፡፡ ውሃውም ያቀዘቅዛችኋል፡፡ እናም በውሃው የሰውዬው (የመጥምቁ ዩሐንስ) መግነጢሳዊነት በውስጣችሁ የሚፈስ ይሆናል፡፡ ውሃ በጣም ተጋላጭ ተሸከርካሪ ነው፡፡ በእጆቹ ውሃን በመንካት የማዳን (የመፈወስ) ሃይል ያለው አንድ ሰው ቢኖር ውሃው ፈዋሽ መድሃኒትን ይሆናል፡፡ እናም ውሃ ከሰውነታችሁ ጋር በጣም በጥልቁ የተያያዘ ነው፡፡ ከሰማኒያ ፐርሰንት በላይ የሆነው አካላችሁ ምንም ሳይሆን ውሃ ነው፡፡

እናስ ትንፈሳችሁ ምን እያደረገላችሁ እንደሆነ ተመልክታችኋልን? ትንፈሳ እሳትን ያመጣል ይህ oxidation ተብሎ ይጠራል፡፡ አካላችሁ ውሃ ነው ፤ ትንፈሳችሁ እሳት ነው፡፡ የምትኖሩት በእነዚህ በሁለቱ ነው፡፡ ትንፈሳ ሲቆም እሳት ይጠፋል፡፡ ከዚያም አካል ሙቀቱን ያጣል፡፡ ከዚያም ይሞታል፡፡ ውሃ ከአካል ጥርግርግ ብሎ ቢጠፋ አካል በጣም የሚሞቅ ይሆናል ፤ ትኩሳት የሚያንገበግበው ይሆናል፡፡ ቶሎም የምትሞቱ ትሆናላችሁ፡፡ በውሃ እና እሳት መካከል ጥልቅ የሆነ ህብረት እና ሚዛን አለ፡፡ ይህም ሚዛን ቀጣይነት መልኩ ያስፈልጋል፡፡

ምግብ ትመገባላችሁ ... በምግብ ውስጥ እሳት ከፀሃይ ወደ አካላችሁ ዘንድ ይደርሳል። ትተነፍሳላችሁ...በትንፈሳ ውስጥ ኦክስጂን በሰውነት ውስጥ ይደርሳል፡፡ ውሃ ትጠጣላችሁ ቀጣይነት ባላው መልኩ ውሃ በአካል ውስጥ ይደጋገማል ፡ ፡ የምትኖሩት በውሃ እና እሳት መካከል ነው፡፡

መጥምቁ ዩሐንስ ከላይ የሆነን አንድ ነገር ለማምጣት ውሃን ተጠቅሟል፡፡ ያ...አንዱ መነሳሳት ነው፡፡ እዚያ ከፍ ያለው መንገድ አለ ፡- ከውስጣችሁ ያለን ነገር ወደ ላይ እንዲጓዝ የማድረግ መንገድ ነው፡፡ ከዚያ በኋላም ይህ ወደ ላይ የሚደረገው ጉዞ አነሳሹ እሳት ነው::መጥምቁ ይሐንስ "እኔስ ለንስኀ በውሃ አጠምቃችኋለሁ፡፡ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ግን ከእኔ ይልቅ ይበረታል፡፡ እርሱ በመንፈስ ቅዱስ እና በእሳት ያጠምቃችኋል ይላል።"

ይቀጥላል....
@Zephilosophy
@Zephilosophy
2.2K viewsedited  11:57
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-17 21:46:18 የታላላቅ ፈላስፎች አባባሎች

1."የጅረቶች ብዛትና የዝናብ መዓት የውቅያኖስ ጣዕም እንደማይበርዙት ሁሉ የመከራ ውርጅብኝም የቆራጥ ሰው ህሊናን በድን አያደርገውም እንዲህ ያለ ሰው የህያውነት ሚዛኑን ይጠብቃልና። "
ሴኒካ

2."የደስታ ምንጭ የምትሞላውና ሳታቋርጥ የምትፈሰው ከውስጣችን በሚፈልቁ ብሩህ አስተሳሰቦችና ስሜቶች ነው።"
ዊሊያም ላዩምፊሊፕስ

3."ቅንዓት ሲመገብ ያደገ ፍቅር አሟሟቱ ከባድ ነው።"
ላቭስ ኩዩር

4.‹‹ እውነት እርቃኑን በባዶው መራመድ ይችላል፡፡ ውሸት ግን ሁልጊዜ
አምሮና ደምቆ መልበስን ይፈልጋል፡፡ ››
ካህሊል ጂብራን

5.በገንዘብህ የጥቅም ጓደኞችን ልታፈራ ትችላለህ በውበትህ የስሜት ጓደኞች ልታፈራ ትችላለህ በእምነትህና በስነምግባርህ ግን..
የህይወት ጓደኞችን ታፈራለህ።
unknown

6."ህይወት ጨካኝ መምህር ነው!!! ምክንያቱም መምህር አስተምሮ ነው የሚፈትነው ህይወት ግን ፈትኖ ነው የሚያስተምረው።"
ስብሃት ገ/እግዚአብሔር

7.የራስህን የህይወት እቅድ ዲዛይን ካላደረግክ ዕጣ ፈንታህ የሚሆነው በሌሎች እቅድ ውስጥ መኖር/መውደቅ ይሆናል።
- ጂም ሮን

8.የወደፊቱን ለመተንበይ የተሻለው ዘዴ፤ ወደፊትን መፍጠር ነው።
- አለን ኬይ

9.ከጌታዬ ሶስት ነገሮችን አጥብቄ እፈልጋለሁ አንድ ጥበብ ሁለት ጥንካሬ ሦሥት ፍቅር። ከነዚህ ከሦስቱ የበለጠ የምሻው ግን ፍቅርን ነው።ፍቅር ሲኖረኝ  ሁሉም ነገር አለኝ ነፃነትም ቢሆን "
ማርቲን ሉተር ኪንግ

10."ልብህ ይናገር ዘንድ ምላስህ ዝም ይበል። እግዚአበሔር ይናገር ዘንድ ደግሞ ልብህ ዝም ይበል።"
አባራሀኒ

@Zephilosophy
@Zephilosophy
987 viewsedited  18:46
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-17 19:25:30 አእምሮአችን እየተጠቀመብን ነው ወይስ እየተጠቀምንበት?

አእምሮ መሳሪያ ነው። የምትጠቀምበት የሆነ አንድ የተለየ ተግባርን ትከውንበት ዘንድ ለአንተ የተዘጋጀ መሳሪያ፡፡ እናም ተግባሩ ተከውኖ ሲያልቅ የምታሳርፈው ድንቅ መሳሪያ (ማሽን) ነው። ከ80 እስከ 90 በመቶ ያህሉ የአብዛኛዎቹ ሰዎች ሀሳብ ተደጋጋሚ እንዲሁም የማይጠቅም እንቶ ፈንቶ ነው፡፡ ይህም ብቻም አይደለም አዕምሮ በተፈጥሮው ፈሩን የመልቀቅና አሉታዊ ነገሮች ጋር የመጠናወት አባዜ አለበት። እናም አዕምሮ ይህ አይነቱ ባህሪ ስላለበት የጥቅሙን ያህልም ጎጅነቱም የዚያኑ ያህል ነው። አዕምሮህን ልብ ብለህ አስተውለው እናም ይህ እውነት መሆኑን እራስህ ትደርስበታለህ።

እንደ እውነቱ ከሆነ አዕምሮ የዚህ አይነቱ በሀሳብ የመጠመድ አባዜ ሱስ ይሆንበታል፡፡ ልክ እንደማንኛውም ሱስ አስያዥ ነገር አዕምሮም የማሰብና በሀሳብ የመባዘን ሱስ ይይዘዋል። ለመሆኑ የሱስ መገለጫዎች ምንድን ናቸው። እጅ ሰጥተሀል፣ ለመተውም አቅቶሀል፣ ለመተው አማራጭ እንዳለህ እንኳ አልታይህ ብሎሀል። ሱሡ ከአንተ የበለጠ ብርቱ የመሰለብህ ሆኗል። በተጨማሪም ሱሡ የውሽት የሆነ የደስታ ስሜትን ሰጥቶሀል፣ ውሎ አድሮ በስተመጨረሻ ስቃይ የሆነ ደስታ፡፡

ለመሆኑ ማሰብ ምን ሊፈይድልን ነው ከማሰብ ጋር ሱስየሚይዘን?

ምክንያቱም አንተ ከአዕምሮህ ጋር እንዲሁም ከሀሳብ ጋር ተቆራኝተሀልና ነው። ማለትም አንተ ማንነትህን የምትረዳውና የምትመዘዉ ከአእምሮህ ውስጥ ከታጨቀ ፍሬ ሀሳብና ድርጊት ስለሆነ ነው፡፡ ምክንያቱም ማሰብ ካቆምኩ አከተመልኝ ብለህ ስለምታምን ነው፣ አስተዳደግህን ተከትሎ በተገራህበት ግለሰባዊና ባህላዊ አተያይ መሰረት በአዕምሮህ ውስጥ የማንነት ምስል ትፈጥራለህ፡፡ ይህንን ምስልም የእራስ ወዳዱ እኔነት የገዛ ራሱ መንፈስ ብለን ልንጠራው እንችላለን፡፡ ይህ የአዕምሮ ተግባራቱንም ያካትታል፡፡ እናም አዕምሮ ህልውናውን የሚያስቀጥለውም ያለማቋረጥ በማሰብ ነው። እራስ ወዳዱ እኔነት (Ego) የሚለው ቃል ትርጉም ከሰው ሰው ይለያያል፣ እኔ ግን ቃሉን እዚህ ላይ የምጠቀምበት እንዲህ በሚል አንድምታ ነው፤ በንቃተ ህሊና አልባነት ምክንያት ከአዕምሮ ጋር በተደረገ ፅኑ ቁርኝት የተፈጠረ የውሸት ማንነት።

ለእራስ ወዳዱ እኔነት፣ ለእርሡ የአሁን ገዜ የሚባል ነገር የለም፤ ለእራስ ወዳዱ እኔነት አስፈላጊውና እግምት የሚገባው የባለፈውና የወደፊቱ ብቻ ነው። ሀቁ ግን ፈፅሞ የተገላቢጦሽ ሁኖ ሳለ፣ ይህንን የአሁን ግዜ አላስፈላጊ፤ የባለፈውና የወደፊቱ ግን አስፈላጊ እንዲሆን ያደረገው በእራስ ወዳዱ እኔነት ስልተ ዘዬ አዕምሮ ፈፅሞ ፈሩን እንዲስት ስለተደረገ ብቻ ነው። እራስ ወዳዱ እኔነት ሁልግዜም ቢሆን ግድ የሚለው የባለፈው ነው የባለፈውን ነፍስ ይዘራበታል፣ ምክንያቱም የባለፈው ከሌለማ አንተ ማን ቢሉህ ማነኝ ትላለህ? እራስ ወዳዱ እኔነት ህልውናውን ለማስጠቀጠል እራሡን ያለማሰለስ ከወደፊቱ ጋር ይተልማል እራሱንም ከወደፊቱ ትልም ውስጥ ያስገባል። እንዲሁም ደግሞ ስኬትን ወይም እፎይታን ከወደፊቱ ይሻል።

ወይም ደግሞ አዕምሮ፣ እርሡው እራሡ ለወደፊቱ ለተለመው ትልም ውጤት ሲል የአሁን ግዜን ከቁብም የማይቆጠር ያደርገዋል። እስቲ አዕምሮህን ልብ ብለህ አስተውለው፣ እናም ይህ እንዴት እንደሚሠራ እራስህ ታየዋለህ፡፡

የአርነት መውጫን ቁልፍ የያዘው የአሁን ግዜ (የአሁን ቅፅበት) ነው፣ ነገር ግን አንተ አዕምሮህን እስከ ሆንክ ድረስ፣ ማለትም አዕምሮህ ማለት አንተ፣ አንተ ማለት አዕምሮህን እስከሆንክና ከአዕምሮህ ጋር እስካልተፋታህ ድረስ ይህን ቁልፍ አታገኘውም፡፡

እዚህ ላይ አንድ ማስተዋል ያለብን ነገር አለ፤ ይኸውም ማሰብና ንቃተ ህሊና አቻ ትርጉም የላቸውም ፤ አቻም አይደሉም፡፡ ማሰብ የንቃተ ህሊና ቁንፅል መገለጫው ነው፡፡ ማሰብ ያለ ንቃተ ህሊና ህልውና ሊኖረው አይችልም፤ ንቃተ ህሊና ግን ያለ ሀሳብ እራሱን ችሎ መቆም ይችላል።

መገለጥ (የበራ ህይወት) ማለት ከሀሳብ ልቆ መገኘት ማለት ነው። መገለጥ ማለት ወደ ሀሳብ ደረጃ አለመቀልበስ ማለት ነው፡፡ ሁኖም ግን የእንስሳትና የእፅዋት ደረጃ ወደ ሆነው ከማሰብ በታች መውረድ ማለት አይደለም፡፡ የመገለጥ ሁናቴ ውስጥ መሆን ማለት አስፈላጊ በሆነ ጊዜ፣ የሚያስበውን አዕምሮህን መጠቀም ትችላለህ፡፡ እናም ደግሞ ስትጠቀምበትም ከበፊቱ ይልቅ በበለጠ አትኩሮትና ብቃት ትጠቀምበታለህ፡፡ ሁኖም ግን ከአንተ እውቅና ውጭ ለሚደረግ የአዕምሮ በሀሳብ መባዘንና ከአዕምሮ ውስጥ ውስጡን ማብሰልሰል ነፃ ነህ፡፡

እናም ደግሞ አንተ አዕምሮህንም ስትጠቀምም፣ ውስጣዊ መረጋጋትህም እንደተጠበቀ ሲሆን፣ በተለይ ደግሞ የሆነ አይነት የፈጠራ መፍትሔ በሚፈለግበት ወቅት በየጥቂት ደቂቃዎቹ አንድ ግዜ ወደ ማሰብ ሌላ ግዜ ደግሞ አዕምሮን ከሚላጋበትና በሀሳብ ከሚቆዝምበት ሁናቴው አውጥተህ እንዲሰክን እያደረግክ ስራህን ትከውናለህ፡፡ ማለትም አዕምሮ አለ፣ አዕምሮ የለም አይነት በነዚህ በሁለቱ መካከል አዕምሮህን በተገቢው መንገድ ትጠቀምበታለህ። አዕምሮ ሳይኖር ማለት ከሀሳብ ነፃ ሁኖ በንቃተ ህሊና ውስጥ መሆን ማለት ነው።

በተጨማሪም አሪፍ የሆነ የፈጠራ ሀሳብ የሚፈልቅልህ በዚህ ሁናቴ ስታስብ ብቻ ነው፤ ምክንያቱም ሀሳብ የነጠረ አቅም የሚኖረው በዚህ መንገድ ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ ሀሳብ ህልቆ መሳፍርት ከሌለው ንቃተ ህሊና ጋር ካልተሳሰረ ግን ብዙም ሳይቆይ ባድማ፣ የተቃወስ እንዲሁም አጥፊ ይሆናል፡፡

የመኖር ዋስትና አቢይ ማሽኑ አዕምሮ ነው። አዕምሮ ከሌሎት አዕምሮዎች ጋር በመፋለም፣ በመከላከል መረጃን ማግኘትና መተንተን የሚችለው አዕምሮ ነው። ሁሉም እውነተኛ አርቲስቶች አውቀውትም ይሁን ሳያውቁት ፈጠራቸው የፈለቀው እንበለ አዕምሮ (አዕምሮ ሳይኖር) ውስጣዊ ርጋታና ስክነት ካለበት ከውስጥ ነው። ታላላቅ ሳይንቲቶች የሚባሉትም እንኳ የፈጠራ ስራቸው ከች ያለላቸው በአርምሞ ውስጥ ሁነው እንደሆነ ተናግረዋል።

ምንጭ ፦ የአሁን ሀያልነት
ደራሲ ፦ ኤክሀርት ቶሌ
ትርጉም ፦ብስራት እውነቱ

@Zephilosophy
@Zephilosophy
673 views16:25
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-17 11:00:22 ሰው ከእንስሳ በምን ይለያል?

ምንጭ ፦ የፍልስፍና አፅናፍ
ፀሀፊ    ፦ አለማየሁ ገላጋይ

የሰው ልጅ ከእንስሳት ሁሉ የሚለይበት መሰረታዊ አፈጣጠር አለው የሚለውን አመለካከት መጠራጠር የጀመሩት አንዳንድ የቅርብ ጊዜ ፈላስፎች ናቸው፡፡ ከፕሌቶ አንስቶ እስከ አስራ ዘጠነኛው ክፍለ ዘመን ድረስ በተዋረድ የተዘረጋ የምዕራባውያን የእሳቤ ባህል ውስጥ ሰውና ሰው ብቻ ምክንያታዊ እንስሳ ነው በሚል ተደምድሞ ቆይቷል፡፡ ይሄ ሰውን ከእንስሳት ሁሉ የተለየ አድርጐ የሚያስቀምጠው ፍልስፍና ሰው ብቻ በእግዚአብሔር አምሳል መፈጠሩን ከሚያስተምረው ከመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ጋር የተስማማ ነበር ለማለት ይቻላል፡፡

በእንግሊዛዊው የተፈጥሮ ሳይንስ ሊቅ ቻርልስ ዳርዊን ዘመን ተቃራኒው አመለካከት ብቅ ማለት ጀመረ፡፡ አመለካከቱ ከሳይንሱ ቤተሰብ ወጥቶ እስከ ልሂቃኑ ድረስ የተዛመተ ነበር᎓᎓ የዳርዊን አስተምህሮት ንድፈ ሀሳብ አንተም እንደምታውቀው የሰው ልጅ እና የዝንጀሮ የዘር ግንድ አንድ ነው ብሎ ደምድሟል፡፡ ድምዳሜው ወዴት እንደሚያመራ ግልፅ ነው፡፡ የሰው ልጅ ስር መሰረታዊ የዝግመተ ለውጥ ምርምር ሰው ከአጥቢ እንሰሳት ሁሉ የሚለየው በአስተሳሰብ ደረጃው ብቻ እንደሆነ ያስተምራል፡፡ የዝግመተ ለውጥ ተመራማሪዎቹ ሰው ብቻ ምክንያታዊ እንስሳ ነው ለሚለው የቀድሞ ድምዳሜ ሌላ የምርምር መዳረሻቸውን ይዘው ብቅ ብለዋል፡፡ በሰውና በተቀሩት እንስሳት መካከል ያለው አስተሳሰብ አንድ ነው፡፡ ሰው ግን ላቅ ያለ የአስተሳሰብ ደረጃ አለው ይላሉ፡፡

የሰው ልጅ ሌሎች እንሰሳት የሌላቸው ኃይል እንዳለው ማረጋገጫ የሚሆነን አንዳንድ ምሳሌዎችን መጥቀስ እንችላለን፡፡ የሰው ልጅ በአግባቡ የሚያከናውናቸው እንስሳት ግን ጨርሶ የማይሞክሩት ነገር አለ፡፡ እሱም
አንዳንድ የሚያበጃጃቸው ነገሮቹ ናቸው፡፡

እርግጥ ነው ንቦች ? ፎ እንደሚሰሩ አውቃለሁ:: ወፎች ጎጆአቸውን፤ ፍልፈሎች ጉድጓዳቸውን ያበጃሉ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ሁሉ የእንስሳቱ ተግባር በደመነፍሳዊ ግፊት የሚከናወኑ ናቸው᎓᎓ ወፎች ሁሉ ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተቀባበሉ የሚሰሩት ያንኑ ተመሳሳይ ጎጆ ነው። ይሄ የሚያሳየን የወፍ ጐጆ የደመነፍስ ግፊት እንጂ በአስተሳሰብ መዳበርና በነፃነት የሚገኝ የጥበብ ውጤት አለመሆኑን ነው። ቤት መገንባት፣ ድልድይ ማበጀትና በመሳሰሉት ተግባራት ላይ የሰው ልጆች የፈጠራ ችሎታቸውን ያውላሉ፤ አንዱን ከሌላኛው ይመርጣሉ፤ በዚህም ሌሎች እንሰሳት የሌላቸው ትክክለኛ የጥበብ ተስዕጦ ባለቤት እንደሆኑ ይመሰክራሉ፡፡

የሰው ልጅ ብቻ ነው የማምረቻ ማሽኖችን የሚሰራው፡፡ ልብ በል ሰው የሚፈልገውን ነገር የሚሰራት ማምረቻ። ሌሎቹ እንሰሳት ባገኙት መሳሪያ ይጠቀሙ እንዳደሆን ነው እንጂ ጥሬ እቃውን ወዳለቀለት ምርት እየቀየረ በፍጥነት የሚስራ ሌላ ማሽን አይሰሩም፡፡ ይህም ሰውን ከሌሎች እንሰሳት ሁሉ የበለጠ ነገሮችን የማበጃጀት ልዩ ችሎታ እንዳለው የሚያመላክተን ምሳሌ ነው፡፡

እንስሳት ምክንያታዊነት እንዳላቸውም ጠቆም አድርገሃል፡፡ እኔ እንደሚገባኝ የተሻለ ትክክል የምንሆነው እንሰሳት ችግር ባጋጠማቸው ጊዜ ከችግር የሚወጡበት ተፈጥሯዊ ግፊት እንዳላቸው የተናገርን እንደሆነ ነው፡፡ ወይም የሚፈልጉትን ለማግኘት እንደዚያው የተፈጥሯዊ ግፊት ዘዴ እንደሚዘይዱ ያሰብን እንደሆነ ነው፡፡ የእንስሳትን «አስተሳሰብ» ሁሉ በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ልናየው ይገባል። የትኛውም እንስሳ ለማሰብ ቁጭ አይልም፡፡ ፈላስፎች ሆነ የሂሳብ ሊቶች የሚያከናውኑት ነገር ሁሉ ለህይወት ከሚያስፈልግ የተፈጥሮ ደመነፍሳዊ ግፊት ነፃ ነው፡፡

የሰው ልጅ አስተሳሰብ በዙሪያ ጥምጥም የሚከናወን ግራ ፈትልና ቋንቋ የተቀላቀለበት መሆኑ እንሰሳት ከሚጠቀሙበት ችግር መፍቻ የተለየ ያደርገዋል። በእርግጥ እንሰሳትም ስሜታቸውን የሚገላለጡበት የእርስ በእርስ መግባቢያ ድምፅ ያወጣሉ፡፡ ነገር ግን በሃሳብ መካፈል ደረጃ ተግባቦት ያላቸው እንስሳት የሉም፡፡ የነገሮችን ትክክለኛነት ለመተማመን የእሰጥ-አገባ ሙግት የሚገጥሙ እንሰሳት እስካሁን አልታዩም። ይሄንን ለማድረግ የሚችለው አመክኑያዊ እንስሳ ሰው ብቻ ነው::

እንዲህ ያሉ ብዙ መረጃዎችን መስጠት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ሰው ከእንስሳት ሁሉ በላይ በተፈጥሮ የተቀባ መሆኑን የሚያመላክት አንድ ማስረጃ አቅርቤ ነገሬን በዚሁ በአቅብ ነው የመረጥኩት፡፡

በታሪካዊ ሂደት እራሱን እያጐለበተና ልምዱን እያዳበረ የመጣ እንስሳ ሰው ብቻ ነው᎓᎓ የተቀሩት እንስሳት በተፈጥሮ ሂደት በመቶ ሺህ ትውልድ ውስጥ የራሳቸውን የአካል ለውጥ አግኝተው ይሆን ይሆናል እንጂ የታሪካዊ ሂደት ለውጥ ተጠቃሚዎች አይደሉም፡፡ ምክንያቱም በደመነፍስ ከሚወርሱት የአኗኗር ዘዬ ውጭ በትውልድ ቅብብል እያሳደጉ የመጡት እውቀት የላቸውም፡፡ ሰውን ያየን እንደሆን ልምዶቹንና ባህሎቹን ከአንዱ ትውልድ ወደሌላው በማሸጋገር ሀሳቦችንና ተቋማቶቹን በማሻሻል እያደረጀ እዚህ እንደደረሰ ከታሪኩ እንረዳለን፡፡

በእኔ ሐሳብ የሰው ልጅ በአፈጣጠሩ እንደማንኛውም እንሰሳ ይሁን እንጂ በምክንያታዊነቱ ግን ከተርታዎቹ እንስሳት እራሱን ነጥሎ ልዩ ቦታ የተቀመጠ አስደናቂ ፍጡር ነው፡፡ በዚህና በሌላ ምክንያቶች የዳርዊንን የሰው ልጅ ዝግመተለውጣዊ ንድፈ ሐሳብ የምናጣጥልበትን አቋም እናገኝ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ስለንድፈ ሐሳቦች መያዝ ያለብን አንድ እውነታ አለ፡፡ ንድፈ ሀሳቦች ሐቅን ፈልፍሎ ለማውጫ እንጂ ሐቅን ለንድፈሐሳብ ማዳበሪያ ብቻ መጠቀም እንደሌለብን ነውና፡፡

@Zephilosophy
@Zephilosophy
1.5K views08:00
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-15 10:41:01 መንጋነትን ተፀየፍ

ሲግመን ፍሮይድ፣ አርኪመድስ፣ ኒቼ፣ ቻርለስ ዳርዊን፣ ጋሊሊዮ፣ ሶቅራጥስ፣ ቡድሃ፣ ቶማስ ኤዲሰን፣ ቫን ጎ፣ የእኛው ሀገር ፈላስፋ ዘርዓያዕቆብ ... ሌሎችም ሌሎችም በየስርቻው በየጉራንጉሩ በእኛም ሀገር ጭምር አሉልህ፡፡ አብዛኞቹ በዘመናቸው የተወገዙ ወይ አድማጭ ያጡ  ነበሩ፡፡ ዛሬ እግርህን በጀብደኝነት አንፈራጠህ ቆመህ ሰልፊ (ራስ በራስ ፎቶ) የምትነሳበትን ስልጣኔ የመሰረቱት ግን እኔው ዘመንን የቀደሙ የትናንት መሰሎችህ ነበሩ፡፡ ካምቤል ኢጁጋርጁክ የተሰኘ የካናዳ ካሪቦ ኢስኪሞ ጎሳዎችን መንፈሳዊ መሪ አባባል ይጠቅሳል፡፡ ኢጁጋርጁክ እንዲህ አለ....

"እውነተኛ ጥበብ ከሰው ልጅ ተሰውራ ትገኛለች፡፡ በታላቅ ሕመምና የብቻ አርምሞ ካልሆነ የሚደረስባት አይደለችም፡፡ ፈተናን መጋፈጥና ብቻነት ግን ወደዚህ ድብቅ ዕውቀት መገኛ ስውር ቦታ አዕምሮን ይመራሉ፡፡"

የምንኖረው ግን በጅምላ በሚመለክበት፣ በጅምላ በሚወገዝበት፣ በጅምላ በሚኮነንበት፣ ሽያጩም፣ ዘረፋውም፣ ግድያውም፣ ቀብሩም ጅምላ ሆኖ ተነጥሎ መቆም ወንጀል በሆነበት ማኅበረሰብ ውስጥ ነው፡፡

እናስ በዚህ ሂደት ከመንጋው የመነጠል፣ ከዘመን የመጣላት፣ ከትውልድ የመኳረፍ አዝማሚያ የሌለው ጠቢብ የመንጋውን መፈክር በውብ ቃላት ሸላልሞ ከማተም በስተቀር ረብ ያለው ሀቲት ሊወጣው ይችላልን? ምንኖረውን የሆነውን ለመጻፍ፣ ለመዝፈን፣ ለማቅለም፣ ለማሰማመር ብዙ መጣር አርቲስት መሆን ያስፈልጋል እንዴ? በየትኛውም ዘመን ተወለድ (በእኛም ዘመን ይሁን) ብዙዎች ከሚስማሙበት ከተለየህ፣ ብዙዎች የሚያደንቁት ካልመሰጠህ፣ ብዙዎች በጅምላ የሚጠሉትን ካልጠላህ ውግዘት ውርደት፣ ግዞት ይደርስብሃል፡፡ ምክንያቱም አንተ የሚቀጥለው ትውልድ አባል ነህ፡፡

የእኛን ነገር እንኳን ተውት፣ ተውት አዲስ አተያይ ማመንጨቱን፣ የሚቀጥለውን ትውልድ ትልም የማርቀቅ ቅብጠቱን ተውት... ተውት፡፡ እኛ ከዘመንና ከትውልድ መኳረፍ ያቃተን፣ ዘልማዳዊ የነተበ ሕይወት የማይሰለቸን፣ አንሰን አንሰን የምናሳንስ፣ በአጥንት እንደሚጣሉ የተራቡ ውሾች እርስ በእርስ የምንናከስ ሕዝቦች ነን፡፡

ለብቻ መቆም መቻል ግን ውበት ነው፡፡ ፅናት ነው፡፡ ጥንካሬ ነው፡፡ ለብቻ መቆም(solitude) መሟላት እንጂ መነጠል (isolate) አይደለም፡፡ መነጠል ብሎ ነገር የለም፡፡ የምትነጠለው ጉልህ ስብዕና አጥተህ ተጀምለህ  የተቆጠርክ ዕለት ነው፡፡ እንደ ጉሬዛ ከዛፍ ዛፍ እየዘለልክ ብትኖር እንኳን ከሰው እንጂ ከምልዓተ ዓለሙ መነጠል አትችልም፡፡ ማንም ሁን ከየትም ና አንተ የምልዓተ ዓለሙ የልብ ትርታ ነህ። አንተ አንተን መሆን ከቻልክ ያለ አንተ ዓለሙ ይጎድላል፡፡

ተደርቦ ተጀምሎ መቆጠርን ተፀየፍ፡፡ በስብዕናህ ራስህን ችለህ ስትር ብለህ መቆምን ቻልበት፡፡ ሰዎችን በሙሉ ልብህ ተቀበል፡፡ ለመሸኘትም ግን ምንጊዜም ዝግጁ ሁን፡፡ በጊዜ ውስጥ አስቀድሞ ያልሆነ ምንም ነገር የለም፡፡ መወለድህም፣ መሸለም መጋዝም በጊዜ ውስጥ ቀድሞውኑ የታሰበ ነው፡፡ ይኼንን ማሰብ መቀበል ስለማትፈልግ ዘወትር ለእያንዳንዷ የሕይወት እርምጃ እንግዳ ትሆናለህ፡፡ ቀላል እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡

ይኼንን የምነግርህ እኔ እንኳን ዘወትር እንደ ተማሪ ነኝ፡፡ ከሰው ልትደበቅ ትችላለህ፡፡ ማንም ግን ከራሱ መደበቅ አይችልም፡፡ በራስህ ምላስ መቅመስ ካልቻልክ አንተ ጣዕምን አታውቃትም፡፡ ብቻህን መቆም ከቻልክ አንተ ነፃ ወጥተሃል፣ ክንፎችህን ሰርተሃል፡፡ ነፃ በወጣህ ጊዜ ሕይወትን በምልዓት ትኖራታለህ፡፡ ሁልጊዜ ከራሳቸው መታረቅ ተስኗቸው ቀላሉን መንገድ በመሻት እንደሚማስኑ ደካሞች አትሆንም፡፡

ግለሰቦች ሲሳሳቱ ስህተቱ ከራሳቸው ወይም በጣም ከጥቂቶች የተሻገረ ጥፋትን አያስከትልም፡፡ መንጋው ከተሳሳተ ግን አያድርስ ነው፡፡ የመንጋው፣ የጅምላው ስህተት የሚያደርሰውን የጥፋት መጠን ለማወቅ ሩዋንዳን መጥቀሱ ብቻ ይበቃል፡፡ መንጋው እንዲያውም ልክ ሆኖ አያውቅም ማለት ይቻላል፡፡ አንተ የዚህ የጅምላ ስህተት አካል መሆንን ተጸየፍ፡፡


አስቀድሜ እንዳወጋሁህ ዛሬ ዘመናዊው ዓለም የደረሰበትን የኑረት ቅኝት የቀረጹት ሺኅ እንኳን የማይሞሉ በራሳቸው መሻት ወይም በመንጋው ግፊት ተገልለው ማሰብ የቻሉ ጥቂቶች ናቸው፡፡ ሌላው ግብስብሱ ለድምቀት ለጭብጫባ ብቻ የሚፈለግ የቤተሙከራ አይጥ ሆኖ አልፏል፡፡ ያልፍማል፡፡ አንተም በፊናህ ጥቂት ስንኝ ቋጥረህ በብዙ የምታቧትር፣ በርካታ የግል አድናቂዎችን ቤት ለቤት እየዞርክ ለመፍጠር የምትማስን ሆነህ ባየሁ ጊዜ ግን አዘንኩልህ፡፡ አንተ ግን ከሰው ይልቅ ሰዎች በልጠውብህ ተቧድነህ ባሩድ ስታሸት ስትወራወር ባየሁህ ጊዜ አነባሁ፡፡

አንተ እኮ አንተ ነህ፡፡ በሰዎች መካከል ስትሆን ደቃቅ አሸዋ ላይ እንደወደቀች አንዲት የጤፍ ዘር ታንሣለህ፡፡ ምርጫህ በሌሎች ምርጫ ይወሰናል፡፡ ድምጽህ በሌሎች ጩኸት ይሸፈናል፡፡ ቁጣህ በሌሎች ግድየለሾች ፌዝ ይከለላል፡፡ ሕማም፣ ሕመምህ በሌሎች ለዛየለሾች ሁካታ ይጨፈለቃል...

ግለሰባዊነት ይለምልም!

ምንጭ-ከባዶ ላይ መዝገን
ደራሲ- ያዕቆብ ብርሀኑ

@Zephilosophy
@Zephilosophy
1.2K views07:41
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-08 20:55:24 "ለምን" የሚባለው ጥያቄ ሆን ተብሎ ተቀብሯል
ቡርሀን አዲስ
ክፍል -2

አቅራቢ -ትዕግስት አንተንጉስ
@zephilosophy
@zephilosophy
846 viewsedited  17:55
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-08 20:33:56 ትምህርት ሰፍቷል ስብዕናችን ወርዷል
ቡርሀን አዲስ
ክፍል -1

አቅራቢ -ትዕግስት አንተንጉስ
@zephilosophy
@zephilosophy
986 viewsedited  17:33
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-06 18:29:48 አከብራለሁ!
(በእውቀቱ ስዩም)

ነገ የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ይከበራል፤ ጥምቀት ይከተላል፤ እኒህን ትልልቅ በዓላት  የሚከሩበትን ቀናት የደነገገችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ናት፤ ስለእርሱዋ የሚሰማኝን ለመናገር ከዚህ የተሻለ አጋጣሚ የማገኝ አይመስለኝም፤

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስትያን የኢትዮጵያ ቀዳሚ አንደበት ናት ፤ የግእዝ ፊደል የተወለደው  ከክርስቶስ ልደት በፊት  በአክሱም ነው፤  ይሁን እንጂ ፊደሉን ከርክመው፥  አሰማምረው ፥  ልገው ፥ ስርአት አስይዘው የዛሬውን መልክ ያስያዙት የኢትዮጵያ ቤተክርስትያን ሊቃውንት ናቸው፤  በአማርኛ በተራቀቅሁ ቁጥር የኒህን ሊቃውንት ውለታ አልዘነጋም::

የሰውን ልጅ  ከበሬ ወይም ከጉማሬ  የሚለየው ባህል ነው፤ በአእምሮ የማይራቀቅ ባህል መፍጠር አይቸልም፤ ኢትዮጵያ ለእንግዳ በኩራት ከምታሳያቸው ደማቅ እና አይነተኛ (ኦሪጂናል) የባህል መለዮዎች መካከል አብዛኞቹ የመነጩት  ከአድባራት ነው፤   እድሜ ይስጠኝ እንጂ ዝርዝሩን እያረፍሁ  አወጋዋለሁ::

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስትያን ባንድ ጊዜ የባህል ሚዝየም እና የባህል መድረክ መሆን ትችላለች፤  በፈርኦኖች ዘመን የኖረ ጽናጽል ብሪቲሽ ሚይዘይም ውስጥ ማግኘት ትችላለህ፤ ጽናጽሉ ወደ ዜማ ሲተረጎም ለመታዘብ  ግን አብማ ማርያም ቤተክርስትያን መገኘት ያስፈልጋል::

የቤተክርስትያን ቅዳሴ መታደም ዝም ብሎ የአማኞችን ጉባኤ እንደመታደም አይደለም፤  የጊዜ መኪና እንደመሳፈር ነው፤  በሀያ አንደኛው ክፍለዘመንን ለቅቀህ ራስህን  በመካከለኛው ዘመን ውስጥ ታገኘዋለህ፤  አጼ ናኦድ ያደመጡትን ዜማ  መስማት መቻልህ ካላስደነቀህ ምን ሊያስደንቅህ ይችላል?  ምንጅላቶችህ ያሸተቱትን እጣን ወይም ከሴ ማሽተት መቻልህ ካላስገረመህ ምን ሊያስገርምህ ይችላል?  እኔ  እንዲህ አይነቱን  እድል ጊዜን እንደማስገበር እቆጥረዋለሁ::

የብሉይን መጽሀፍት ብታነቢ የጥንታዊ እብራውያን ታሪክ፤ ባህል እና ህልም ታውቂያለሽ፤ ሀዲስ ኪዳንን ስታጠኚ  የጥንት እብራውያን ግሪካውያን እና ሮማውያን እምነት፤ ህልም  እና ስነልቦና ትገነዘቢያለሽ፤  የቀደምት አባቶችሽ እና እናቶችሽ ምን  ያስቡ እንደነበር ለመረዳት ከፈለግሽ  ግን የጻድቃን ገድላትን ማንበብ ይጠበቅብሻል፤   የኢትዮጵያውያንን ስነጽሁፍ፥ ስነልቦና ፥ መልክአምድር  ለማወቅ የሚገደው ሰው የጻድቃን ገድላትን እና ድርሳናትን መመርመር ይጠበቅበታል::

በአርባ ቀኔ ማንኩሳ ሚካኤል ተጠምቂያለሁ፤ የልደት ስሜም ወልደሚካኤል  መሆኑ ይታወቅልኝ! በባህል  ረገድ ራሴን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ  ቤተክርስትያን እመድባለሁ፤  ያም ሆኖ ዓለማዊነቴን  ለመሸመጥጥ አልሞክርም፤     ሊቁ አድማሱ ጀምበሬ  “ የምናውቀውን ዓለም በማናውቀው  ዓለም  እንለውጣለን”  ይላሉ፤  ይመቻቸው! እኔ የሚታወቀውን ዓለም  በማይታወቀው ዓለም  የሚያስለውጥ ምክንያት እስካሁን  አልገጠመኝም፤   የሚታወቀውን ዓለም  ከነ ትርኪምርኪው  በጸጋ እጄን ዘርግቼ፥ ልቦናየን ከፍቼ እቀበላለሁ:: በምድር ስኖር የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ  የስልጣኔ ፍሬዎችን ያበረከቱልን ሁሉ ማክበር እና ማመስገን እንደሚገባን ተረድቻለሁ::
ሰናይ በአል!

@Zephilosophy
@Zephilosophy
795 views15:29
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-01-06 15:17:13 እውነት ምንድነው?

ምንጭ ፦ የፍልስፍና አፅናፍ
ፀሀፊ ፦ አለማየሁ ገላጋይ

በአንዳንድ መመዘኛዎች አብዛኛው ሰው እውነት ብሎ የተስማማበት ነገር ከሞላ ጐደል እውነትነት አለው ተብሎ ይታሰባል፡፡ ይሁንና ይሄ ብያኔ ከብዙ የእውነታ ማረጋገጫ መንገዶች አንዱ እንጂ የመጨረሻ ማጠቃለያው እንዳልሆነ ልብ ማለት ይገባል፡፡ ስለዚህ አንተም ሆንክ የሀዲስ ኪዳኑ ጲላጦስ «እውነት ምንድር ነው?›› ስትሉ ለጠየቃችሁት የጓደኞችህ መደምደሚያ አርኪ ምላሽ አይሆንም።

ከሁሉም በፊት ውሸት እንድንናገር የሚገፋፉን ነገሮች ምንድን ናቸው ብለን መነሳት የእውነትን ተፈጥሮ መርምሮ ለማግኘት ይረዳናል:: አንድ ሰው እንደማያፈቅራት ልቡናው የሚያውቀውን ሴት ‹‹አፈቅርሻለሁ› ቢል ውሸት ተናግሯል ማለት ነው:: ወይም አንድ ልጅ የብስኩት ማስቀመጫውን አድፋፍቶ እያለ እናቱ ስትጠይቀው ‹‹አላደረኩም›› ቢል ዋሽቷል፡፡ ውሸት ማለት የምታውቀውን የምታስበውንና የሚሰማህን ክደህ መናገር ነው፡፡ እንዲህ ያለው ድርጊት በየዋህነት ወይም በስህተት ከሚፈፀመው የተለየ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ የእግር ኳስ ዳኛ በአጠራጣሪ ሁኔታ የገባን ጎል ቢሽር ማለት ነው፡፡

የቅርብ ጊዜው አሜሪካዊው ታላቁ ፈላስፋ ጆሲያህ ሮይስ (Josiah Royce) ለውሸት ትርጓሜ ሲሰጥ የሰው ልጅ ይሆነኝ ብሎ የድርጊት መወከያ ቃላቱን በማቀያየር የሚያውቀውን እውነታ ሲቃረን ነው ይላል፡፡ «አይደለም» መባል የሚገባውን «ነው በሚልበት ጊዜ፤ ወይም «ነው» ማለት ሲገባው «አይደለም›› ለማለት ሲደፍር። ሮይስ ውሸትን የፈታበት መንገድ ወደ ጥንታዊ የእውነት ትርጓሜ ይመራናል፡፡ ከ2ሺህ 5 መቶ አመታት በፊት ፕሌቶና አርስቶትል በዚሁ መንገድ ለእውነትና ውሸት ብያኔ ሰጥተው ነበር፡፡

ፕሌቶና አርስቶትል እንደሚሉት የጨበጥነው አስተያየት ትክክለኛ መሆኑ የሚረጋገጠው <<ነው» መባል ያለበት <<ነው» ተብሎ ሲገኝ ወይም ‹‹አይደለም› መባል የሚገባው «አይደለም» ሲባል ነው፡፡ በአንፃሩ አስተያየታችን ሐሰት ሆኖ የሚገኘው ደግሞ የተገላቢጦሽ «ነው› መባል ያለበት <<አይደለም» በሚል ተለውጦ ሲገኝ ወይም ‹አይደለም›› በ«ነው» ተተክቶ ስናገኘው ነው፡፡ ፕሌቶና አርስቶትል እንደሚሉት የአስተያየታችን እውነትነት የሚረጋገጠው ከገሃዱ ዓለም ተጨባጭ ሁናቴና ከተፈጥሮ ህግ ጋር እየተመሳከረ ይሆናል፤ አስተያየታችን ከገሃዱ ዓለም ሆነ ከተፈጥሮ ህግ ጋር የተስማማ ሆኖ ከተገኘ እውነትነት ሲኖረው በአንፃሩ ከተጣረሰ ደግሞ ስህተት ተናግረናል ማለት ይቻላል ይላሉ፡፡

ስለዚህ ከላይ እንደተመለከትነው የእውነታን ምንነት አንጥሮ ማውጣት በጣም ቀላል ነው:: ፍቺውንም መረዳት ያን ያህል አዳጋች አይደለም፡፡ ጲላጦስ ኢየሱስን ስለእውነት ምንነት ሲጠይቅ ምናልባትም ምላሹ በኋላ ለሌላ ጥያቄ እራሱን አዘጋጅቶ ነበር «የተነገረን እውነት ይሁን ሐሰት እንዴት ማረጋገጥ እንችላለን? በነገራችን ላይ አንተና ጓደኞችህ ስለእውነት መቋጫ ለመስጠት የሞከራችሁት ለዚህ ለጲላጦስ ያልተጠየቀ ጥያቄ ምላሽ በመሻት ነበር የተነገረን እውነት ይሁን ሐሰት እንዴት ማረጋገጥ እንችላለን?››

ለዚህ ጥያቄ ሶስት ዋና ዋና ምላሾች አሉ፡፡ አንዳንዱ ጉዳይ በራሳችን ተጨባጭ እውነታ የምንዳኘው ነው፡፡ «ድፍኑ ከቁራሹ ይበልጣል›> ይሄ እውነት በራሳችን አይተን ያረጋገጥነው በመሆኑ በየትኛውም አግባብ ተቀይሮ ቢመጣ ልንቀበለው የሚያዳግተን ነው፡፡ ድፍኑን እናውቃለን፤ ቁራሹንም እንረዳለን፡፡ ስለዚህ ቁራሹ ከድፍኑ ሊበልጥ የሚችልበት አንድም መንገድ የለም፡፡ የአንዳንድ ነገር እውነትነት የምናረጋግጥበት አግባብ ቁራሹ ከድፍኑ የአለመብለጡ እውነታን መመዘኛ አድርገን ነው፡፡

ሁለተኛው እውነታን የማረጋገጫ መንገድ ደግሞ ልምድ ወይም ምልከታን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ አንድ ሰው ያለፈው አንድ ወር ሙሉ ቺካጐ ውስጥ አንዴም አለመዝነቡን ቢነግረን ሜትሮሎጂ ያዘጋጀውን የአየር ንብረት ሁኔታ መዝገብ በመመልከት ማረጋገጥ እንችላለን፡፡ ወይም ስለመዋኛው ገንዳ ውሃ ሙቀት ቢነግረን አንድ እግራችንን ሰደድ አድርገን ማረጋገጥ ነው። እዚህ ላይ ሳይንስ ነክ ማጠቃለያዎች እንደ እውነታ የሚወሰዱት ተቃራኒ ሐሳብ እስካላጋጠማቸው ጊዜ ድረስ ብቻ ነው።

ሶስተኛው መንገድ በራሳችን ተጨባጭ እውነታ ሆነ በሶስተኛ ወገን ማረጋገጫነት የምንዳኘው እውነታ ሲያጋጥመን የምንጠቀምበት ዘዴ ነው፡፡ ለምሳሌ ስለአንድ ሰው ባህርይ ሊሆን ይችላል፤ ወይም ስለአንድ ምርት ውጤታማ አገልግሎት እንዲህ ያለው ጥያቄ ምላሽ የሚያገኘው ድምፅ በማሰባሰብ ሂደት አብላጫ ተቀባይነት ያለውን በመለየት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ አብላጫ ድምፅ ያገኘ ነገር እንደ እውነት የመቆጠር እድሉ እጅግ በጣም ሰፊ ነው::

ይሄ ሶስተኛው የእውነታ ማረጋገጫ መንገድ ጓደኞችህ በደፈናው የነገሩህ መሆኑ ነው፡፡ ነገር ግን አብዛኛው ሰው በደፈናው የተስማማበት ነገር «እውነት ምንድነው» ለሚለው ጥያቄ ትክክለኛ ምላሽ ሰጪ አይሆንም፡፡ የዚያኑ ያህል የተሟላ ምላሽም ሊሆን አይችልም፡፡

እውነትን መግለጽ ቀላል ነገር ነው:: የሚነገረንን እውነት ይሁን አይሁን ለይቶ ማውቁ የበለጠ ከብዶ ይገኛል፡፡ ከእነዚህ ሁሉ በላይ ደግሞ የራስን እውነት ለሌሎች ለማስረዳት መሞከር ዋነኛው አዳጋች ጉዳይ ነው፡፡

@Zephilosophy
@Zephilosophy
3.0K views12:17
ክፈት / አስተያየት ይስጡ