2023-03-05 09:46:03
ለአብሮነት በእጅጉ የሚጎረብጥ፤ የመርጦ አልቃሽ ሲኖዶስና ተከታዮቹ ገመና!
የሳምንቱ የአዲስ አበባ ገፅታ የመርጦ አልቃሾችን እውነታ ይበልጥ በግልፅ ያሳየ ነው፡፡ በአንድ በኩል የዓድዋን በዓል አስመልክቶ የታየው የይገባኛል ግርግርና ለቅሶ፤ በሌላ በኩል አቶ አብርሃምና ኣቶ ጴጥሮስ የሰጡት የኢትዮጵያው ሲኖዶስ መግለጫ፤ የአገሪቱ ገፅታ ምን ያህል እንደወረደና የሕዝቦች አብሮነት ይበልጥ የተናጋ አፍራሽ ሓዲድ ላይ እየተንከባለለ መሆኑን ግልጥልጥ አድርጎ ያሳየ ትእይንት ነበር፡፡
የዓድዋ በዓል ቀዳሚ ተጠሪዎች ተጋሩ እንደሌሉ በመቁጠር፤ በይገባኛል የታሪክ ሽሚያ የሰከሩ የአገሪቱ ፖለቲከኞችና ልሂቃን በተራ የፈጠራ ታሪክ ተውኔት ገፀባሕሪ ተላብሰው ሲራኮቱ የሰነበቱበት ገፅታ፤ ማንነታቸውን እርቃኑን አውጥቶታል፡፡ የዓድዋን በዓል ከሕዝባዊ በዓልነት አውጥቶ ፖለቲካ ያደረገው የአብይ አገዛዝ፤ የስልታዊ ስትራተጂካዊ የንግስና ጉዞው ቀጣይነት፤ ግጭቶችን በመፍጠር በመምራት በመቆጣጠር፤ ለአገሪቱ ሕዝቦች የግጭት አጀንዳ እየሰጠ በስጋት ውስጥ በማጎር፤ የመፍትሔ ነብይ ሆኖ የመታየት አካሄዱን ያስመሰከረበት ሂደትም ነበር፡፡
ዘንድሮ እንደታየው ልሙጥ ባንዲራ ያዛቹህ፣ የምኒሊክ ስዕል ያለበት ቲ-ሸርት ለበሳችሁ፤ በሚል ክልከላና እንግልት ግድያ ድረስ የሄደ እርምጃ ተወስዷል፡፡ ለበዓሉ የምኒሊክ ሃውልት ባለበትና ጊዮርግስ ቤተክርስትያን በሚገኝበት ኣካባቢ በተገኘ ሕዝብ ላይ አስለቃሽ ቦምብ፣ ዱላና ጥይትም በመጠቀም ለመበተን ተሞክሯል፡፡ ለዚህም ጩኸቱ ተበራክቷል፡፡
ዘንድሮ ይህንን የአብይን አካሄድ በመቃወም በመጮህ፣ በማልቀስ፣ በሚዲያ ግርግር ላይ የተሰማራው መንጋ በሙሉ፤ በእነዚያ በረገሟቸው 27 «የጨለማ» ዓመታት ውስጥ እንዳሻቸው ልሙጥ ባንዲራ ሲጠቀሙ፣ ባለኮከቡን ባንዲራ ሲቀዱና ሲያቃጥሉ የኖሩ፣ የዓድዋ በዓል ሕዝባዊነቱ እንደተጠበቀ ሆኖ በተለያየ መንገድ በፈለጉበት አገባብና አካባቢ ሲያከብሩ የነበሩ ናቸው፡፡ አሁን እውነተኛው ባህሪው ተገልፆላቸው፤ «ግራዝያኒ» ብለው እየጠሩት ያለውን አብይ አህመድን፤ «እውነተኛ ኢትዮጵያዊ፣ የአንድነት ሃይል፣ የኢትዮጽያ የለውጥ መሪ፣ ነብይ መጣልን» እያሉ እያንቆለጳጰሱ፤ «የኢትዮጵያን ታሪክ አጉልቶ ያደሰ ሙሴ» አሳክለው የሳሉ ናቸው፡፡
ትናንትና በትግራይ ህዝብ ላይ የጆኖሳይድ ጥቃት ሲፈፅም አዝማች ዘማች አጨብጫቢ ሁነው፤ «ግፋ በለው» እያሉ፤ በአውሮፕላን በድሮን በመድፍ በጥይት መግደል አላረካም ሲላቸው፤ ትግራዋይ መሆንን እንደ ወንጀል ቆጥረው፤ የፊጢኝ አስረው ጎርፍ እንዲወስደው በየጅረቱ የወረወሩ፣ ከእነህይወቱ አስረው ገደል አፋፍ ወስደው የገፈተሩ ናቸው፡፡ ይህም አላረካ ብሏቸው ከእነህይወቱ በእሳት እንዲቃጠል ያደረጉና በአድራጎታቸው እርካታቸውን ለመግለፅ በቪዶ እየቀረፁ በዩቲዩብ በመልቀቅ የትግራይን ሕዝብ በማንነቱ ለማሸማቀቅ የጣሩ ናቸው፡፡ መረን የለሹ የግፍ ግፋቸው፤ የሰውን ልጅ እንደእንሰሳ አርደው ጭንቅላቱን በእንጨት ላይ ሰክተው በሽለላና ፉከራ ለትርኢት ያቀረቡ ናቸው፡፡
በመላው ትግራይ እያንዳንዱ ቤተሰብ እንዲያለቅስ ውስጡ እንዲደማ አድርገውታል፡፡ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት፣ የአማራ ልዩ ሃይልና ፋኖ፣ ከባእዳን የኤርትራና የሱማሊያ ወታደሮች ጋር አብረው፤ በቡዱን እየተፈራረቁ፤ «ዘር ለማፅዳት» በመቶ ሺዎች የትግራይን እናቶች፣ ልጃገረዶች፣ ህፃናት፣ መነኮሳትና የቄስ የሓጂ ሚስቶችን ሳይቀር አምፀው ደፍረዋል፡፡ ይህም አልበቃ ብሏቸው፤ «ማህፀናችሁ ዘር እንዳይተካ» በሚል ፍፁም አረመኔነት፤ ማሕፀናቸው ውስጥ ከጋለ ብረት አንስቶ ምስማርና የተለያዩ ግዑዝ ነገሮችን አስገብተው፤ የቁም ስቅል ስቃያቸውን በማሳየት፤ የደም እንባ ያኔ ብቻም ሳይሆን እስካሁን ለወደፊትም እያነቡ ያለቅሳሉ፡፡ ከዚህም አልፎ ኤድስ ተጠቂዎችን በትግራይ ውስጥ በብዛት በማሰማራት የትግራይን ሴቶች በመድፈር የግፍ ግፍ የዘር ማጥፋት ወንጀል ፈፅመዋል፡፡
በመላ ኢትዮጵያ የሚኖሩ የትግራይ ተወላጆችን በማንታቸው በማሳሰር፣ በግፍ በማስቃየት፣ ቤት ንብረትና የባንክ ገንዘብ ሳይቀር በመዝረፍ፣ በመግደል፣ የሰው ልጅ ወገኔ በሚለው ሕዝብ ላይ ይፈፅመዋል ያደርገዋል ተብሎ የማይታሰብ ግፍ ሁሉ ፈፅመዋል፡፡ በመላው ዓለም የሚገኝ ትግራዋይ ሲያለቅስ ሲጮህ፤ አብይ ደመቀና ኢሳያስ የሚያካሂዱትን የነበረውን የጀኖሳይድ ወረራ ደግፈው ሲሳለቁ የነበሩ ናቸው፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በትግራይ ሕዝብ ላይ የተፈፀመውን የጦር ወንጀል ከግምት ውስጥ በማስገባት የጦር ወንጀል የምርመራ ቡዱን ተቋቁሞ እንዲያጣራ ሲወስን፤ «ጣልቃ ገብነትን እናወግዛለን፣ የአሜሪካ ኢምፔሪያዝም ይውደም» ብለው የደርግ ያረጀ መፈክራቸውን አቧሯውን አራግፈው ሰልፍ ጠርተው እሪ ያሉ ናቸው፡፡
አሁን በጭስ ቦምብ ተመታን ብለው የሚያለቃቅሱት፤ አብይ አሕመድንና ተባባሪዎቹን ደጋግፈው አንቆለጳጵሰው ፋሽስት ሆኖ ሕዝብን እንደሕዝብ እንዲያጠፋ ጀኖሳይድ እንዲፈፅም ያበረታቱና የተባበሩ ያስተባበሩ ናቸው፡፡ አብይ አህመድ፤ ስልጣኑን ለመጠበቅ የፈለገውን ሃይል ተጠቅሞ ዝም ሊያሰኛቸው መንቀሳቀሱ፤ ስለምን ያስለቅሳቸዋል? እንደዛ እንዲሆን የተጫወቱትን የእነሱን የላቅ ሚና ለምን አሳንሰው ሊያዩት ሞከሩ?
አቶ አብርሃምና ኣቶ ጴጥሮስ የሰጡት የሳምንቱ የኢትዮጵያው ሲኖዶስ መግለጫ
ከዓድዋ በዓል ግርግር ባሻገር በጣም ግልፅ ማንነታችውንና ምን ጊዜም በጥላቻ የተዘፈቁ መሆናቸውን ያረጋገጠው ሌላው የሰሞኑ ገፅታቸው፤ አቶ አብርሃምና አቶ ጴጥሮስ የሰጡት የሳምንቱ የኢትዮጵያው ሲኖዶስ መግለጫ ነው፡፡ የቦረና እና አካባቢው ሕዝብ ላይ የደረሰውን የድርቅና ረሓብ አደጋ ለመከላከል በቤተክርስቲያኒቱ ሙሉ ዓቅም በዓለም አቀፍ ደረጃ እርዳታ ለማሰባሰብና ለመደገፍ ያደረጉትን ተነሳሽነት እያደነቅኩ፤ መርጦ አልቃሽነታቸው ግን እጅጉኑ ከነከነኝ፡፡ የትግራይ ሕዝብ ከዚህ ጎጠኛና የዘረኝነትና የጥላቻ መለኪያዎች ሁሉ ጥግ የሆነ ሲኖዶስ ጋር አብሮ የኖረበት ዘመን የእርግማን ዘመን እንደነበር ነው የተሰማኝ፡፡ እውነተኛ ቅን ህሊና ያለው ሰው ሁሉ፤ ይህንን የሳምንቱን የእነ አብርሃምና ጴጥሮስ መግለጫ በማዳመጥ ጥግ የደረሰ አረሜኔያዊ ገመናቸውን ለማየት ይችላል፡፡
የትግራይን ሕዝብ እንደዘር ለማጥፋት ተረባርበው፤ ከሁለት ዓመታት በላይ በፍፁም ዝግ እየጨፈጨፉ፤ የዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ የለገሰውን ምግብና መድሃኒት እንኳን እንዳያገኝ ሁሉንም በሮች ዘግተው በረሓብ፣ በበሽታ በጥይት ከአንድ ሚልየን ሕዝብ በላይ ህይወት ቀጥፈዋል፡፡ የሚገደለውን ገድለው፣ የቀረውን ከቀየው አፈናቅለው ቤት ንብረቱን ዘርፈው አውድመዋል፡፡ እስከ አሁን ድረስ ከሶስት እስከ አራት ሚልየን የትግራይ ሕዝብ በትግራይ ውስጥና በሱዳን ተሰዶ እየተንከራተተ ይገኛል፡፡ አገራችን ናት ብለው በታማኝነት ያገለገሉ በሃያ ሺዎች የሚቆጠሩ የመካላከያና የአገር ደሕንነት ባልደረባ የነበሩ፤ ትግራዋይ ማነታቸው ብቻ ወንጀል ሆኖ፤ ከሁለት ዓመታት በላይ በአስከፊ እስራት ግፍና ግድያ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ይህ ሲኖዶስ ድምፁን ስለ ኦርቶዶክሳውያን የትግራይ ምእመናን ሊያሰማ አይደለም የዘር ማጥፋቱ ወረራ እንዲስፋፋና እንዲጠናከር እስከ ጦር ግንባር እየዘለቀ ቀስቃሽ አስተባባሪ ነበር፡፡..........
660 views06:46