2023-05-25 13:17:45
ዕርገት
በዚህ ዕለት የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት ሆነ።
“እናንተ የገሊላ ሰዎች ሆይ ! ወደ ሰማይ እየአያችሁ ለምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ ያረገው ኢየሱስ ከእናንተ ወደ ሰማይ ሲያርግ እንዳያችሁት እንዲሁ ዳግመኛ ይመጣል” የተባለበት ታለቅ ቀን ነውና፡፡
ዛሬ ዕርገት ነውና “አሕዛብ ኹላችሁ እጆቻችሁን አጨብጭቡ፤ በደስታ ቃልም ለእግዚአብሔር ዕልል በሉ፡፡ እግዚአብሔር በዕልልታ፣ ጌታችንም በመለከት ድምፅ ዓረገ”
እያልን ወደ ላይ ወደ ሰማያት ላረገው ለጌታችን እንዘምር ዘንድ ከእኛ ጋር የክቡር ዳዊትን ቃለ መዝሙር አምጡ፡፡
የወደቀውን አዳም ያነሣው ዘንድ ከሰማየ ሰማያት የወረደው ከድንግል ማርያም የተወለደው ዛሬ ከሰማየ ሰማያት በላይ ያረገው ነው፡፡
ነቢያት በትንቢት መነጽር ያዩት እርሱን እንጂ ሌላ አይደለም፤ ሐዋርያትም የበሉት ከእርሱ ጋር እንጂ ከሌላ ጋር አይደለም፡፡
በአባቱ ዕቅፍ የነበረው ፤ በጲላጦስ የተፈረደበትም ኢየሱስ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡
በመስቀል ላይ በሚስማር የተቸነከረው፤ በዘባነ ኪሩብ ላይ የነበረውም ክርስቶስ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡
ጻድቁ ዮሴፍ በጨርቅ የጠቀለለው እርሱ እንጂ ሌላ አይደለም፤ በእጁ መዳፍ ፍጥረታትን የያዘውም እርሱ ዛሬ ያረገው እንጂ ሌላ አይደለም፡፡
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጡቷን ያጠባችው ያዘለችው እሹሩሩ ብላ ጉንጮቹን የሳመችው እሱ ዛሬ ያረገው እንጂ ሌላ አይደለም።
በመቃብር ያደረው እርሱ እንጂ ሌላ አይደለም፤ ሱራፌል ያመሰገኑትም እርሱ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡
በአባቱ ቀኝ የተቀመጠው እርሱ እንጂ ሌላ አይደለም፤ ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋን ነስቶ ሰው የኾነውም እርሱ እንጂ ሌላ አይደለም፡፡
እግዚአብሔር በዕልልታ ዓረገ፡፡ አምላክ በመለከት ድምፅ ዓረገ፡፡
ነቢያት በትንቢት መነፅር እንዲያዩ ያደረጋቸው፣ ለሐዋሪያት ሐብተ ፈውስና ባለ ሙሉ ስልጣንን ያደረጋቸው፥
“አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ” ብሎ የነገራቸው እርሱ ዛሬ በዕልልታና በመለከት ድምፅ እየታያቸው ዓረገ፡፡
ወደ ሰማያት በዕልልታ ያረገው፣ በአባቱም ቀኝ የተቀመጠው የክብር ጌታ ነው፡፡
መላእክትና አለቆች ኃይላትም ይገዙለታል፡፡ ቁርጥ ልመናችንን የሚቀበል፣ ኃጢአታችንን የሚደመስስ፣ ሳንለምነው የልባችንን ሐሳብ የሚፈፅም እርሱ ነው፡፡
ስለርሱ ምድር ብራና ብትሆን ዛፎች ብዕር ቢሆኑ ባሕር ቀለም ብትሆን ፅፈን አንጨርሰው እንደው ዕፁብ ብቻ።
ለእርሱ ከቸር አባቱና ሕይወት ከሆነ ወመንፈስ ቅዱስ ጋር ምስጋና ስግደት አምልኮት ይገባል ለዘላለሙ አሜን።
@MENFESAWItsufoche
5.4K viewsKalkidan, 10:17