2023-08-19 10:53:10
+ የሐዲስ ኪዳን ደብረ ሲና +
አይሁድ ‘እኛ የሙሴ ደቀ መዛሙርት ነን ፤ እግዚአብሔር ሙሴን እንደተናገረው እኛ እናውቃለን ይህ ሰው ግን ከወዴት እንደሆነ አናውቅም’ ብለው ክርስቶስን ሊያቃልሉ ሞክረው ነበር፡፡
ዛሬ በደብረ ታቦር የተከናወነውን ቢያውቁ ምን ይሉ ይሆን? እነርሱ ሕጉን እንጠብቃለን ብለው የሚመኩበትና የእርሱን ሕግ እየጠቀሱ ክርስቶስን ሊነቅፉ የሚሞክሩበት ሙሴ ዛሬ በታቦር ተራራ ከጌታ ፊት በፍርሃት ቆመ፡፡ አይሁድ ይህንን ቢያዩ ምን ይሉ ይሆን? ፈሪሳውያን ሆይ ወደ ደብረ ታቦር ብቅ ብትሉ የእርሱ ደቀ መዛሙርት ነን ብላችሁ የምትመኩበት ሙሴን የክርስቶስ ደቀ መዝሙር ሆኖ ታገኙታላችሁ፡፡ የሕግ ፍጻሜ ክርስቶስ የሕጉን ተቀባይ ሙሴን ጠርቶ እያነጋገረው ነው፡፡ ሙሴም በሲና ተራራ በዛፍ ላይ ሲነድ ካየው እሳት ጋር እየተነጋገረ ነው፡፡
አይሁድ ሆይ በጌታ ፊት በትሕትና ብትቀርቡ ኖሮ የት እንደተቀበረ እንኳን የማታውቁትን ሙሴ ለማየት በታደላችሁ ነበር፡፡ የሙሴን መጻሕፍት በቃላችሁ የምታውቁ ሕግ አዋቂዎች ሆይ እናንተ ቁጭ ብላችሁ ክርስቶስ ለሦስት ትሑታን ዓሣ አጥማጆች ሙሴን እያሳያቸው ነው፡፡ ‘ኤልያስ ይመጣል’ የምትሉ ጻፎች ሆይ የክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ብትሆኑ ኖሮ ኤልያስን በታቦር ተራራ ባያችሁት ነበር፡፡ ደብረ ታቦር ብትገኙና ኤልያስን ብታዩት ኖሮ መስቀሉ ሥር ቆማችሁ ኤሎሔ ሲል ስትሰሙ ‘ኤልያስን ይጠራል ያድነው ከሆነ እናያለን’ ብላችሁ ባልሰማ ጆሮአችሁ ከፈጣሪ ጋር አትጣሉም ነበር፡፡
ደብረ ታቦር የሐዲስ ኪዳን ደብረ ሲና ሆነች፡፡ ሙሴ ሕዝቡን ከተራራ በታች ትቶ ከኢያሱና ከወንድማማቾቹ አብዩድና ናዳብ ጋር ወደ ሲና ተራራ ይወጣ እንደነበር ክርስቶስም ከጴጥሮስና ከወንድማማቾቹ ያዕቆብና ዮሐንስ ጋር ወደ ታቦር ተራራ ወጣ፡፡ ሙሴ በሲና በደመና መካከል የእግዚአብሔርን ድምፅ እንደሰማ በታቦርም የአብ ቃል ተሰማ፡፡ የታቦር ድምፅ ግን እንደ ሲና ‘ባሪያዬ ሙሴ’ የሚል ሳይሆን ‘የምወደው ልጄ’ የሚል ነበር፡፡ ሙሴ በሲና ተራራ ባየው የእግዚአብሔር ክብር ምክንያት ፊቱ እስራኤል ተሸፈንልን እስኪሉት ድረስ አበራ፡፡ የታቦር ተራራው ግን የተለየ ነበር ፤ ብርሃኑ ከውስጡ የፈለቀው ጌታ ፊቱ ከሙሴ ይልቅ አበራ በልብሱ እንዳይሸፍነው ልብሱም ብርሃን ነበረና ተማሪዎቹ ወደቁ፡፡
ታቦር እንዴት ያለች ‘እግዚአብሔር የወደዳት’ ተራራ ናት? [ደብር ዘሠምሮ እንዲል] ሐዋርያትና ነቢያት በአንድነት ቆመው የሚተያዩባት ፤ ብሉይና ሐዲስ የተዋወቁባት ፤ ጥላና አካል የተጋጠሙባት ይህች ተራራ እንዴት የተመረጠች ናት? ‘ታቦርና አርሞናዔም በስምህ ደስ ይላቸዋል’ እንደተባለ ነቢያትና ሐዋርያትን በግራ በቀኙ አድርጎ በሰማያዊ አባቱ ‘የምወደው ልጄ’ ተብሎ ሲጠራ ስሙን ሰምታ ታቦር ምንኛ ደስ ይላት ይሆን? የሰናፍጭ ቅንጣት ታህል እምነት አጣን እንጂ ነቅለን ወደ ሀገራችን ከምናስገባቸው ተራሮች አንዱ ታቦር በሆነ ነበር፡፡
በታቦር ተራራ ሐዋርያትና ነቢያት በአንድ ወንበር ከሊቀ ሊቃውንት ክርስቶስ ትምህርት ተምረው ተመለሱ፡፡ ሐዋርያቱ የነቢያት ጌታ መሆኑን ሲማሩ ነቢያቱ ደግሞ የሐዋርያት አምላክ መሆኑን አወቁ፡፡ ነቢያት ደክመው የዘሩትን ከሚያጭዱ አጫጆች ሐዋርያት ጋር ተዋወቁ፡፡
ነቢያት አምላክነቱን ያውቃሉ ፤ ሐዋርያት ደግሞ ሰውነቱን ያውቃሉ፡፡ በታቦር ተራራ ግን አዲስ ትምህርት ተማሩ፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም እንዲህ ይላል ፦ ‘‘ነቢያቱ አይተውት የማያውቁትን ሰውነቱን አይተው ተደሰቱ ፤ ሐዋርያቱ አምላክነቱን አይተው ተደሰቱ’’
ሐዋርያት ደነገጡ ፤ እነርሱ ባልነበሩበት በዮርዳኖስ የተናገረውን የእግዚአብሔር አብን ድምፅ በታቦር ተራራ ሰሙ ፤ ጴጥሮስ ‘አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ’ ያለው በሰማይ ያለው አብ ገልጦለት ነበረ ፤ አሁን በልቡ ያንን ቃል ያስቀመጠውን የአብን ድምፅ ሰምቶ ዓለቱ ስምዖን በፍርሃት ወደቀ፡፡ የጌታን ፊት አብርቶ ሲያይ ሳያይ ያመነውን አምላክነቱን አወቀ፡፡ ‘ሐዋርያት በአንድ ቀን ሁለት ፀሐይ ወጥቶ አዩ ፤ አንደኛው የተለመደችው ፀሐይ ስትሆን ሁለተኛው ደግሞ የሚያበራው የጌታ ፊት ነበር’ ይላል ቅዱስ ኤፍሬም፡፡ እውነትም ስሙን ለሚፈሩ ሐዋርያት የጽድቅ ፀሐይ ክርስቶስ በታቦር ተራራ ላይ ወጣላቸው፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም በታቦር ተራራ ነቢያትና ሐዋርያት መገናኘታቸውን እንዲህ ሲል ያደንቃል ፦
‘የብሉይ ኪዳን ጸሐፊዎች የሐዲስ ኪዳን ጸሐፊዎችን አዩ ፤ ቅዱሱ ሙሴ ቅዱስ ጴጥሮስን አየው የአብ እንደራሴ የወልድን አገልጋይ ተመለከተው፡፡ የብሉይ ኪዳኑ ድንግል ኤልያስ የሐዲስ ኪዳኑን ድንግል ዮሐንስን አየው፡፡ በእሳት ሰረገላ ላይ የተሳፈረው ኤልያስ ወደ እሳታዊው ክርስቶስ ደረት የተጠጋውን ዮሐንስን አየው፡፡ የታቦር ተራራ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ሆነ ፤ ክርስቶስም ሁለቱን ኪዳናት አዋሐዳቸው!’
ሐዋርያት ወድቀው ‘የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት’ የሚል ቃል ከሰሙ በኋላ ሲነሡ ከክርስቶስ ብቻ በቀር ማንንም አላዩም፡፡ በእርግጥም ‘የምወደው ልጄ ይህ ነው’ ተብለው ማሳሰቢያ ከተሠጣቸው በኋላ ቀና ሲሉ ማግኘት ያለባቸው ‘የሚወደው ልጁን’ ክርስቶስን ብቻ ካልሆነ አዋጁ ስለማን እንደሆነ ግራ ይገባቸው ነበር ይላል ማር ኤፍሬም፡፡
ሐዋርያት ቀና ሲሉ ሙሴ የለም ፤ ኤልያስም የለም፡፡ ለነገሩ ከሙሴም ከኤልያስም የሚልቀው ጌታ ከእነርሱ ጋር ካለ ምን ይፈልጋሉ? ባልወለደው ፈርኦን የልጅ ልጅ ተብሎ ከተጠራው ሙሴ ይልቅ ባልወለደው ዮሴፍ የዮሴፍ ልጅ ተብሎ የተጠራው ክርስቶስ ከእነርሱ ጋር ነው፡፡ ከፈርኦን ሰይፍ ተርፎ እስራኤልን ነጻ ካወጣው ሙሴ የሚበልጠው ከሔሮድስ ሰይፍ ተርፎ ዓለምን ነጻ ያወጣው ክርስቶስ ከእነርሱ ጋር አለ፡፡ እናቱ ሞግዚቱ ሆና ካሳደገችው ሙሴ በላይ ‘እናትና ገረድ ማርያም ደስ’ ብሏት ያሳደገችው ክርስቶስ አይሻላቸውም? ግብፃዊውን ገድሎ ለማንም አትናገሩ ከሚለው ሙሴ ይልቅ ዕውራንን አብርቶ ለምፃምን አንጽቶ ፊቱ እንደ ፀሐይ አብርቶ ለማንም አትናገሩብኝ የሚለው ክርስቶስ አብሮአቸው ካለ ምን ይፈልጋሉ፡፡ ‘የቆምህበት ሥፍራ የተቀደሰች ናትና ጫማህን ከእግርህ አውልቅ’ ተብሎ ከተነገረው ሙሴ ይልቅ ‘የጌታ እግር በሚቆምበት እንሰግዳለን’ ‘የጫማህን ጠፍር እንኳን ልፈታ አይገባኝም’ እየተባለ የተዘመረለት ክርስቶስ ከእነርሱ ጋር ነውና ለሦስቱ ደቀ መዛሙርት የሙሴ መሔድ አላስደነቃቸውም፡፡
ኤልያስንም ስላላዩ አላዘኑም ፤ በእሳት ሰረገላ ከሔደው ኤልያስ በላይ ልብሱ እሳት ቀሚሱ እሳት የሆነው አምላክ ከእነርሱ ጋር ነው፡፡ ኤልያስ ለደቀ መዝሙሩ ወደ ሰማይ ሲሔድ መጎናጸፊያውን ትቶለት ሔዶ ነበር፡፡ የሐዋርያት መምህር ክርስቶስ ግን ሲያርግ ልብሱን አልወረወረላቸውም፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳለ እርሱ ሲያርግ ለደቀ መዛሙርቱ የተወላቸው ልብሱን ሳይሆን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ነው፡፡ ስለዚህ ኤልያስ ቢሔድ ሙሴም ቢሰወር ደቀ መዛሙርቱ ጌታችንን ከብበው ከታቦር ተራራ በደስታ ወረዱ፡፡
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ነሐሴ 13 2012 ዓ.ም
አዲስ አበባ : ኢትዮጵያ
ፎቶ : ጴጥሮስ "ሦስት ዳስ እንሥራ" ያለበት ምኞቱ ቆይቶ ተሳክቶ በአሁኑ ሰዓት በታቦር ተራራ ሦስት ቤተ መቅደሶች ያሉ ሲሆን የመካከለኛው የጌታ ግራና ቀኙ ደግሞ የሙሴና የኤልያስ ናቸው:: የምትመለከቱት ፎቶ ከሦስቱ ዳስ በአንዱ በሙሴ ዳስ ውስጥ የተነሣሁት ነው::
18.6K views , 07:53