2022-03-04 08:20:49
ቢያዎች
አቋቁመው በየዓመቱ በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ
ችግኞች በየአብያተ ክርስቲያናቱ ሰበካና
ለሕዝባውያን ድርጅቶች እንዲከፋፈሉ
በማድረጋቸው የተራቆቱ መሬቶች በዛፎች
እንዲዋቡ ጥረዋል፡፡
መ/ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት
በማስፈቀድ በማኅደረ ማርያም የሐዲሳት፣
የድጓና የቅዳሴ ት/ቤት አሠርተው ለመምህራኑ
ከ50 እስከ 200 ብር ደመወዝ እንዲከፈላቸው፣
ለደቀ መዛሙርቱ ድጎማ እንዲሰጣቸው
አድርገዋል፡፡
ሠ/ ጥንታዊውንና ታሪካዊውን የጣና ቂርቆስ
ገዳም በብር 8ሺሕ835 እንዲታደስ አድርገዋል፡፡
በጣና ለሬማ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ብር
4ሺሕ ረድተዋል፡፡ የደረሞ ቅዱስ ሚካኤልን ቤተ
ክርስቲያን ብር 21ሺሕ 114 በማውጣት
አሳድሰዋል፡፡ እንዲሁም ጥንታዊውን የግርቢ
ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በብር 8ሺሕ860 ብር
እንዲታደስ አድርገዋል፡፡ በአዘዞ በሰሚ ቅዱስ
ሚካኤል ወደ ካህናቱ ማሠልጠኛ የሚወስደው
መንገድ በምግብ ለሥራ መርሐ ግብር እንዲሠራ
አድርገዋል፡፡
በጎንደር መንበረ መንግሥት ጥበበ እድና የአዳሪ
ቤቱ ዙሪያ ርዳታ በመጠየቅ ከ9ሺሕ በላይ
በማወጣት እንዲሠራ አድርገዋል፡፡ በጎንደር
ጉባኤ ቤትና የዶክተር አየለ ዓለሙ የመቃብር
ቤት የአራቱ ጉባኤያት ሥዕል እንዲሠራበት
አድርገዋል፡፡ በሊቦ አውራጃ በቆላ እብናት
ለአምራቾች የኅብረት ሥራ ማኅበር ብር 15 ሺሕ
ረድተዋል፡፡ በጎንደር ከተማ በአዘዞ አባ ሳሙኤል
በመጠለያ ለሚረዱ ከልማትና ክርስቲያናዊ
ተራድኦ መምሪያ ጋራ በመተባበር የኤልክትሪክ
ምጣድ ርዳታ አድርገዋል፡፡ በዳባት ወረዳ
የሚገኘውን የደፍቂ ቅዱስ ሚካኤልን በብር
5ሺሕ፣ ቆማ ፋሲለደስን በብር 5ሺሕ
አሳድሰዋል፡፡ ለአምስትያ ገዳም ብር 4ሺሕ፣
ለጣርክ ማርያም ብር 7ሺሕ ረድተዋል፡፡
ዐደባባይ ኢየሱስም በብር 40ሺሕ እንዲታደስ
አድርገዋል፤ የድምፅ ማጉያም አስገብተውለታል፡፡
በጎንደር ዙሪያ አውራጃ ለቸንከር ተክለ ሃይማኖት
ርዳታ በመጠየቅ ብር 764ሺሕ አበርክተዋል፡፡
በዚያው በጎንደር ዙሪያ ከማክሰኝት እስከ አርባያ
ለመንገድ ሥራ ብር 30ሺሕ ርዳታ እንዲገኝ
አድርገዋል፡፡ ከእብናት እስከ ጎሐላ ለመንገድ
ሥራ የብር 6ሺሕ ርዳታ እንዲገኝ አድርገዋል፡፡
በስሜን አውራጃ ለሚገኙ ጥንታውያን ገዳማት፤
ለቤተ ሚናስ ዋልድባ ከብር 10ሺሕ በላይ፤
ለጣዕመ ክርስቶስ ብር 10ሺሕ፣ ለሰቋር ዋልድባ
ብር 4ሺሕ ግምት ያላቸው የቁሳቁስ(የዓይነት)
ርዳታ አድርገዋል፡፡
በጎርጎራ ገዳም በደሴተ ጣና ለሚገኙ ገዳማት፤
ለማን እንዳባ ገዳም ብር 1ሺሕ880፤ ለብርጊዳ
ማርያም ገዳም ብር 1ሺሕ ለበሬ መግዣ
እንዲሰጥ አድርገዋል፡፡
ከልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ መምሪያ ርዳታ
ሰጪ ድርጀቶች በመጠየቅ አቅም በፈቀደ መጠን
በተወሰኑ አብያተ ክርስቲያናት የቆዳ፣ የሽመና፣
የሹራብ ሥራ፣ የልብስ ስፌት፣ የወፍጮ ቤትና
የዳቦ ቤት እንዲቋቋምና አገልግሎት እንዲሰጡ
አድርገዋል፡፡ በተጨማሪም ለስብከተ ወንጌል፣
ለሰንበት ት/ቤትና ለሕዝብም መሰብሰቢያ
የሚያገለግሉ አዳራሾች በየአብያተ ክርስቲያናቱ
አካባቢ አሠርተዋል፡፡ ሕዝቡ ንጹሕ ውኃ ማግኘት
እንዲችል የውኃ ጉድጓድ በማስቆፈር ለዚሁ
የሚያገለግል ሞተርና ቧምቧ እንዲያገኙ
የበኩላቸውን ጥረዋል፡፡
ለሀገረ ስብከቱ ያስገኟቸው ሽልማቶች ፤
የሰበካ ጉባኤ ቃለ ዐዋዲ ደንብ በትክክል
እንዲፈጸም በማድረጋቸውና ሰበካ ጉባኤን
በሚገባ በማደራጀታቸው፣ በየዓመቱ በሚደረገው
የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ
ዓመታዊ ስብሰባ የሥራ ግምገማ በተደረሰበት
ውጤት የጎንደር ሀገረ ስብከት ቅድሚያ ቦታ
እንዲይዝ አድርገዋል፡፡
በዚህም መሠረት፡- ከ16ቱ አህጉረ ስብከት፣
ከ1975 እስከ 1977 ዓ.ም. በተከታታይ እንዲሁም
በ1979 ዓ.ም. አንደኛ፤ በ1978 ዓ.ም. ኹለተኛ
በመኾን በውጤታማነት እንዲሸለም አድርገዋል፡፡
ብፁዕነታቸው፣ ከዚህ በላይ ጠቅለል ባለ መልክ
በተዘረዘረው ዓይነት ተልእኳቸውን በትክክል
የተወጡ አባት ከመኾናቸውም በላይ በ1979
ዓ.ም. በተደረገው የብሔራዊ ሸንጎ አባላት
ምርጫ በጎንደር ዙሪያ አውራጃ ምርጫ ጣቢያ
ደንቢያ ከመረጠው 26ሺሕ127 ሕዝብ መካከል
17ሺሕ249 ድምፅ በማግኘት ተመርጠው
ሕዝብን አገልግለዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስ፣ የበላዮቻቸውን መካሪ፣
የበታቾቻቸውን አክባሪ፣ በሥራ ታታሪ፣ መንፈሳዊ
አባትነታቸውና ትሑት ሰብእናቸው አርኣያነት
ያለው ቁጥብ አባት ናቸው፡፡
ለፕትርክና በከፍተኛ ድምፅ የተመረጡበት ኹኔታ ፤
ብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስ፣ ለ11 ዓመታት ያህል
በመጀመሪያ በኦጋዴን አውራጃ ኤጲስ ቆጶስ
ቀጥሎም በጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
በመኾንና በቅዱስ ሲኖዶስ አባልነት
አገልግለዋል፡፡ ለፕትርክና ምርጫው በተዘጋጀው
ደንብ አንቀጽ 2 መሠረት፡- የትምህርት
ዝግጅታቸው፣ ገዳማዊ ሕይወታቸው፣ የአስተዳደር
ችሎታቸው፣ የመንፈሳዊና ማኅበራዊ
አገልግሎታቸው፣ ሥነ ምግባራቸው ተመዝኖ
ብቃትና አርኣያነት ያላቸው አባት ኾነው
በመገኘታቸው በዕጩነት ተመርጠዋል፡፡
የመራጭ አባላት ቁጥር፤
በምርጫው ደንብ መሠረት፣ 32 የቅዱስ ሲኖዶስ
አባላት፣ 7 የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ
የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት፣ 48 የአህጉረ
ስብከት ሰበካ ጉባኤያት ሥራ አስፈጻሚ
ኮሚቴዎች ተወካዮች፣ 22 የቀደምት የአንድነት
ገዳማትና ታላላቅ አድባራት ተወካዮች በድምሩ
109 መራጮች ነሐሴ 22 ቀን 1980 ዓ.ም.
በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ተገኝተው
ድምፅ ሰጥተዋል፡፡
በዕጩነት ከቀረቡት ሦስት ሊቃነ ጳጳሳት መካከል፣
ብፁዕ አቡነ መርቆሬዎስ፣ 66 ከፍተኛ ድምፅ
በማግኘት፣ 4ኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ
ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ኾነው ለመመረጥ
በቅተዋል፡፡ ሢመተ ፕትርክናቸው ነሐሴ 29 ቀን
1980 ዓ.ም. የተፈጸመ ሲኾን፣ 4ኛ ፓትርያርክ
በመኾን ቃለ መሐላ ፈጽመዋል፡፡ በፖሊቲካዊ
ግፊትና ጫና መንበራቸውን እስከለቀቁበት፣
ነሐሴ 28 ቀን 1983 ዓ.ም. ድረስም፣ ለሦስት
ዓመታት ለቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ አባታዊ
አመራር ሰጥተዋል፡፡
196 viewsbisrat, 05:20