2022-09-01 10:23:21
አሜሪካ ምን ነክቷት ነው?
ኢትዮጵያውያን ለአሜሪካ ያላቸው እይታ መልካም ነበር። ኢትዮጵያውያን የአሜሪካውያንን የመንግስት ስርዓታቸውን ያደንቃሉ። ፊልማቸውን ይወዳሉ። ኢትዮጵያ ውስጥ ካፌና ሆቴል እንኳን በአሜሪካ ከተሞች ስም ነው የሚጠራው። ከሳዳም ጋር ያደረጉትን ጦርነት ወቅት የገጠር ከተማ እየተምርኩ ነበር። ያኔ ቴሌቪዥን በየቤቱ አልነበረም። ሻይ ቤት ሄደን ነበር የምናየው። ያን ጦርነት ታዲያ እንደ እግር ኳስ ነበር የምንመለከተው። ቀጥታ ስርጭት አይደለም። ምሽት ላይ ከየቦታው የመጣው በርካታ ሰው ወንበር አጥቶ ቆሞ ይመለከታል። ጋዜጠኛው አሜሪካ ድል እየቀናት እንደሆነ ሲናገር የሚደግፈው ቡድን ጎል እንዳገባ ወጣቱ ይጨፍራል። በለው ይላል። ያ ወጣት የአሜሪካን ፖሊሲ በደንብ ባያውቅም ተፅዕኖው ግን ነበር። ቀደም ሲል የነበረው መልካም ግንኙነት ገጠር ሳይቀር ደርሷል። የኢትዮጵያን ሕዝብ ግራ ዘመሙ ትውልድ እንኳን ስለ አሜሪካ የከፋ አቋም ያስያዘው አይመስልም።
ዩኒቨርሲቲ ሲሻሊዝም እየተማርንም፣ አሜሪካ የምታደርጋቸውን እያወቅንም አሜሪካን የሶሻሊስቶቹ ጀብደኞች እንድንጠላት አላደረጉንም ነበር። የኦባማ ምርጫ ኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት ቀጥታ ስርጭቱ ታይቷል። ኢትዮጵያውያን የመኪናቸውን ስም ሳይቀር ኦባማ ብለው ቀይረውታል። ጥቁር ስለሆነ ብቻ አይደለም። ኢትዮጵያውያን የጥቁሩ ዓለም ግንባር ቀደም አርበኛ እንደሆኑ ያውቃሉ። የአሜሪካ እሴት ነው የሚሉትንም ስለሚያደንቁ ነው።
አሜሪካ በጦርነት እንዴት አንድነቷን እንደጠበቀች ስለሚታወቅ ኢትዮጵያውያን ሞዴል ያደርጓታል። ብዙ ኢትዮጵያውያን የተስፋ ምድር አድርገው ይመለከቷት ነበር። ደሕና ገንዘብ ስለሚሰሩባት ብቻ ግን አይደለም። ሴራም ይኑረው፣ ለጥቅሟ የፈለገችውንም ታድርግ አሜሪካ የምትከበርባቸው እሴቶች ነበሩ። የአገር አንድነት ላይ አደጋ የደቀነን አሸባሪ በዚህ ደረጃ ወርዳ ትደግፋለች ብሎ መገመት ከባድ ኖሯል።
ያች ጦርነቷን እንደ እግር ኳስ በምሽት ሌላ ቦታ አይተን "በይው አሜሪካ!" ያልናት አገር የአሸባሪው ትህነግ ተራ አክቲቪስት ስትሆን እንደማየት የሚገርም ነገር የለም።
ዛሬ የተፈጠረው እንደዚህ ነው። የትህነግ ሰዎች በጌታቸው በኩል ጦርነት ተከፈተብን ከማለታቸው በፊት ይደግፉናል ወዳሏቸው ሰዎች ሪፖርት አደረጉ። ባለፉት ሳምንታት ትህነግ ወረራ ሲፈፅምብን ምንም ያላሉት የአሜሪካ ሰዎች፣ ትናንት ጀምሮ ትህነግ ሪፖርት ባደረገላቸው መሰረት መጀመርያ እነሱ ለይምሰል ጦርነት ይቁም ወዘተ አሉ። ከእነ አሜሪካ ቀጥለው እነ ጌታቸው ረዳ ዛሬ ጠዋት ተወረርን አሉ። ተመጋጋቢ ነው። የአሜሪካ ኤምባሲ የለጠፈውና ጌታቸው ረዳ የለጠፈው ልዩነታቸው የደቂቃ ነው። እነ ጌታቸው መጀመርያ አሜሪካኖቹ ቢለጥፉት ይሻላል ብለው፣ የአሜሪካኖቹን ተቀጥለው ነው ተወረርን የሚሉት።
አሜሪካ የኢትዮጵያውያንን ድጋፏን እንዲህ አፈር ድሜ አብልታ ለአንድ ጎሬ ውስጥ ለመደበቅ የሚዘጋጅን አሸባሪ የምትደግፈው ምን እያሰበች ነው? እንዴት እያሰበች ነው? ፖለቲካ ይወቅ አይወቅ በዚህ ወቅት አሜሪካ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ጉዳይ አሉታዊ አስተዋፅኦ እያደረገች ነው ብሎ የሚያስበው ሰው ብዙ ነው። አሜሪካ ግን ምን ነክቷት ነው?
20.6K views07:23