2023-05-20 23:42:22
መስጂዶች ህልውናችን ናቸው!
በሀገራችን ኢትዮጵያዊ የተገነቡ መስጂዶችን ታሪክ ስናይ አብዛኛው ብዙ መስዋትነት ተከፍሎባቸው የተገኙ ናቸው::
ሙስሊሞች እና መስጂድ የማይነጣጠሉ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታዎች ናቸው:: አሳ ያለ ውሃ እንደማይኖረው ሁሉ ሙስሊሞችም ያለሰላት እና ያለመስጂድ መኖር አይቻላቸውም::
መስጂዶች ለሙስሊሙ ከአምላኩ ጋር የሚገናኝባቸው የአምልኮ ቤቶች ብቻ ሳይሆኑ ሀይማኖቱን እና ስ-ነምግባሩን የመማሪያ፣ የመወያያ፣ እና አንድነቱን የሚያጠናክርባቸው መድረኮች ናቸው::
ቀደምት አባቶቻችን በብዙ መስዋትነት ያስረከቡን ሆነ አሁን ላይ በገንዘቡ፣በላቡ እና በደሙ የመሰረታቸውን መስጂዶች ማፍረስ እና ማጥቃት የሙስሊሙን ህልውና የሚፈታተን ተግባር ነው::
በሸገር ሲቲ ተባብሶ የቀጠለው መስጂዶቻችንን የማፍረስ ተግባር በአስቸካይ ይቆም ዘንድ ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡
የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት (መጅሊስ) እንደ ተቋም በአዋጅ ህጋዊ ሰውነት አግኝቶ የተቋም ግንባታውን የጠነከረ አለት ላይ ለማሳረፍ ሰፊ ስራዎችን እየሰራ ባለበት በዚህ ወቅት የህዝበ ሙስሊሙን ህልውና የሆኑ ተቋማት ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን በቸልታ የሚያልፋቸው አይደሉም::
አዲሱ የመጅሊሱ አመራር እንደ ግለሰብ ወደ ተቋሙ ከመምጣታቸውም በፊት ከማንም በፊት መስጂዶችን በማስገንባት፣ ለመስጂዶች እና በአጠቃላይ ለዲኑ መከበር ዘብ በመቆም ብዙ መስዋትነትን የከፈሉ አባቶች ናቸው::
ትላንት ተሰሚነት ያለው የሙስሊሙ ወኪል እንዲኖር ብዙ ሲለፋ የነበረ አመራር ዛሬ ላይ የሙስሊሙ ወኪል የሆነውን መጅሊስ በሃላፊነት እንዲመራ ሲደረግ የሙስሊሙን ቁስል እና ህልውናን አደጋ ላይ የሚጥል ድርጊት ሲፈፀም ችላ ሊል ይችላል ብሎ ማሰብ ተገቢ አይደለም::
በተቋም ደረጃ የሚሰሩ ስራዎች ተቋማዊ አሰራራቸውን በጠበቀ መልኩ እርከናቸውን እና ስርዓታቸውን ጠብቀው እየተሰሩ ይገኛሉ::
ለአፍታም ቢሆን የሙስሊሙን ህልውናን የሚፈታተኑ ተግባራትን በዝምታ እና በቸልታ የሚያልፍ አመራር አለመኖሩን አስረግጬ ለማሳሰብ እወዳለሁ::
ይህ ከመሆኑም ጋር የተቋም ግንባታ በአንድ ጀንበር የሚጠናቀቅ አይደለም:: ይህን ለማሳካት አመራሩ ብቻውን የሚወጣው አይደለም:: ህዝበ ሙስሊሙ ተቋሙን ከጎኑ በመሆን በሚፈልገው ቁመና እና ልክ ከፍ ብሎ እንዲወጣ ሁሉም ተቋሜ ብሎ ድጋፍ ማድረግ ይኖርበታል::
መጅሊሱ እንደ ተቋም የመስጂዶችን ህልውና ለመታደግ ብቻ ሳይሆን ህዝበ ሙስሊሙ በሚገባው ልክ የአምልኮ ቦታዎች እንዲሰጡት ማድረግ ግዴታው ነው:: የሙስሊሙን ህልውና የሚፈታተኑ ዘመናትን ያሳለፉ የአስተሳሰብ እና መዋቅራዊ ችግሮችን ለማስተካከል የራስን ተቋም በማጠናከር ስር ነቀል ለውጥ ለመምጣት በጋራ መልፋትም ያስፈልጋል ::
በሀገራችን የትኛውንም የፓለቲካ መስመር የሚከተል አመራር የሀገሪቱ ግማሽ የሆነውን ህዝበ ሙስሊም ባከበረ እና ታሳቢ ባደረገ መልኩ መንቀሳቀስ ካልቻለ አድሏዊ አሰራርን፣ ጭቆናን እና መገፋትን አሜን ብሎ የሚቀበል ትውልድ አለመኖሩን ማስታወስ ያስፈልጋል::
ህዝበ ሙስሊሙ እንደ ዜጋ በሀገሪቱ ላይ እኩል ባለድርሻ መሆኑን በማወቅ የሚወጡ ህጎችም፣ ፖሊሲዎችም ሆነ የልማት እቅዶች ይህን መርህ ታሳቢ ያደረጉ መሆን ይኖርባቸዋል::
መስጂዶችን በህገወጥነት ስም በማፍረስ እና በማጥፋት ሙስሊሙን በመግፋት የሚመጣ ልማትም ሆነ እድገት ሊኖር አይችልም:: ሁሉንም የሀገሪቱ ህዝቦች በእኩልነት እና በፍትህ ያማከሉ የልማት እቅዶች ውጤታቸውም ለሁሉም በእኩልነት እና በፍትሃዊነት ተጠቃሚ ማድረጉ አይቀርም::
ሙስሊሙ ማህበረሰብ የህልውናው መሰረቱ በሆኑት መስጂዶቹ ላይ የተቃጣውን ጥቃት ከመሪ ድርጅቱ እና ከኡለማዎቹ ጎን በመቆም እና መሪውን በማድመጥ የመስጂዶቹ ዘብ መሆን ይጠበቅበታል::
ጠንካራ ተቋም ሲኖር ተሰሚነትም ይጨምራል:: ይህን ተሰሚነት ለማሳደግም የተቋሙ ባለቤት የሆነው ህዝበ ሙስሊም ተቋሙን በማጠናከር፣ በመምከር እና በማገዝ ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ ለማሳሰብ እወዳለሁ::
አላህ ሱወ ይርዳን
አገራችንን ሠላም ያድርግልን
ኡስታዝ አቡበከር አህመድ
813 views20:42