2022-06-29 21:44:46
ዙል ሂጃ
10 የዙል ሂጃ ቀኖች
ዙል-ሒጃህ በእስልምና ወር አቆጣጠር አስራ
ሁለተኛው (የመጨረሻው) ወር ነው፡፡ በዚህ ወር
ውስጥ ካሉት 29/30 ቀናት ውስጥ የመጀመሪያዎቹ
አስር ቀናት እጅግ የተከበሩ ቀናቶች ናቸው፡፡
መከበራቸውን ከሚያመላክቱት ውስጥ፡-
ሀ. አላህ የማለባቸው መሆኑ፡-
"በጎህ እምላለሁ። በዐሥር ሌሊቶችም።" ሱረቱል
ፈጅር 1-2
ታላቅ የሆነው ጌታችን አላህ የሚምለውም ታላቅ
በሆነ ነገር ስለሆነ የቀኑን ክብደት ይገልጽልናል፡፡
እነዚህ አስር ሌሊቶች የተባሉት የዙል-ሒጃ
የመጀመሪያዎቹ አስር ቀናት እንደሆኑ አብዝሓኞቹ
የቅዱስ ቁርኣን ተንታኞች ይገልጻሉ፡፡
ለ. እኔን አስታውሱባቸው ማለቱ፡-
" ለነሱ የሆኑ ጥቅሞችን ይጣዱ ዘንድ፣ በታወቁ
ቀኖችም ውስጥ ከማለዳ እንሰሳዎች በሰጣቸው
ሲሳይ ላይ የአላህን ስም ያወሱ ዘንድ፣ (ይመጡሃል)፤
ከርሷም ብሉ፤ ችግረኛ ድኻንም አብሉ።" ሱረቱል-ሐጅ
28
"የታወቁ ቀኖች" የተባሉት እነዚሁ አስርቱ ቀናት
እንደሆኑ ሙፈሲሮች ያስረዳሉ፡፡ ታዲያ አላህን
በማንኛውም ጊዜ ማውሳትና ማወደስ ከመቻሉ ጋር፡
በነዚህ ቀኖች አወድሱት ብሎ ቀኖቹን ለይቶ
መጥቀሱ የተለየ ደረጃና ክብር እንዳላቸው
ይጠቁማል፡፡
ሐ. ከዱንያ ቀናት ሁሉ በላጭ መሆናቸው፡-
ከጃቢር ኢብኒ ዐብዲላህ (ረዲየላሁ ዐንሁ)
በተላለፈው ሐዲሥ ረሱላችን (ሰለላሁ ዐለይሂ
ወሰለም) እንዲህ ብለዋል፡-" ከዱንያ ቀናቶች ሁሉ
በላጩ (የዙል-ሒጃ) አስሩ ቀናት ናቸው " (ሶሒሕ አል-
ጃሚዑ ሰጊር 1133)፡፡
በዚህ መሰረት እነዚህ አስርት ቀናቶች ልዩ ክብር
የሚሰጣቸው ናቸው፡፡
ምን እንሥራባቸው?
ዐብደላ ኢብኑ አባስ እንዳስተላለፉት የአላህ
መልክተኛ (ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) እንዲህ
ብለዋል፡- "መልካም ስራ ከዙል-ሒጃ አስርቱ ቀናት
በልጦ አላህ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነበት ቀናት
የለም፡፡" ሶሓባዎችም፡- በአላህ መንገድ ጂሐድም
(ጠላትን መታገልም) ቢሆን? ሲሉ፡ እሳቸውም፡- አዎ
ጂሐድም ቢሆን ሰውየው ከነፍሱና ከንብረቱ ጋር
በዛው ሳይመለስ የቀረ ካልሆነ በስተቀር
አይበልጥም" አሉ፡፡ (ቡኻሪይ)፡፡
ታዲያ ያለምንም የመግቢያ ክፍያ እንዲህ ዐይነት
ታላቅ ኤግዚቢሽን ከተዘጋጀልን እኛስ ለመሳተፍ ምን
ያህል ወስነናል፡፡ ጠላታችን ሰይጣን እንዳንጠቀምበት
ደፋ ቀና ማለቱ አይቀርምና እኛም አላህን ይዘን እሱን
ድል በመምታት ቀኑን እንጠቀምበት፡፡ ከሚሰሩ
መልካም ሥራዎች ውስጥ፡-
1. ሐጅና ዑምራህ፡-
" ዑምራህ መፈጸም ቀጣዩ አመት ዑምራ እስኪመጣ
ድረስ (በመሐል ለተፈጸሙ ጥቃቅን ኃጢአት)
ማስተሰረያ ነው፣ ትክክለኛ ሐጅ ደግሞ ከጀነት ውጪ
ክፍያ የለውም" ቡኻሪና ሙስሊም፡፡
2. ጾም፡-
የፈለገ ሙሉውን ዘጠኝ ቀን ካልሆነም የቻለውን
ያክል መጾም ይችላል፡፡ ዐብደላህ ኢብኑ አባስ
(ረዲየላሁ ዐንሁማ) እንዳስተላለፉት የአላህ
መልክተኛ (ሰለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) እንዲህ
ብለዋል፡- "መልካም ስራ ከዙል-ሒጃ አስርቱ ቀናት
በልጦ አላህ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ የሆነበት ቀናት
የለም፡፡" በዚህ ሐዲሥ መሰረት ጾም "መልካም ስራ"
የተባለው ሐዲሥ ውስጥ ስለሚካተት በጾሙ
የቻለውን ያክል መበርታት ይችላል፡፡
3. አላህን ማውሳት፡-
" ለነሱ የሆኑ ጥቅሞችን ይጣዱ ዘንድ፣ በታወቁ
ቀኖችም ውስጥ ከማለዳ እንሰሳዎች በሰጣቸው
ሲሳይ ላይ የአላህን ስም ያወሱ ዘንድ፣ (ይመጡሃል)፤
ከርሷም ብሉ፤ ችግረኛ ድኻንም አብሉ።" ሱረቱል-ሐጅ
28
ይህ ቅዱስ አንቀጽ አላህን በነዚህ ቀናት ማውሳት
መዘከር እንዳለብን ይነግረናል፡፡ ዐብደላህ ኢብኑ
ዑመር (ረዲየላሁ ዐንሁማ) ባስተላለፉት ሐዲሥ ላይ
ነቢዩ (ዐለይሂ-ሶላቱ ወስ-ሰላም) እንዲህ ብለዋል፡-
"በነዚህ ቀናት ውስጥ ተህሊል (ላ ኢላሀ
ኢልለላህ)፤ተክቢር (አላሁ አክበር)፤ተሕሚድ (አል-
ሐምዱ ሊላህ) ማለትን አብዙ" (አህመድ 7/224)
ዐብዱላህ ኢብኑ ዑመር እና አቢ ሁረይራህ (ረዲየላሁ
ዐንሁማ) ወደ ገበያ በመውጣት በተክቢራ ሲያሞቁት
ሰዎቹም የነሱን ተከትለው ተክቢራ ይሉ ነበር
(ኢርዋዑል-ገሊል አልባኒይ 651)
4. ተውበት ማብዛት-
"…ምእምናኖች ሆይ! ትድኑ ዘንድ ሁላችሁም ወደ
አላህ (በመመለስ) ተጸጸቱ።" ሱረቱል አሕዛብ 31
5. መልካም ስራዎችን ማብዛት፡-
በኢስላም የመልካም ስራ በሮች ብዙ ናቸው፡፡
ተቆጥረው አይዘለቁም፡፡ ከኛ የሚጠበቀው ስራው
ላይ ተሳታፊ መሆን ነው፡፡ ከቤተሰብ ጀምረን እሰከ
ሩቅ ሰው ድረስ አቅማችን የቻለውን ያህል በመርዳት
ወደ አላህ እንቃረብ፡፡
6. በዒባዳ መጠናከር፡-
ከፈርድ ሶላት ቀጥሎ ያሉትን ሱንና ሶላቶችን
ማብዛት፤ቁርኣንን ማንበብና ማዳመጥ፡፡
7. ከሐራም መቆጠብ፡-
ከላይ የተጠቀሱት መልካም ስራዎች ላይ በመሳተፍ
የአላህን ተውፊቅ ያላገኘ ሰው ቢያንስ ከሱ እጅና
ምላስ ሌሎች ሰላም እንዲሆኑ እራሱን
ማቀብ፡፡እሱም ትልቅ ተውፊቅ ነውና፡፡
#ማረድን-የፈለገ፡-
የዒዱል አድሓን እርድ ለመፈጸም የነየተ የአላህ
ባሪያ (ወንድም ሆነ ሴት) ወሩ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ፡-
የሰውነት ጸጉሩን መላጨትም ሆነ መቀነስ፣ የእጁንም
ሆነ የእግሩን ጥፍር ማስተካከል፣ ከገላው ላይ
የተወሰነ ቆዳንም ቢሆን ቆርጦ ማንሳት
አይፈቀድለትም፡፡ ይህ ብይን የሚመለከተው የዒዱን
እርድ በራሱ ወጪ ለማረድ የነየተውን ግለሰብ ብቻ
ነው፡፡ ቤተሰቦቹን ብይኑ አይመለከታቸውም፡፡
ሰውየው በቀጥታ እራሱም አራጅ ሆነ፡ ወይም
በወኪል ቢያሳርድ ኃላፊው እሱ እስከሆነ ድረስ ብይኑ
ይመለከተዋል፡፡ ወኪል ሆኖ የሚያርደውን ሰው ግን
ብይኑ አይመለከተውም፡፡
ኡሙ ሰለማህ (ረዲየላሁ ዐንሃ) እንደነገረችን የአላህ
መልክተኛ (ሶለላሁ ዐለይሂ ወሰለም) እንዲህ አሉ፡-
"የዙል-ሒጃህን ጨረቃ ካያችሁና አንዳችሁም
ኡድሑያን (እርድን) ከነየተ፡ ጸጉሩንና ጥፍሩን
(ከመቀነስ) ይቆጠብ" (ሙስሊም 1977)፡፡
በሌላ ዘገባ ላይ ደግሞ ‹‹ከጸጉሩና ከሰውነቱ
(ቆዳው) ይቆጠብ›› ይላል፡፡ ስለዚህ ዕለተ ሐሙስ
የዚል-ቂዕዳህ 29ኛው ቀን ስለሆነ፡ ወሩ በዚያው
ሊጠናቀቅም ስለሚችል፡ የመግሪብ አዛን ከተሰማ
በኋላ ያለው ምሽት የዙል-ሒጃህ 1ኛ ቀን ሆኖ
ይጀምራል ማለት ነው፡፡ ወሩ ሠላሳ ከሞላ ደግሞ፡
ከጁምዓህ መግሪብ በኋላ ወሩ የዙል-ሒጃህ 1ኛ ቀን
ይሆናል ማለት ነው፡፡ እናም ለዒዱ እርድን የነየታችሁ
ወንድምና እህቶች ሆይ! ከዕለተ ሐሙስ መግሪብ
አዛን በፊት (የጸጉር፣ የጥፍርና የቆዳ) ጣጣችሁን
ጨርሱ፡፡
ሌላው ሊታወቅ የሚገባው ነገር፡ እርዱን የነየተ ሰው፡
በዙል-ሒጃህ የመጀመሪያዎቹ ዘጠኝ ቀናት ውስጥ
ጸጉሩን ወይም ጥፍሩን ቢቀንስ፡ ከፋራው ‹ካሳው›
ተውበትና ኢስቲግፋር ብቻ ነው በማለት ዑለሞች
ፈትዋ ሰጥተዋል (ኢብኑ ቁዳማህ፡ አል-ሙግኒይ
9/346)፡፡
አላህ ተጠቃሚ ያድርገን።
@Darul_Islam_channal
@Darul_Islam_channal
3.1K viewsedited 18:44