Get Mystery Box with random crypto!

በማለዳ ንቁ !

የቴሌግራም ቻናል አርማ bemaleda_neku — በማለዳ ንቁ !
የቴሌግራም ቻናል አርማ bemaleda_neku — በማለዳ ንቁ !
የሰርጥ አድራሻ: @bemaleda_neku
ምድቦች: ሃይማኖት
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 18.24K
የሰርጥ መግለጫ

(2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች ምዕ. 13)
----------
11፤ በቀረውስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ደኅና ሁኑ። ፍጹማን ሁኑ፥ ምክሬን ስሙ፥ በአንድ ልብ ሁኑ፥ በሰላም ኑሩ፥ የፍቅርና የሰላምም አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል።
14፤ የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ኅብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን። አሜን፡፡
@bemaledaa_neku_bot

Ratings & Reviews

2.33

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

0

3 stars

1

2 stars

2

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 2

2023-06-18 11:22:07
ብዙና ሰፊ ሀሳቦች የታጨቁበት ርእስ ነው፤ በጥሞና ቢመለከቱት ይጠቀም ይሆናል፡፡ ሥዕሉን ወደ ጎን ብናየው (horizontally) 'Vesica Piscis' የሚሉት፥ ሁለት ክቦች የተጠላለፉበትን ሞላላ የዕንቁላል ቅርጽ ይሰጣል፡፡ Vesica Piscis - የብርሃን በር - በሥነ ፍጥረት የአፈጣጠር ማብራሪያ አጽናፈ ዓለሙ የተወለደበት ማኅፀን ነው ይሉታል፤ በቀላል አማርኛ ፈጣሪ ፍጡራንን ከማይታየው ወደሚታየው፣ ካለመገለጽ ወደ መገለጽ (እም ኀበ አልቦ ኀበ ቦ) ያመጣበት ከምንም የማስገኘት ጥበብ ውክልና ነው፡፡ በእርሱ ውስጥ ቁርባን ተጽፏል፡፡ ምክንያቱም ቁርባንም እንዲሁ በሚታየውና በማይታየው መካከል የተዘረጋ ድልድይ፤ በሞትና በህያውነት፣ በምናውቀውና በማናውቀው፣ በተጨበጠውና በተሰወረው መካከል ያለ በር ነውና ነው፡፡ በሥጋ፥ በድንግል ማርያም ይወከላል /እመ - ብርሃን/፡፡ በተዋሕዶ ጉባዔ ትንተና በኩል ካየነው፥ በሃይማኖትና በመንፈሳዊነት፣ በላይኛውና በታችኛው፣ በክርስቶስና በክርስቶስ ሕይወትነት ሊኖሩ የሚተጉት መካከል ያለ መተላለፊያ ነው፤ የያዕቆብ መሰላል እንደማለት፡፡
5.8K viewsedited  08:22
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2023-02-18 09:05:27 ሰላም ለናንተ ይሁን፤

የጀመረነው ጉዞአችን አልተቋረጠም፡፡ አይቋረጥምም፡፡ በዚሁ አጋጣሚ በዚህ ቻናል በሚተላለፉ ሀሳቦች ይብዛም ይነስም ብርታት ስታገኙ ቆይታችሁ ግን ሰሞኑን የተዳከማችሁ ካላችሁ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡ ተቋርጠን አይደለም፤ ይልቅ ወደ ተሻለው ልንሄድ ነው፡፡

ዝርዝሩን በአጭሩ ላድርገውና፥ በዋነኝነት እስከዛሬ የተቀባበልናቸውን የትኅርምት ትምህርቶች በይዘት አጠንክረን፣ በመሠረት አደላድለን፣ አስፈላጊን ጨምረን፣ የሚተዉትን ቀንሰን መጽሐፍ ልናደርጋቸው ስላሰብኩ ነው የተጠፋፋነው፡፡ የመጽሐፍ መኖሩ ነገር አስፈላጊ መስሏል፡፡ በደንብ የተሰናዳና አንድ ከፍ ያለ ዓላማ ያለው ጥራዝ የእስከዛሬዎቹ ትምህርቶች ሊሆኑ አስፈልጓቸዋል፡፡ ወጥ የሆነ፣ ቢያንስ መሠረታዊ ውጊያ መናፍስትን የተመለከተ ሃሳብ ስለሌለ፥ ብሎም ትኅርምት በራሱ ወደ አንድ ከፍታ የመድረሻ ሂደት እንጂ ማብቂያ አለመሆኑን የግንዛቤ እጥረት በሰፊው ስላለ ተልዕኮ ያለው መጽሐፍ ማዘጋጀቱ ግድ ብሎኛል፡፡ ቅድሚያ በሕይወቴ እየተጻፈ ነው፤ በየዕለቱ! የሕይወት መጽሐፍ ቃላት ደ'ሞ የአምላክ ፊደሎች ናቸው፡፡

ዞሮ ዞሮ የሚሆነውን አሁን ባላውቅም፥ መጽሐፉን እንደጨረስን ይሄን ምዕላድ አሳድገን፣ የሃሳብ ክበቦቹን አስፍተን፣ የነበረውን አካሄድ በዓላማ ሳይሆን በይዘትና ቅርጽ አሻሽለን እንመለስበታለን፡፡ እንዳትበተኑ፡፡ የተተወ እንዳይመስላችሁ፡፡ ብንተወዉ የማይተወን ውስጥ አንዴ ገብተናልና፡፡ እስከዚያን፥ ራሳችሁን እየሠራችሁ ቆዩ፡፡ አንድ ነገር በሙሉ እርግጠኝነት ልንገራችሁ፤ በመጠኑም ይሁን አግኝቶኝ ስላገኘሁት ነው፡፡ የትናንቱ እግዚአብሔር ዛሬም እየሠራ አለ፡፡ መንፈሱ ሕያው ነው፡፡ ይሄ መንፈስ ነው ብንተወዉም አይተውም የሚያሰኘው፤ ልክ ዮናስ ከፊቱ የሸሸ መስሎት ወደርሱ እንደሄደው፡፡ ስለዚህ ራሳችሁ እየሠራችሁ ወደፊት ገስግሱ፡፡ ለክርስቲያኖች የማንነት መሠሪያቸው ወንጌል የምትባል መሣሪያ ናት፡፡ ጳውሎስም "ሥር ሰዳችሁ #በእርሱ ታነጹ" ሲል ያግዘኛል (ወንጌል እርሱ (ሕይወቱ) ነውና)፡፡ዓለም ላይ ያሉ እውነተኛና በጎ ሃሳቦች ሁሉ የጽዮን ሕግ፣ የወንጌል ነጸብራቆች ናቸው ብዬ በግሌ አምናለሁ፡፡ ስለዚህ ተሠሩባት፤ በልብ አኑሯት፤ እንደ ማኅተም በክንድ እሠሯት፤ ተመሩባት፡፡ ይህን እንዲሁ በተለመደ የስብከት መንፈስ አትመልከቱት፤ ነገሩ እንዲሁ ጥሩ ሰው የመሆን ያለመሆን፣ የነፍስ ጽድቅና ኩነኔ ብቻ አይደለም፡፡ የሰውነት፣ የዕረፍት፣ የሙሉነትም እንጂ፡፡ አንጠፋፋንም፤ ባይሆን ወደ ላቀው እንሰበሰባለን እንጂ፡፡ በያላችሁበት በበጎ ምኞት አስቡኝ፤ ደግ ምኞት የልብ ጸሎት ነውና፡፡

#ጽኑ
827 viewsedited  06:05
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-12-22 19:43:43 መግፍኤ : - "ወካልእታሂ እንተ ትመስላ አፍቅር ቢጸከ ከመ ነፍስከ ወዘየዐቢ እምእላንቱ ትእዛዛት አልቦ፡፡ - ሁለተኛይቱም። ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ የምትል እርስዋን የምትመስል ይህች ናት። ከእነዚህ የምትበልጥ ሌላ ትእዛዝ የለችም።" ማር 12፥31

ይርበናል አይደል? እነርሱም ይርባቸዋል፡፡ ይበርደናል አይደል? እነርሱም ይበርዳቸዋል፡፡ ደስ ይለናል አይደል? እነርሱም ደስ ይላቸዋል፡፡ ይጨንቀናል አይደል? እነርሱም ይጨንቃቸዋል፡፡ ያስፈልገናል አይደል? እነርሱም ያስፈልጋቸዋል፡፡ ያናድደናል አይደል? እነርሱም ያናድዳቸዋል፡፡ ይረሳናል አይደል? እነርሱም ይረሳቸዋል፡፡ ..ማናቸው እነርሱ? ይሄን ጥያቄ "ባልጀራህን እንደ ራስህ ውደድ" የተባለው ሰው ጠይቆት ነበር፡፡ 'ማንኛውም እንዳንተ ያለ ሰው' የሚል መልስም ተመልሶለታል፡፡ ሉቃ. 10፥ 30-37

በእርግጥም ልክ ነው፡፡ የሚሰማን ሁሉ የሚሰማው እንደኛ ሰው የሆነ ማንኛውም ሰው ነው፡፡ ጨካኝ የተባለ ሰው እንኳ ጀርባውን እየቸበቸበ አይዞህ የሚለውን ይፈልጋል፤ ሰው ነዋ! ፍቅር የባሕርያችን ጉዳይ ነዋ! ይሄ፥ ሥነ አመክንድም እንበለው ፍልስፍና፥ ሳይንስም እንበለው ሥነ መለኮት፥ ተፈጥሮም እንበለው ንግርት፥ የትኛውም ዓይነት ዕውቀት፣ ሀሳብ የሚያምነውና የሚያረጋግጠው ቀላልና ግልጽ እውነት ነው፡፡ እንደ ሰው የምንፈልገው ሁሉ እንደ ሰው እንደሚያስፈልጋቸው ለማወቅ መገለጥ፣ የተለየ ጥበብ አሊያ የሚሥጢር ቁልፍ አይጠይቅም፡፡ ሰው መሆን በቂው ነው፡፡

አስተውለናል አይደል?
ፍቅር የበጎ ነገር ሁሉ እናት የሆነችው በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ ርኅራኄ፣ ቸርነት፣ የዋህነት፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣.. ሁሉም የሚወለዱት ለእኛ ያልነውን መልካም ለእነርሱም ስንል ነው፡፡ ለምሳሌ ይጠማናልና አይጥማቸው ስንል ለጋስነት ይመጣል፡፡ እንስታለንና እንረዳቸው ስንል ቅንነት ይገኛል፡፡
..እንቢኝ ልቡናዎች ሆይ፥ እስቲ ተሸነፉ፡፡ ልብ ሰጥቶን ሳለ ልብ ይስጠኝን ተዉ፡፡ ሲዖልን ለገነት የሚያድሰው የፍቅር ጥበብ ነው፡፡ ጥፋትን የሚያጠፋው የፍቅር ኃይል ነው፡፡ ጴጥሮስ ለዚህ እኮ ነው "ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ" የሚለው፡፡ 1ኛ ጴጥ. 4፥8 ..ለማንኛውም፥ ባስጀመረን መግፍኤ የጀመርነውን እንጨርስ፡፡

መልእክቱ ለዮሐንስ :- "ማንም። እግዚአብሔርን እወዳለሁ እያለ ወንድሙን ቢጠላ ሐሰተኛ ነው፤ ያየውን ወንድሙን የማይወድ ያላየውን እግዚአብሔርን ሊወደው እንዴት ይችላል? እግዚአብሔርንም የሚወድ ወንድሙን ደግሞ እንዲወድ ይህች ትእዛዝ ከእርሱ አለችን።" 1ኛ ዮሐ. 4፥20-21

@bemaleda_neku
1.5K views16:43
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-12-09 14:22:29 ተሞክሮ 131

@bemaleda_neku
1.4K views11:22
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-12-03 13:01:20 መንፈስ በመንፈስ አይቆምም!

ከዲያቢሎስ መንፈሶች ጋር በሚደረገው ትግል ውስጥ ብዙ ዓይነት ሂደቶች ይታለፋሉ፡፡ እነኚህም ሂደቶች በተለያየ ዓይነት ተለዋዋጭ ስሜቶች፣ ጊዜያት፣ ሀሳቦች ውስጥ ያሳልፋሉ፡፡ ሂደቶቹ የውጊያ ሲሆኑ፥ እንደ ውጊያነቱ መውደቅ፣ መነሣት የሚባሉት ይኖሩ ዘንድ የግድ ይጠበቃል፡፡ ጳውሎስ ይህንን መንፈሳዊ ጦርነት "መጋደል" ሲል የሰየመው ስለዚሁ ነው፡፡ (ኤፌ. 6፡12)

የምንጋደላቸው ክፉዎች መናፍስት በተለያየ አቅጣጫ ወደኑሮአችን የሚመጡ ናቸው፡፡ አንዱ በሰዎች አማካኝት የጥቃት ተልዕኮ ይዘው የሚመጡት የመተት፣ የድግምት፣.. መንፈሶች ናቸው፡፡ እነዚህ በአብዛኛው በሥጋ ሕይወት ጉዳይ ጥፋት እንዲያደርሱ የሚሰለፉ ስለሆኑ፥ የሥጋም ነገር በራሱ ደካማ ከመሆኑ ጋር በተያያዘና ወዲህም የብዙዎቻችን በመንፈስ ያለመንጠንከር ምክንያት፥ ፈተናቸውን ከባድና ትንፋሽ ጨራሽ ያደርገዋል፡፡ ነገሩን ይብሱን ፈታኝ ያደረገው ደ'ሞ የሚላኩ መናፍስት መላልሰው የመምጣት (የመታደስ) ሰፊ ዕድል ያላቸው መሆኑ ነው፡፡

ከዚህ የተነሣ ምሬቶች አሉ፡፡ መታደሱን ለማስቆም የምን ይሻላል ጥያቄዎች ይጠየቃሉ፡፡ ለነዚህም ከሚሰጡ ምላሾች መካከል "መናፍስቱን ወደ ላኪዎቹ መላክ" የሚሉ መልሶች ሲደመጡ ይሰማሉ፡፡ እናም፥ እንዲህ ያሉ መልሶች ስሕተት እንዳለባቸው፣ አግባብ እንዳይደሉም አስተያየት መስጠት የዚህ ጽሑፍ ዋና መልእክት ነው፡፡

እንደ መጽሐፍ እውነት፥ ክፉ የሚሸነፈው በደግ ብቻ ነው፡፡ (ሮሜ. 12፡21) ጨለማ የሚገፈው በብርሃን መገለጥ ነው፡፡ (1ኛ ዮሐ. 3፡9) ርኵስ መንፈስ ቦታ የሚለቀው የተቀደሰው መንፈስ ስፍራውን ሲይይዝ ነው፡፡ እርስ በእርሱ የሚለያይ መንግሥት በአንድ አይቆምምና፡፡ እንዲሁ የመተትም እድሳት በቁርባን ኃይል፣ በትእዛዘ እግዚአብሔር፣ በጊዜ እግዚአብሔር እንጂ መተቱን በመመለስ የሚከሽፍ አይደለም! በጭራሽ አይደለም!

እንደው ከሸፈ እንኳ ብለን ብንወስድ፥ የሰይጣናቱ ፈተና በዚሁ ያበቃ ይመስለናልን? ከመተት ውጪስ በሌላ ብዙ መንገድ የመጡትን ወደማን እንሰዳቸዋለን? ደ'ሞስ በመንፈስ የመታገሉስ ግብ ፈተናን ማስቆም ነው ወይ? ዲያቢሎስ ጌታን ፈትኖ ሲያበቃ "እስከ ጊዜው" ተወው የተባለ ስለምን ይመስለናል? (ሉቃ. 4፡13) ከዚህ ከተሸነፈ ዓለም እስክታልፉ በፈተና ታልፋላችሁን እንደምን አስተውለነዋል? (ዮሐ. 16፡33) ከአጋንንቱስ ባሻገር ያለብንን የባሕርይ ጾር በምን እናስቆመዋለን? ወደ ስብዕና ሙላት፣ ወደ መንፈስ ቅዱስ ማደሪያነት፣ ወደ ኅብረታዊ ማንነት በመከራ ካልሆነ በምን መንገድ ልንጓዝ እንችላለን?  ..ብናውቅበትስ፥ ረድኤተ አምላክን፣ ጽናትን፣ የአእምሮና የልቡና መታደስን፣ እምነትና እውነትን በማዋሐድ በኩል አድርጎ ወደልዕልና ጫፍ እንደ ሥቃይ የሚያደርሰን ምንም ጓዳና አናገኝም፡፡ (ዕብ. 12፡11) ሥጋዊት ዓለም እንኳ ይሄ በሞት እያለፉ የመኖር ጥበቡ ተገንዝቧት "የስኬት መግፍኤው ውድቀት ነው" ስትል ትልቅነቶችን ትሰብካለች፡፡

በርግጥ ይሄ ሲያወሩት እንጂ ሲኖሩበት ቀላል አይደለም፡፡ በተደጋጋሚ በሚታደሱ መናፍስት ምክንያት ያለውን አበሳ ያሉበት ብቻ ያውቁታል፡፡ ነገሩ በመኖርና ባለመኖር መካከል ባለ ቀጭን መስመር ጭምር የሚያቆም ሊሆን ይችላል፡፡ ሳያቋርጡ በሚላኩ ክፉ መናፍስት ሰበብ የተሰላቹ፣ የተበሳጩ፣ እልህ የተጋቡ፣ ሰላም የተነጠቁ፣ በረከት የተሰለቡ፣.. ብዙዎች ናቸው፡፡ በባዕዳን ሀገራት በብቸኝት፣ አጽናኝ በማጣት፣ በተስፋ መዘጋጋት የሚጨናነቁ ወገኖቻችን አሉ፡፡በቤተ ክርስቲያናት ቅጥር ውስጥ አርፈው የደቂቃዎች እፎይ የናፈቃቸው በርካታ ይሆናሉ፡፡

ታዲያም በሚከታተል የኑሮ ውጣ ውረድ መንስኤነት ሆደ ቡቡ የሆኑ ብዙ ምእመናን መገኘታቸው እሙን ሲሆን "መተትን ወደመታቹ መላክ መንፈስ እንዳይታደስ መፍትሔ ነው" የሚል ሀሳብ እንደ መረጃ መስጠት አግባብነት የለውም (ቀድሞውኑ መንፈስ ቅዱስ እንዲህ ያለውን ጸሎት ሆነ የእምነት ትእዛዝ ተፈጻሚ አያደርገውም)፡፡ "በጣም የተቸገሩቱ እናስ እንደምን ይሁኑ?" ብለን እንኳ ሀሳቡን በቀናነት ብንመለከተው፥ እጁን የተጫረም ሆነ እጁን የተቆረጠው በአንድ ላይ እንደሚያደምጡ ማጤን አስፈላጊ እይታ ነው፡፡ እናቱ የሞተችበትም ገበያ የሄደችበትም እኩል ያለቅሳሉ፡፡ ገና በትኅርምቱ መስመር መምጣት የጀመረም ይሁን ለዓመታት የከረመው "አቤት የኔ ትንንቅ" እንደሚሉ መቼም የታወቀ ነው፡፡ ስለዚህ እንደዚህ ዓይነት የጭንቅ ጊዜ አማራጮችን ለተለያዩ አዳማጮች እስከነቃጭሉ ማሰማት የትክክልነትን ሚዛን አይደፋም፡፡ በወንጌል ዕውቀት ያልበረቱ፣ በልምድ ትምህርት ያልዳበሩ፣ የመንፈሳዊ ውጊያን መሠረታዊ ጠባያት በውል ያልተረዱ አማንያንን ታሳቢ ያላደረጉ መልእክቶች ከአገልግሎት ሊታረሙ ያስፈልጋቸዋል፡፡

ቃላተ እግዚአብሔር ዶግማ (መሠረትና ጠርዝ) ናቸው፡፡ አይጣሱም፣ አይለወጡም፣ አይሻሻሉም፡፡ እኛ ወደ ትእዛዛቱ እንወጣለን እንጂ ትእዛዛቱን ወደእኛ አናወርዳቸውም፡፡ የከበዱንን ቆርጠን አናወጣቸውም፡፡ የቀለሉንን መርጠን አንለያቸውም፡፡ ወደምርጫችን ቀጽለን ወደፈቅድነው አንመራቸውም፡፡ እንግዲያው በተለይ ፍቅርን ማዕከልና አድራሻ ያደረጉትን ሕግጋተ ወንጌል ከላይ ከሞገትነው ሀሳብ አንጻር እንደምን ልናስማማቸው እንችላለን? (ማቴ. 5፡39 ፤ 44-45 ፤ ሮሜ. 12፡17 ፤ .. )

የምሕረቱ ዘመን ደቀመዛሙርት ድምፃቸው የሚያጠነጥነው፥ በመምህራቸው ዓላማ በፍቅር ዙሪያ ነው፡፡ በዚያውም ላይ ክርስቲያኖች የክርስቶነታቸው መታወቂያ በፍቅር እንደ ፀሐይ ማብራታቸው ነው፡፡ ፀሐይ ለኃጥአን ከልክላ ለጻድቃን የምትፈቅደው ጨረር የላትም፡፡ ከሰማዩ በታች ጠንቋዩም የዋሁም አሉ፡፡ ሁለቱም ማለዳቸውን በከፈቱ ጊዜ የሰማይቱን ፀሐይ ይመከለታሉ፡፡ ለመጥፎ ጨልማ ለበጎ የምትደምቅ ፀሐይ የለችም፡፡ እነሆም አማናዊው ፀሐይ ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርዩን ብርሃን በሐዋሪያት በኩል ለተቀበሉት ሁሉ በጸጋ ማካፈሉ "አንትሙ ውእቱ ብርሃኑ ለዓለም። - እናንተ[ም] የዓለም ብርሃን ናችሁ" በማለቱ ታውቆአል፡፡ (ማቴ. 5:14) ይህም ብርሃን እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ ነው ያለው፡፡ (ቁ.16) ለእገሌ ታይቶ ለእንቶኔ ይጥፋ አላለም፡፡ ይልቅስ እንዲሁ ይብራ!

ፍቅር እንዲሁ የምናበራው የማንነት ፀሐይ እንጂ በከፉብን ተከፍተን የምናጸልመው ብርሃን አይደለም፡፡ እንደውም ሐዲስ ብእሲ ክርስቶስን የሚከተል ፋና እርምጃውን ማቅናቱ የሚታወቀው እስከሞት የጠሉትን በመውደዱ ውስጥ ነው፡፡ ለመስበር የገፉትን በማቀፉ በኩል ነው፡፡ የሚወዱንን ብቻ ብንወድ እንኪያስ ይህ ምን ብልጫ አለው? በብሉይ ዓለም ያሉት ይሁኑ የማያምኑቱ ይህንኑ ያደረጉ የለምን? መስቀልን የመሸከም እውነተኛ ትርጉሙስ እንደምን ያለ ነው? መስቀል የእግዜር ውኃ እንኳ ስለሚነፍጉን የምንጸልይበት የመውደድ መቅደስ እንጂ የአንገት ላይ ምልክት ብቻ አይደለም፡፡ እናስብበት፡፡ ትኅርምትን ከትምህርት ማስተባበር ይኑረን፡፡ ያክርመን!

@bemaleda_neku
1.3K views10:01
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-11-20 14:55:36
መናፍስት ወደ ሰው ሕይወት መጥተው ጦርነት ሲከፍቱ ምሽግ የሚሠሩት በረቂቅም በግዙፉም አካል ውስጥ ነው:: ርእሳችን እንዳይሰፋ ረቂቁን ብቻ እንያዝና፥ ክፉዎቹ ተደብቀው የሚቀመጡት ለእነርሱ በሚመቻቸው ጠባይ ውስጥ ጭምር ነው:: ከላይ በጀመርነው ምሳሌ ስንጨርስ፥ ትሕትናን ያልተዋወቀ አንድ ሰው ትዕቢተኛ በሆነ ማንነቱ ውስጥ ትዕቢተኞች የሆኑ መናፍስት ይሸሸጋሉ:: በኋላም ይኸው ግለሰብ የውጊያው ዓለም ገብቶት መንፈሳዊ ልምምድ ሲጀምር፥ መናፍስቱ የተሸሸጉበት ግንብ እንዳይናድ በጥንቃቄ የውጊያውን ምሪት አቅጣጫ ያስለውጡታል:: ማለትም መንፈሳዊ ልምምዶቹን እየለመደ ያለው ወጣኒ ስለ ቅንነት፣ የዋህነት፣ ልበ ንጹሕነት ምንም እንዳይገደው ሥጋዊ ጉድለቶቹን ብቻ እያጎሉ ያሳዩታል:: በመሆኑም "አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ፥ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል" የሚለውን ታላቅ መመሪያ በማሳት፥ የሚጨመረውን የሥጋ ነገር ፍለጋ በመንፈሳዊ ድካም ሲባዝን፥ "ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው" ካለው፥ ጽድቅን እንደ እህል ውኃ ሊያስስ ከሚገባው ቀዳሚ ፍለጋ ብሎም መድረሻ አሽሽተው ካርታ የሌለው ከርታታ ያደርጉታል:: (ማቴ. ፮፥፴፫)

በዚህ ውጊያውን በተመለከተ ነገር ላይ ጳውሎስ ያለውን ልበልና አንቀጸ ብፁዓንን ማስተዋወቅ ልጨርስ:: ሐዋሪያው፦

"የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ። .. ወገባችሁን በእውነት ታጥቃችሁ፥ የጽድቅንም ጥሩር ለብሳችሁ፥ በሰላም ወንጌልም በመዘጋጀት እግሮቻችሁ ተጫምተው ቁሙ፤ በሁሉም ላይ ጨምራችሁ የሚንበለበሉትን የክፉውን ፍላጻዎች ሁሉ ልታጠፉ የምትችሉበትን የእምነትን ጋሻ አንሡ፤ የመዳንንም ራስ ቁር የመንፈስንም ሰይፍ ያዙ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው።"

(ኤፌ ፮፥፲፩-፲፯)


እነሆ የእግዚአብሔር ቃል መንፈስም ሕይወትም ብቻ ሳይሆን መናፍስትን የመውጊያ ጦር ዕቃም ነው ማለት ነው:: ይሄ መሣሪያ በየዓይነቱ ተደርድሮ የተቀመጠበት ዕቃ ቤት ደግሞ አንቀጸ ብፁዓን ይባላል:: በሌላ አባባል መድኃኒታችን ከተራራ ሆኖ የደነገጋቸው እንደ ትሕትና ያሉት ብፁዕ ትእዛዛት፥ ሰው የመሆንን ነገር የሚያስጠብቁልን ሕግጋት ብቻ ሳይሆኑ ሰው እንዳንሆን የሚፋለሙንን የስብዕና ጠላቶች የምንጋደልባቸው የመንፈስ ሰይፎች ናቸው:: ስለዚህ.. ..

አንቀጸ ብፁዓንን ጌታችን ያስተማረውን የተራራው ስብከትን (ማቴ. 5-7) ታነቡት፣ ታጠኑትና ሕይወት እንዲሆንላችሁ ዕለት ዕለት ትኖሩት ዘንድ እማልዳለሁ:: ያቆየን!

@bemaleda_neku
2.1K views11:55
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-11-20 14:55:36 በእንተ ብፁዓን !

ክርስትና እንደ ክርስቶስ የመኖር ሕይወት ነው:: የእግዚአብሔር ልጅ ራሱን በሰው ልጅነት በለካበት መሥፈሪያ ሰውነትን መለካት የሐዲስ ኪዳን ክርስትና በቁዔት ነው::

በእውነት ለምናምን፥ አድራሻችን፣ ጥጋችን፣ ፍጻሜያችን ሁሉ ክርስቶስን በመምሰል እርሱን በጸጋ መዋሐድ ነው:: አድራሻችን፣ ጥጋችን ካልን፥ ቃላቱ አንዳች ሊያሳዩ የፈሉት ጉዞ ወይንም ሂደት አለ ማለት ነው:: ይህንን ጉዞ የምንጓዘው ደግሞ በተሳሳተ አቅጣጫ እንዳይሆን እርሱን እንድንመስለው ሲል እኛን የመሰለው ጌታ "እኔ መንገድ ነኝ" አለ:: (ዮሐ. ፲፬፥፮)

የዚህ መንገድ የመጀመሪያ ተጓዦች ሐዋሪያት ነበሩ:: እነርሱም የወጠቡት የወረዱበት፣ የወደቁበት የተነሡበት፣ እንደ በጎች በተኩላ መካከል የተሰማሩበት ይህን መንገድ ከእኛ በኋላ የምትነሡም ክርስቲያኖች ሂዱበት ሲሉ "እኔ ክርስቶስን እንደምመስል [እናንተም] እኔን ምሰሉ" በማለት በኑሮአቸው ገልጠው አስተማሩ:: (1ኛ ቆሮ. ፲፩፥፩)

እንግዲህ አንድ ስለ ክርስትናው ነገር በእውነት ያለ ሐሰት የሚያስብና ዋጋውንም በሕይወት ማክበር የሚፈልግ አማኝ፥ ይህንን ክርስቶስ የመሠረተውን፣ መሥርቶም የተጓዘውን፣ ተጉዞም እሱ በሄደበት ሌሎችን ያስከተለውን መንገድ እንዴት ላገኘው እችላለው? ሲል ሊጠይቅ ይገባዋል:: ጥያቄውንም አሰምቶ በተናገረ ጊዜ መልስ የምትሆን ቃል እንዲህ ትለዋለች፦ 'ወንጌልን አንብብ፥ ከወንጌልም ማቴዎስን፥ ከማቴዎስም፥ የተራራውን ስብከት - አንቀጸ ብፁዓንን!'

አንቀጸ ብፁዓን እንደ ክርስቶስ የምንኖርበት፥ በምድር የምንራመደው ሰማያዊ ፍኖት ነው:: በሐዲስ ኪዳን የተጻፉ ወንጌላትና መልእክታት ማዕከላዊ ርእሶች፥ በዚህ፥ ክርስቶስ ተራራ ላይ ወጥቶ ደቀመዛሙርቱንና ሕዝቡን ባስተማረው ትምህርት ዙሪያ ያጠነጥናሉ:: የዚህም ምክንያት፥ እነዚህ የተመሰገኑ ቃሎች ትምህርቶች ብቻ ሳይሆኑ ሕግጋትም በመሆናቸው ጭምር ነው:: የሃይማኖት ጠቢባን የኦሪት ሕግ በ(ሲና)ተራራ እንደተሠራች፥ ሐዲሷም ሕግ በተራራ ተመሠረተች ይላሉ:: ስለዚህ አንቀጸ ብፁዓን ክርስትናን የምንከተልበት ጎዳና ብቻ ሳይሆን ክርስትናን የሚያኖረን ትእዛዝም ነው ማለት ነው::

ክርስቶስ በአንቀጸ ብፁዓን ያስተማረው ራሱን ነው:: እርሱ የሚናገራቸው ንጹሕና በጎ ቃላት መንፈስም ሕይወትም ናቸው:: (ዮሐ. ፮፥፷፫) እንደ ሕይወትነታቸው አንድም እርሱ የኖረውን ሕይወት እንድንኖር ያሳስባሉ:: ለምሳሌ፥ "በመንፈስ ድሆች የሆኑ (ትሑታን) ብፁዓን ናቸው" ሲል የተራራው ስብከት ይጀምራል:: የትሕትና ጠባይ፣ ልክና መሠረት ደ'ሞ ሌላ ማንም ሳይሆን ክርስቶስ ነው (እኔ በልቤ ትሑት ነኝና ማለቱን ያስታውሷል (ማቴ. ፲፩፥፳፱)):: እንደገና ዝቅ ብለን ብናነብ "የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው፥ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና" ሲል እናገኛለን:: እንግዲያስ ነፍስና ሥጋን፣ ሰውና እግዚአብሔርን፣ መላእክትና ሰውን፣.. ያስማማው የእግዚአብሔር [የባሕርይ] ልጅ ኢየሱስ አይደለምን? እንቀጥል ብለን "ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው" የሚለው ጋር ብንደርስም እንዲሁ የምናገኘው መድኃኒታችንን ነው:: ገና ከልደቱ ስፍራ ከቤተልሔም ጀምሮ ማረፊያ አጥቶ ሲሰደድ ኖሯልና::

እንኪያስ ክርስቶስን መኖር የፈለገ ሰው አንቀጸ ብፁዓንን መኖር ይገባዋል:: (፩ኛ ዮሐ. ፪፥፮) እርሱ እንደኖረው ሳይኖሩ ክርስቲያን (እንደ ክርስቶስ) ነኝ ማለት ሐሰት ይሆንብናል:: "ማንም በኋላዬ ሊከተለኝ የሚወድ መስቀሉን ተሸክሞ ዘወትር ይከተለኝ" በማለት ክርስቶስ ክርስትናን ሲሰብካት እኮ፥ መስቀሉን (መከራውን) ያሸከመን አንገታችን ላይ በምናኖረው ማኅተብ ብቻ ሳይሆን በሕይወታችን ውስጥ በምንኖረው፥ "ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ (መከራን የሚታገሡ) ብፁዓን ናቸው" ባለው ቃል ጭምር ነው:: እንደዚህ ያሉትን የጌታን ቃላት ሳይሸከሙ፥ ጌታን መከተል አይቻልም:: መስቀል በአንገት የሚያጠልቁት ከልብ ግን የሚያወጡት ምልክት አይደለም:: እንዲህማ ከሆነ፥ የዳዊትን መጽሐፍ ይዘው ዳዊትን ከማያውቁት አይሁዳውያን በምን ተሻልን?

ክርስቶስን የምንወድ ልቦናዎች እንስማ:: ቃሉን ሳይኖሩ ክርስትናን መኖር አይቻልም:: እርሱም "የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል" ያለው ይህንን ነው:: (ዮሐ. ፲፬፥፳፫) አንቀጸ ብፁዓንን ትቶ ክርስቶስን አለመተው አይቻልም:: እውነትስ የዋህ ሳይሆኑ ክርስቲያን የሚሆኑት እንደምን ባለ ጥበብ ነው?

አንቀጸ ብፁዓንን ስናነብ ክርስቶስን እንደምናነብ፥ ክርስቶስን ስናነብ ሰውነትን እንደምናነብ፥ ሰውነትን ስናነብ ሁላችን ልንሆን የሚገባውን እንደምናነብ እናስተውል:: አንቀጸ ብፁዓን አንድ የሃይማኖት ተቋምን የተመለከተ ጉዳይ ሳይሆን ከሁሉ የሚቀድመውን ሰውነትን የተመለከተ ጉዳይ መሆኑን የምናውቀው፥ ትምህርቶቹ በአንድም በሌላም መንገድ የሚያምኑም ሆነ የማያምኑ ሰዎችን ቀልብ ሲገዙና ክርስቶስን የሚቃወሙ ርእዮቶች ጭምር ሲስማሙባቸው መገኘቱ ነው:: "ሰው" የሆነ ሰው ሁሉ አንቀጸ ብፁዓንን ሊገፋት አይችልም:: ቢያንስ በብያኔ ደረጃ ትሕትናን የሚጠላት፣ ምሕረትን የሚነቅፋት፣ ንጽሕናን የሚቃወማት፣.. አይገኝም::

ስለዚህ አንቀጸ ብፁዓን፥ በመግቢያው ላይ እንደተጠቀሰው ለሰውነት የሚያበቃ የስብዕና ትምህርት ነው:: እንዲህ ባለ አረዳድ ብንረዳው፥ እግዚአብሔር በአንድያ ልጁ ዓለምን ለመጠቅለል የወደደበትን ሚሥጢር እንረዳዋለን:: ይሄን ባንረዳ እንኳ ሌላው ቢቀር እንደተፈጠርንበት ተፈጥሮ ሰው ሆኖ የመኖር ዕድሉን እናገኛዋለን::

ሌላው ከመንፈሳዊው ውጊያ አንጻር አንቀጸ ብፁዓን ያለው አገልግሎት ነው:: ለብዙ ሰዎች የመንፈሳዊው ፍልሚያ ጦር ዕቃ የሚመስላቸው መንፈሳዊ ልምምድ (ስግደት፣ ጸሎት፣ ጾም፣.. ) ብቻ ነው:: በዚህም አስተሳሰብ የተነሣ የነዚህ ሰዎች የፍለጋ ዝንባሌ የሚያተኩረው ልምምዶቹ ላይ ሆኖ ይወሰናል:: ይሄ መወሰንም፥ ዞሮ ከተነሡበት የሚያደርስ፣ ሃይማኖታዊ ጉልምስናን የሚያቀጭጭና ጊዜ እየሰነበተ ሲሄድም ወደ መሰላቸት የሚያመራ ይሆናል::

መንፈሳዊ ልምምዶች መነሻዎች እንጂ ውጤቶች አይደሉም:: ይኸውም መጽሐፍ "ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ" በማለቱ ታውቆአል:: (ማቴ. ፫፥፰) መንፈሳዊ ልምምዶች አንድ ዘር ተዘርቶ እንዲበቅል ውኃ በማጠጣት፣ ተገቢ ብርሃን በመለገስ፣ ከአረም በመጠበቅና አስፈላጊ ማዕድናት በመስጠት የሚጠበቀው ፍሬ እንዲገኝ እንደምንሠራው ያሉ ሥራዎች ናቸው እንጂ በራሳቸው ፍሬዎች አይደሉም:: ማለትም የሚጸልይ ሰው በመጸለዩ ምክንያት የመጣው ለውጥ መታየት ይኖርበታል:: የሚሰግድም እንዲሁ ከማይሰግደው የሚለይበት መገለጫዎች ሊኖሩት ይገባል:: አለዚያማ እንግዲያ በመጾምና በመራብ መካከል ያለው ልዩነት ምን ሊሆን ነው?

በመንፈሳዊ ልምምዶች መናፍስትን መዋጋት አንቀጸ ብፁዓንን እንድንኖር ማስተዋል የሚከፍትልን ሂደት እንጂ መደምደሚያ አይደለም:: በሌላ አገላለጥ በመንፈሳዊ ልምምዶች ላይ ተገኝቶ ከአንቀጸ ብፁዓን የጠፋ ምእመን፥ በረጅሙ የታሰረ የዲያብሎስ ምርኮኛ መሆን አይቀርለትም:: እውነትም ከጌታ ፊት ራሱን ሊያዋርድ ስለ አምልኮት የሚሰግድ ጉልበት፥ በሕይወቱ ገጠመኞች ውስጥ የተከበረችውን ውርደት (ትሕትና) የማይገልጣት ሲሆን፥ ትሕትናን የሚያሳድዳት ክፉውን ኃይል እንዴት አድርጎ ያሸንፈዋል?
2.1K views11:55
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-11-04 09:43:42 ወዲህም
በጥብቅ ለሚያውቁት ግን ለማይፈሩት ሰው የሚሰጡት ነጻነት፣ አብሮነት፣ ትዕግስት፣ ..
ወዲያም
በጥብቅ ለማያውቁት ግን ለሚፈሩት ሰው የሚሰጡት ጥንቃቄ፣ ክብር፣ ትሕትና፣ ..
ውሕደት ማለት - ፍቅር ማለት!

እንዴት ማለት?

ፍቅር፥ ክርስቶስ ነው፡፡ ያ ማለት ፍቅር ሲተረጎም፣ ሲበየን ክርስቶስ ማለት ነው፥ ነው በአጭሩ፡፡ ክርስቶስ የሥግው ቃል ስም ነው፡፡ እርሱም ከሁለት ባሕርያት ያለመቀላቀል፣ ያለመለወጥ፣ ያለመከፈል አንድ ባሕርይ የሆነ ነው፡፡ ሁለቱ በመጠባበቅ የተዋሐዱት ባሕርያት ከአንድነታቸው አስቀድሞ ለየብቻ ሳሉ የተለያዩ ናቸው፡፡ መለኮት፥ አምላክ፣ ረቂቅና ምሉዕ ነው፡፡ በተቃራኒው ትስብእት፥ ፍጡር፣ ግዘፍነት ያለውና ውሱን ነው፡፡ እነዚህ፥ አንዱ አንዱን ሳያስለቅቀው፣ ሳይጠቀልለው ተዋሕደው በክርስቶስ አሉ፡፡ እነሆ የፍቅር አንደኛው ትርጉሙ በዚህ አለ፤ ፍቅር ማለት አንድም አንድነት ነውና፡፡ የፍቅር አንድነት ተመሳሳይን ብቻ የሚያዋሕድ አይደለም፤ መስተቃርናንም ጭምር እንጂ፡፡ ይሄ በክርስቶስ ለኛ ሲገለጥ፥ ባስተማረን ቃላቱም ውስጥ ነው፡፡ ለምሳሌ በወንጌል አንድ ቦታ እንደ እባብ ልባም ደ'ሞ እንደ ርግብ የዋሃን ሁኑ ይለናል፡፡ ነገሩን ነጣጥለን ስናየው፥ መሬት ለመሬት የሚሳበው እባብና በአየር የምትሄደው ርግብ በብዙ የተለያዩ ናቸው (እንደ ፍጡርነት አንድ የሚሆኑባቸው እንዳለ ሆኖ)፡፡ በነርሱ አንጻር የተገለጡትም [ለብዙዎቻችን] በተዋሕዶ ለማስኬድ የተመቹ አይደሉም፡፡ ልባም ለመሆን ስንጥር የዋህነት ትኮስስብናለች፤ የዋህነትን ስናጎላት ልባምነት ትቀነጭርብናለች፡፡ ምክንያት? ሁለቱን በመጠባበቅ አንድ የምታደርጋቸው የፍቅር ጥበቧ የለችንምና፡፡

ከላይ እንደተገለጸው፥ ለምናውቀው ግን ለማንፈራው ሰው የተሰጡት ከታችኞቹ ጋር በትይዩ ሲዋሐዱ ፍቅርን ያስተረጉማሉ ፡፡ ከሁሉም (የምናውቃቸውም ሆነ የማውናቃቸው) ሰዎች ጋር በእውነት መውደድ ስንኖር፥ በነጻነት ያለ ጥንቃቄ፥ በአብሮነት የሚዘልቅ መከባበር፣ በመታገስ የማይደክም ትሕትና ገንዘባችን ይሆንልናል፡፡ እንበለ ፍቅር ካለን ግን መረን ነጻነት ጥንቃቄን ይንቅና ሰውን እናስቀይማለን፤ አብረን በኖርን ቁጥር ሆድ ለሆድ በመተዋወቅ ስም መከባበርን እናርቃለን፤ ትዕግሥትን ከትሕትና እንነጥላትና እየታበይን፣ እያስጨነቅን ታግሼ ኖርኩ እንላለን፡፡ እንደሚታወቀው፥ ፍቅር ክርስቶስ ነጻ አድርጎናል፥ ግን ደ'ሞ ስንጠብቀው የሚጠብቀንን ሕግንም ሰጥቶናል፡፡ በአንድነት ሳለችሁ አንዱ አንዱን ዘወትር ያገልግልም ሲል የትውውቅ ቆይታ ክብርን እንዳያደበዝዝብን በሐዋሪያት አንጻር ነግሮናል፡፡ ነፍሱን ስለነፍሳችን ሊሰጥ መከራ ሲቀበል ሥቃዩን ሲታገስ ኃይል እንደሌለው (ትሑት) ሆኖ ነው፡፡ ይሄ የሚረዳንና ወደ ሰዎችም የምናካፍለው ፍቅር ሲረዳን ይሆናል፡፡ አለበዚያ ነጻነት ጥንቃቄን እየተገዳደረብን፥ አብሮነት መከባበርን እያስረሳን፥ መታገስ ትሕትናን እየፈተነብን በሚያልፍ ኑሮ ውስጥ ተላልፈን እንኖራለን፡፡

@bemaleda_neku
403 viewsedited  06:43
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-11-02 14:26:21 ስለ ተዋሕዶ ስንነጋገር ሰውነትን ማዕከል ስላደረገ እውነት እያወራን ነው፡፡ ከጽንሰት እስከ ዕርገት ያለውን ሙሉ ጉባዔ በሕልውና ላይ የሚጽፍ የሰብአዊነት ብዕር ተዋሕዶ ይባላል፡፡ እርሱም 'አምላክ ሰው ሆነ፥ ሰውም አምላክ ሆነ' ብሎ በማመን የሚነበብ የሕይወት፣ የጥበብ መጽሐፍ ነው፡፡

በዚህ ጥበብ ውስጥ ጽኑ ፍቅር ከእውነት ጋር አለ፡፡ የተዋሕዶ አናት ላይ የሚያርፈው አስኬማ የተጠለፈው በመውደድ ክሮች ነው፡፡ ከገሊላ ተነሥቶ እስከ ቢታንያ የሚዘልቀው መንገድ ጠርዝና ጠርዙ የተሰመረው በፍቅር ልክ ነው፡፡ ፍቅርም ያለ ምንም ሚዛንና ምላሽ ራስን ያለ ቀሪ የመስጠት መሥዋዕትነት ነው፡፡

ዛሬ ዛሬ፥ መንፈሳዊነትን ከገነትና ከሲዖል፣ ከግል ጉዳይና መሰሉ ጋር የምናስተሳስር "ምእመናን" በዝተንባት እንጂ፥ በፍቅርና በእውነት ዓለት ላይ የቆመችው ተዋሕዶስ በግለሰብ፣ በዘመንና በታሪክ ላይ በደማቁ የሚመዘገብ እጅግ ያማሩ የሰውነት ኅብረ ቀለሞች ነበሯት/ አሏት፡፡

የአምላክ ልጅ የሰው ልጅ በመሆን ተዋሕዶ ባሕርያችንን አግኝቶት ለሁላችን ያስቀመጠልን የመኖር መመሪያ ሰው የመሆንን ምዕራፍ የሚተንተን ቃሉን ነው፡፡ በሰው ሕይወት በፍቅር የሚተረጎም እና በእውነት መንፈስ (ዕውቀት) የሚገለጥ ንጹሕ ቃሉን! ይሄንንም ቃል ከወንጌልና ከኑሮ ላይ የሚያነብ ሰው ስለ ስብእና ጥሩ ይገነዘባል፡፡

እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ያለው ጉዳይ በጠቅላላው ሰው ከመሆናችን ጋር በጥብቅ የተያያዘ ነው፡፡ ሰውነትም በፍቅርና እውነት መልክ የተቀረጸ ልዑል ፍጥረት ነው፡፡ አሁንም በብሉይ ዓለም ላለነው "አዳም ሆይ ወዴት ነህ?" በሚለው የገነቱ ፍለጋ በኩል ከዚህ ሰውነት ጠፍተን እንዳንቀር በየጊዜው ሕሊናችን ሆኖ ይጠራናል፡፡ በእርግጥ፥ ሰው ሆኖ ከሰውነት መጥፋት አለ፡፡ ነገሩን ሰው መስሎ መኖር ብንለው እንችላለን፡፡

አንድ ወቅት መድኃኒታችን ነገራችንን ትኩር ብሎ አየ፡፡ በትናንትም፣ በዛሬም፣ በነገም ውስጥ ተመለከተን፡፡ ለጥቆ እንዲህ አለ፦

"ወደ ጥፋት የሚወስደው ደጅ ሰፊ፥ መንገዱም ትልቅ ነውና፥ ወደ እርሱም የሚገቡ ብዙዎች ናቸው፤ ወደ ሕይወት የሚወስደው ደጅ የጠበበ፥ መንገዱም የቀጠነ ነውና፥ የሚያገኙትም ጥቂቶች ናቸው።" (ማቴ. 7፥14)

ጥቅሱ በተለያዩ የትርጉም አንድምታዎች ተተንትኖ ሊቀርብ ይችላል፡፡ ሀሳብ የያዝንበት ርእሳችን ስለ ሰው ልጅ ነውና ቃሉን በስብእና ክርታስ ጠቅልለን እናስቀምጠው፡፡

በፍቅር፣ በእውነት አዝርዕቶች የተሞላን እርሻ ዓለም አትወደውም፡፡ ምክንያቱም ዓለም ከእርሻው ባለቤት ጋር የተስማማች አይደለችም፡፡ ማለት፥ ምድራዊት፣ ሥጋዊት የአኗኗር ሥርዓታችን ከእግዚአብሔር አሳብ (አብ) ዘንድ አይደለችም፡፡ (1ኛ ዮሐ. 2፥16) እርሷ፥ ከፍቅር ትእዛዝና ከእውነት ሕግ ወጥተን ያመጣናት ጠቅላይ ስብስባችን ናት፡፡ ስለዚህ የተዘራባትን እሾህና (ጥላቻ) አሜኬላ (ሐሰት) እያበቀለች የእርሻውን ፍሬዎች አንቃ ታስቀራለች፡፡

የሰው ልጆች ለፍቅርና ለእውነት ቦታ ከሰጡ በሰውነት የተገለጠ የአምላክ ልጅ መንፈስ ማደሪያ እንደሚሆኑ፥ አሁን ሐዲስ ኪዳንን የሚዋጋው፥ ይሄን ዓለም በድክመቶቹ በኩል የሚዘውረው ክፉ ሥርዓት ያውቃል፡፡ ስለሆነ የእውነትና የፍቅርን ነገር ያለግብዝነት የሚያበረታቱ ማንነቶችን፣ ዕሴቶችን ያስጨንቃቸዋል፡፡ ይዋጋቸዋል፡፡ በላይኛው አንቀጽ ለመናገር ያህል፥ ጠላት እንክርዳዶችን በአምላክ እርሻ (ሰው) ላይ ይዘራል፡፡ በመሆኑም የምድር አስፓልቶች ስለ ፍቅርና ስለ እውነት የጠበቡ ናቸው፡፡ በእነርሱ ለሚያሸበርቅ ሥነ ሕይወትም ዓለም መተላለፊያዎቿን በሙሉ ሆነ ብላ ታቀጥነበታለች፡፡

በአንጻሩ ተቃራኒው ጎዳና ሰፋ ያለ ነው፡፡ ሰፋ ስላለ ብዙ ሰው ያስተናግዳል፡፡ የዓለም ብዙ ሰው፣ ርዕዮቱና ልማዱም ፍቅርና እውነትን ጥሎ ወደሚተምበት መሄድ እምብዛም አይከብድም፡፡ ጠባቧን ደጅ በአንድ ተቀጣሪ ግለሰብ የኑሮ ቁመት ስንለካት፥ መሥሪያ ቤት ያሉ አለቆችና ባልደረቦች ሲዋሹ፥ እውነትን ተናግራ፥ ሥራን እስከ ማጣት ድፍረት ድረስ ረዝማ፥ ትታየናለች፡፡ ለእንጀራ ሲሉ ማታለል፣ ለደስታ ሲሉ ማመፅ፣ ለጨዋታ ሲሉ መተማማት፣ ለስኬት ሲሉ መገፋፋት ያው ቀላል ነው፡፡ መሳደብ፣ መጥላት፣ መተቸት፣ መክዳት፣ መናቅ፣ መታበይ፣ መመቅኘት ብዙም አያስለፉ፡፡ በዚህ ትልቅ መንገድ የሚተላለፉ ተራማጆችም በርካታ ሲሆኑ፥ ክፉውን ለመጠቆም የሚቻኮሉ ጣቶችም በዝተው አሉ፡፡ ይልቅስ ግፊያ የማይገኝበት መስመር፥ ከአቤል መሥዋዕት ቀጥለን መባዕ ለማቅረብ ሰልፍ የምንይዝበት ደጉ መስመር ነው፡፡ ይሄ መስመር ግን ፊት የሚያጠቁር፥ አጥቁሮም ሳያበቃ በድንጋይ የሚወግር ቃየን አለበት፡፡

በታቦር ጫፍ ከመለኮት ጋር በአንድነት ያለ ትስብእት/ሰውነት በክብር በርቶአል፡፡ "የምወደው ልጄ ይህ ነው" የሚለው የሰማዩ ድምፅ ስለ ዳግማዊው አዳም ሲመሰክር ተጽፎአል፡፡ በዳግማዊው አዳም የቀዳማዊው አዳም ባሕርይ ተዋሕዶ አለ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ገንዘብ ያደረገው፥ መልካም እንደሆነ አስቀድሞ ታይቶ ከአምላክ ፈቃድ የተወለደውን የመጀመሪያውን ሰው ንጸሐ ባሕርይ ነው፡፡ ለዚህም ባሕርይ፥ ከላይ እንዳልነው ፍቅርና እውነት (አንድ ላይ ቅድስና) እርሱነቱ፣ መልኩ፣ መታወቂያው ነው፡፡ እናም፥ ለእኛ፥ በእምነት በሚታየው ሃይማኖታዊ አምልኮ በኩል የመጓዝ፥ መለኮት በሥጋ እንደመጣ የመታመን ጥጉ፥ እዚህ መታወቂያ፣ መልክ ላይ መድረስ ነው፡፡ ...

ለማንኛውም፥
በተዋሕዶ ካመንን፥
ያመንነውንም መኖር ከፈለግን፥
ሰውነትን ከየትኛውም መሥፈርት በፊት እናስቀምጠው፡፡ ሰውነት ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀምጦ እስኪነግሥ ድረስ በጥልቅ እንደተወደደ ስንተኛም ስንነቃም እናስታውስ፡፡ እንደዚህ እያስታወስን ከጫማ ይልቅ እግርን ለሚያከብር ውብ አመለካከት ዋጋ ይኑረን፡፡ ሰውነትን ወደ አውሬነት ከሚያወርድ የጥላቻ ከተማ እንውጣ፡፡ ይልቅስ እንስሳቱን ከአራዊቱ ያግባባች ኖኅነት መርከብን እንፈልጋት፡፡ ከያዕቆብ ማረፊያዎች አስበልጦ አምላክ በሚወዳት በጽዮን ታዛ ሥር ሁለመናችንን ለማስጠለል እንድከም፡፡ የቤተ እምነትን ሕንፃና ተያያዦቹን ለማሠራት ያለንን ስናወጣ፥ ጎዳና የሚያስተዳድረውን ወገን ለመደገፍ እንዲሁ ፍቅር እናዋጣ፡፡ ደ'ሞ ኢትዮጲያውያን ተዋሕዶን ስንሰማት ኦሪትን ሳንለቅ ነው፡፡ በጉን ስንቀበል ሙሴን አልተውንምና የሁለቱንም ቅኔ አንድ'ጋ እንዘምራለን፡፡ በዚህ መዝሙር ውስጥ በብሉይም ሆነ ሐዲሱ አለን፡፡ አሮጌውን ከአዲሱ እያወጣን የምንጽፈውም ለዚህ ነው፡፡ ኪዳናችን በእንጨትም በልብም የተጻፈ ነው፡፡ እህሳ ታቦት ተሸክመን ሰውን አንጥልም፡፡ እስቲ ተዋሕዶን ለመዋሐድ የአንድነት ኃይል ፍቅርን እንድመቅባት! እውነትን እንጠመቃት! በፍቅር ባለ በእውነት ቃል በተሠራ ማንነት አብና ወልድ መጥተው ያድራሉ፡፡ ከእነርሱ የተነሣም መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ዓለም ቦታ ሆኖ ይሠራበታል፡፡ የተነገረውን ያጸናለታል፤ ዕውቀት ይገልጥለታል፤ የሚመጣውንም ያሳስበዋል፡፡ በዚህ ስለዚህ የሰው መንፈስ የእግዚአብሔር ብርሃን ስለመሆኑ ለሚያገኙት ሁሉ ያስረግጥላቸዋል፡፡

@bemaleda_neku
975 views11:26
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-10-28 22:35:04 የአንድ ሰው ጥያቄ ፦ ለምንድነው እግዚአብሔር ግን ራሱን የማይገልጥልን? ተገልጦ ቢያሳውቀን እኮ የምናያቸው ሁሉ እንደምናያቸው አይሆኑም ነበር:: ስለምን ነው ለሁሉም ሰዎች ሁሉን ግልጥልጥ የማያደርግላቸው?

የአንድ ሰው መልስ ፦ የትኛው ንባብ ላይ እንደሚገኝ አሁን የማላስታውሰው መልካም ቃል "የሰው ኅሊና ወደ ደግ ነገር ሳትሳብ የእግዚአብሔር ጸጋ ሰውን አትረዳውም" ይላል:: አብርሃም አምላክን የገለጠበትን ታሪክ ሲያስረዱ ነው ይህንን ያሉት:: ዝርዝሩን ወደኋላ እናመጣዋለን:: እንግዲህ የማምነውን ዕውቀት ነው የምነግርህ:: ..እግዚአብሔር በየዕለቱ ራሱን ለሰው ልጆች ይገልጣል:: መገለጡ ያልተገለጠልን ለኛ ነው:: በምሳሌ ላስረዳህ:: ፀሐይ ወጥታ ሳለ በጨለማ ቤቱ ተክትቶ ያለ ሰው ፀሐይ የለችም ቢል: እውነቱ አለማየቱ እንጂ የፀሐይ አለመውጣቷ አይደለም:: ብርሃኗን ሊያይ ከወደደ ቢያንስ መስኮቱን መክፈት አለበት:: የአንተ ጥያቄ አንድ በመጽሐፍ ቅዱስ በተጻፈ ባለጠጋ ሲጠየቅ አንብቤያለሁ:: እስቲ ሉቃስ 16'ን ተመልከተው:: [1] ኑሮ ደስ ያለው ሐብታም ሰውና በድህነት፣ ሳይበቃው በቁስልም የሚሠቃይ ሰው ታሪክ ታገኛለህ:: ያው ሞት አይቀርምና ሁለቱም ከዚች ዓለም አረፉ (በርግጥ አልዓዛር የሚባለው፣ ደሃው ነው ያረፈው):: ነገሩን ላሳጥረውና ሐብታሙ ወደ ሲዖል የተቸገረው ወደ ሕፀነ አብርሃም በነፍሳቸው ሄዱ:: ባለጠጋው የወኅኒ ቤት መከራ ሲጸናበት እዛው ሆኖ ጸለየ አሉ:: ረፍዷል ተባለ:: እሺ ቢያንስ ቤተሰቦቼን እንደኔ እንዳይዘገዩ አስጠንቅቁልኝ አለ፤ ሙሴና (ሕግ) ነቢያት (ትምህርት) አሏቸው እነርሱን ይስሙ የሚል መልስ ተሰጠው:: አይደለም፥ ሙታን ተነሥተው ቢመክሩልኝ ይሻላል አለ (የጨነቀው!):: ሙሴና ነብዮቹን ካላደመጡ ሙታኑን አይሰሙም ተብሎም ቁርጡ ተነገረው:: ልብ ካልክልኝ የመጨረሻይቱ ቃሉ ያንተ የጥያቄ ሐሳብ ነው:: የሙታን ትንሣኤ ይመስክርልኝ ያስባለው ከቃል የተሻለን መገለጥ ሲመርጥ እንደሆነ አስተውልሃል? ትምህርት አይጨበጥማ:: የትምህርት መገለጥ ለዓይን አይደለም፤ ለልብ ነው:: ቤተሰዎቹ ዓይን እንጂ ልብ እንደሌላቸው ያውቃል ማለት ነው:: ..እግዚአብሔር የመጨረሻውና ፍጹሙ ደግ ባሕርይ ነው:: ዘመናትን አላንዳች ምልክት አይተዋቸውም:: ሰዎችን እንዳሉበት ልዕልና ማናገሩን ለደቂቃ አልተወም:: ለምሳሌ አንተ ከቤት ወጥተህ እስክትመለስ ምን ያህል በጎ ሰዓታትን አሳለፍክ? በእርምጃዎችህ ገለል ብለህ ያለፍካቸው አልዓዛሮች የሉም? ምናልባት ደምቆ የተጻፈ ጽሑፍ እያነበብህ አላየኻቸው ይሆናል:: በዓይንህ ብቻ የምታይ ከሆነ: የሕንፃ ቀለም በመንገድ ከተኮራመቱ ወገኖች በላይ ትኩረት ይወስድብሃል:: 'ነርቩ' ከልቡ'ጋ ያልተገናኘለት ብሌን ከውበት አስተርፎ ሊመለከት አይችልም:: ይህንን ነው የሰው ኅሊና ለደግነት ሳትሳብ የእግዚአብሔር ጸጋ ሰውን አትስበውም የሚሉህ:: ለባለጠጋው ሰውየ ረፍዶብሃል የሚለው አብርሃም ነበረ:: እርሱ ከአባቱ ቤት ሳለ የቀዬውን ጣዖት ይቀርጽ ነበር አሉ:: [2] የኋላ የኋላ በእጁ የሠራው ሥራ እኔንም ሠርቶኛል ብሎ መቀበል ስላቅ ሆነበት:: አፍንጫውን የማረዝም የማሳጥርለት ይሄ እንዴት አፍንጫዬን ቀረጸልኝ? ሲል ተመራመረው:: አሁንም ልብ በል! ይሄን የአብርሃምን ጥያቄ ሌሎቹ እንዳይጠይቁ አልታፈኑም:: ግን እርሱ ብቻ ጠየቀ:: በሌላ አባባል እርሱ ብቻ መስኮት ከፈተ:: ስለዚህ የከፈተውን ያህል ብርሃን አየ:: ኅሊናው ጣዖቱን ናቀበት:: ተውም ቢለው በጄ አላለለትም:: በቃ ይሄ እኮ ነው መገለጥ ማለት! እንዳልኩህ እግዚአብሔር በየቀኑ የሚከፍትልን አንድ የሆነ በር አለ:: ይሄ ግን የሚገባን ልቡናችንን ስንከፍት ነው:: ይኸውም ጥልቅ ፍላጎት ነው:: አብርሃም ጣዖቱን ሰበረው:: በእጁ የሰበረው በኅሊናው ከሰበረው በኋላ እንደሆነ ያዝልኝ:: ስለዚህ ጸጋ እግዚአብሔር በልቡናው አድራ እርሱን ወደ መፈለግ መራችው:: ፍለጋውን ጀመረ:: ከግዙፉ ተራራ ጀመረ:: ሌላ የገዘፈ ተራራ ተመለከተና የቀደመ ሐሳቡን ተወው:: ወደ ባሕር ቀጠለ:: እያንዳንዱ እያነሳ የሚጥለው ፍጥረት ወደ ፈጣሪ ያስጠጋው ነበረ:: አግኝተኸኝ ከሆነ: አብርሃም የአምላክን መኖር ነበር የፈለገው:: አለመኖሩን ቢፈልግ ኖሮ የፍለጋ ውጤቶቹ ጉዞውን ለማቋረጥ በቂ ምክንያቶች ነበሩ:: ለካ ጽኑ ፍላጎት አለመሳካትን ሂደት እንጂ ገደብ አያደርገውም:: በጣም ለምትሻው ነገር አለመመቸትን ጆሮ ዳባ ልበስ ትለዋለህ:: ነጮቹ ስለዚህ 'ፍላጎት እኮ ኃይል ነው' ይላሉ:: ቅን ፍላጎት ወደ አምላክ የሚመራ መንገድ ነው:: አብርሃምን: በእያንዳንዱ የፍላጎት እርምጃዎቹ በኩል ጌታ ይቀርበው ነበር:: ይህን የምታውቀው የአብርሃም አፈላለጉ እየረቀቀ መሄዱን ካጤንክ ነው:: ከሚታዩት ወደ ማይታዩት እየረቀቀ ሄዷል:: ብርሃን፣ ነፋስ፣.. እያለ ወደማይጨበጡት ፍለጋው ተጉዟል:: ቅን ፍላጎት ወደ አምላክ ትወስዳለች:: እርሱም'ኮ ፈልጉ ታገኙማላችሁ ብሏል:: [3] ፈልጉ ሲል እኔንም ፈልጉኝ ይጨምራል:: ከፍላጎት ትይዩ ታገኛላችሁ ደሞ ካለ: እናገኘው ዘንድ አስቀድሞ ያኖረው አንዳች ነገር አለ ማለት ነው:: ሳይንስ አፈላለጉ ጥሩ ነው:: አነሳሱ ግን አይደለምና ከባክቴርያ የሚረ'ቀው 'አተም' ነው አለ:: በመሠረቱ አንድን ነገር በዓይንህ ካየኸው አልረቀቀም ማለት ነው:: እና በሥጋ ለሚታዩህ እምብዛም አትደከም ወንድሜ:: ጳውሎስ የሚባል ሰው "የማይታየው ባሕርይ እርሱም የዘላለም ኃይሉ ደግሞም አምላክነቱ ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሠሩት ታውቆ ግልጥ ሆኖ ይታያልና፤ ስለዚህም እግዚአብሔርን እያወቁ እንደ እግዚአብሔርነቱ መጠን ስላላከበሩትና ስላላመሰገኑት የሚያመካኙት አጡ፤ ነገር ግን በአሳባቸው ከንቱ ሆኑ የማያስተውለውም ልባቸው ጨለመ" እያለ ይናገራል:: [4] "የማይታየው.. ይታያልና.. ነገር ግን.. ልቡናቸው ጨለመ" ያላቸውን አሰናስለህ አስተውልልኝ:: ልብ ነው ከነፋስ የሚረቀውን የሚያየው:: እርሱ ከታወረ የማይታየው ባለመታየቱ ይቀጥላል:: ወዳጄ "አጥብቀህ ልብህን ጠብቅ፥ የሕይወት መውጫ ከእርሱ ነውና":: [5] .. በል ሰንብትልኝ!

[1] ሉቃ. 16፥19-31
[2] ኦሪት ዘልደት ም. 12 አንድምታ
[3] ማቴ. 7፥7
[4] ሮሜ. 1፥20-21
[5] ምሳ. 4፥23


( ለአቀራረብ የተሞረደ እውነተኛ ቃለ ምልልስ )

@bemaleda_neku
3.6K views19:35
ክፈት / አስተያየት ይስጡ