Get Mystery Box with random crypto!

በማለዳ ንቁ !

የቴሌግራም ቻናል አርማ bemaleda_neku — በማለዳ ንቁ !
የቴሌግራም ቻናል አርማ bemaleda_neku — በማለዳ ንቁ !
የሰርጥ አድራሻ: @bemaleda_neku
ምድቦች: ሃይማኖት
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 18.24K
የሰርጥ መግለጫ

(2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች ምዕ. 13)
----------
11፤ በቀረውስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ደኅና ሁኑ። ፍጹማን ሁኑ፥ ምክሬን ስሙ፥ በአንድ ልብ ሁኑ፥ በሰላም ኑሩ፥ የፍቅርና የሰላምም አምላክ ከእናንተ ጋር ይሆናል።
14፤ የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ኅብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን። አሜን፡፡
@bemaledaa_neku_bot

Ratings & Reviews

2.33

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

0

3 stars

1

2 stars

2

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 3

2022-10-27 10:31:37 ንሕነሰ ሕሊናሁ ለክርስቶስ ብነ

አስተሳሰባችን ከ-እስከ ዛሬ ትናንታችን ጋር ይያያዛል፡፡ መጽሐፈ ኢዮብ "እኛ የትናንት ነን" እንዳለ፡፡ የሰው ትናንቱ ደ'ሞ እንደየታሪኩ ይለያያል፡፡ ክርስቶስ ወደኛ የመጣው ይህን መለያየት ከእኛ ይለይልን ዘንድ ነው፡፡ እንዴት?

ብሉይቱ ዘመን ለዛሬይቱ ሐዲስ ዘመን መሠረት የሆነች ትናንት ናት፡፡ እንደትናንትነቷ፥ አልፋለች፡፡ ትናንታችን አስተሳሰባችን ነው ብለናል፡፡ በትናንቶቻችን ውስጥ ስናውቅ እንደመጣነው፥ ዛሬን እናያለን፣ እንተረጉማለን፣ እንገነዘባለን፣ ማንነታችንን እንገልጻለን፡፡ ይሄ ከማንኛውም ፍጥረታዊ/አዳማዊ ሰው የተጠበቀ ጤናማ አስተሳሰብ ነው፡፡

በሽታው የሚመጣው፥ በእኔ ትናንት ዛሬህን ኑር የሚል ጉልበተኛ የሚኖር ሲሆን ነው፡፡ ይኸውም በአሁኑ አማርኛ ጽንፈኛ ይባላል፡፡ የጽንፈኝነት ክፋቱ፥ የእርሱ ትናንቱ ለሁሉም እስኪሆን ማስገደዱ ነው፡፡ ጽንፈኛ ሰው፥ ሁሉም ሰው የራሱ ትናንት እንዳለው አይገባውም፡፡ ሰው በራሱ ትናንት ውስጥ የእኔ የሚለው እውነት አለው፡፡ የዚህ እውነቱ ጥቅል፥ በእስከዛሬው የጊዜ መስመር ውስጥ ያለው እምነቱ፣ ዕውቀቱ፣ ባሕሉ፣ ዕሴቱ ሁሉ ነው፡፡ ጽንፈኝነት ይሄ አይረዳውም፡፡ ሁሉ እንደኔ ካላወቀ፣ እንደኔ ካላሰበ ይላል፡፡ በአጭሩ በሃይማኖትም ሆነ በፖለቲካውም ሆነ በሌላው ውስብስብ ስብስብ ውስጥ ያለው የብሉዩ ዓለም ትልቁ በሽታ ይሄ ነው፡፡

ዝርዝሩን ለማሳጠር ያህል፥ ሐዲስ ዘመንን ያስገኘ መድኃኒት ክርስቶስ፥ በመንገድነቱ፣ በእውነትነቱ፣ በሕይወትነቱ በኩል ከዚህ ብሉይ በሽታ እየፈወሰ ወደ አባቱ ይወስደናል፡፡ በተለመደው አገላለጽ፥ የሰው ልጅ የሆነውን የእግዚአብሔር ልጅ በመምሰል የሕይወት ሂደት በኩል የክርስቲያን ታላላቆች ጴጥሮስና ጳውሎስ ወዳመለከቱን የመጨረሻ ዕድገት፥ ማለትም ሱታፌ አምላክነት፥ እንገሰግሳለን፡፡ በዚህም ከፍታ ሳለን "እኛ ግን የክርስቶስ ልብ አለን፡፡ - ንሕነሰ ሕሊናሁ ለክርስቶስ ብነ፡፡" እንላለን፡፡ (1ኛ ቆሮ. 2፥16)

የክርስቶስ ልብ ያለው ጠቅላዩ አስተሳሰብ አለው፡፡ እርሱም አብ ነው፡፡ በአብ ልብነት ያለ ዕውቀት ሁሉን የሚያውቅ በምልዓት ያለ ዕውቀት ነው፡፡ ከጊዜና ከቦታ አጥር ውጪ ስለሆነ በትናንት ምክንያትነት አይወሰንም፡፡ ከዚህ ዕውቀት በጸጋ የተካፈሉ ሰዎች፥ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ፈቃዳቸው ነው፡፡ እነርሱ በእነርሱ ውስጥ የሉም፡፡ በእነርሱ የሚያየው፣ የሚሰማው፣ የሚሠራው እርሱ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ስለዚህ ለሁሉ እንደሁሉ የሚሰማውን ድምፅ ይናገራሉ፡፡ የሰውን ትናንት በክፉ ሳይገፉ ከትናንት ውጪ የሆነ ዕውቀታቸውን ወደሰው ትናንት ገብተው ያሰደምጣሉ፡፡

እነዚህ ሰዎች፥ የሰውን ድካሙን ያውቃሉ፡፡ በመሆኑ እስከ ሰው ድካሙ ታች ወርደው፥ ሰውን ያግዛሉ፡፡ በሌላ አባባል አስተሳሰቦችን ሁሉ እንዳሉበት ልዕልና ያስተናግዳሉ፡፡ ሲሆን፥ ከፍ እንዲሉ፥ ያልታረመ ያርማሉ፤ የታረመን ያጸናሉ፡፡ ካልሆነ፥ ክፍተትን ይሸፍናሉ፤ ውድቀትን ያነሣሉ፡፡ እንግዲህ አገር የተስፋይቱን ምድር የምታገኘው፥ እንዲህ ያሉ አምላክ ዘበጸጋዎች የበዙ እንደሆነ ነው፡፡

ስለዚህ?
እግዚአብሔር ዓለምን በጠቀለለበት በአንድያ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በእውነት የምናምን ሁላችን፥ እንደቆምንበት ብቻ ሳይሆን እንደቆሙበት ማየትን እናይ ዘንድ እግዚአብሔርን የመምሰል ታላቅ ምሥጢር ክርስትናን በእውነት እንኑረው፡፡ እስክንበቃ ድረስ አዘውትረን እንኑረው፡፡ ስናሰላስል፥ እንደሌሎችም ለሌሎችም እናሰላስል ዘንድ፤ ስናዳምጥ፥ የሌሎችንም እውነት እንረዳ ዘንድ፤ ስንናገር፥ ለሌሎችም የሚሆን ቃል እናወራ ዘንድ፤ በልዩነት ባለች ኅብረት አንድነትንም እናመጣ ዘንድ፤ ልቡን ለሰጠን አምላክ ልባችንን እንሰጠው፡፡

"ልጄ ሆይ፥ ልብህን ስጠኝ፥ ዓይኖችህም መንገዴን ይውደዱ፤" (ምሳ. 23፥26)

@bemaleda_neku
4.8K viewsedited  07:31
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-10-18 21:13:05 ጳውሎስ ፦

(2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች ምዕ. 6)
----------
3፤ አገልግሎታችንም እንዳይነቀፍ በአንዳች ነገር ማሰናከያ ከቶ አንሰጥም።
4፤ ነገር ግን በሁሉ እንደ እግዚአብሔር አገልጋዮች ራሳችንን እናማጥናለን፤
5፤ በብዙ መጽናት፥ በመከራ፥ በችግር፥ በጭንቀት፥ በመገረፍ፥ በወኅኒ፥ በሁከት፥ በድካም፥ እንቅልፍ በማጣት፥
6፤ በመጦም፥ በንጽህና፥ በእውቀት፥ በትዕግሥት፥ በቸርነት፥ በመንፈስ ቅዱስ፥ ግብዝነት በሌለው ፍቅር፥ በእውነት ቃል፥
7፤ በእግዚአብሔር ኃይል፥ ለቀኝና ለግራ በሚሆን በጽድቅ የጦር ዕቃ፥ በክብርና በውርደት፥
8፤ በክፉ ወሬና በመልካም ወሬ ራሳችንን እናማጥናለን፤ አሳቾች ስንባል እውነተኞች ነን፤
9፤ ያልታወቁ ስንባል የታወቅን ነን፤ የምንሞት ስንመስል እነሆ ሕያዋን ነን፤ የተቀጣን ስንሆን አንገደልም፤
10፤ ኀዘንተኞች ስንሆን ዘወትር ደስ ይለናል፤ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን ባለ ጠጎች እናደርጋለን፤ አንዳች የሌለን ስንሆን ሁሉ የእኛ ነው።


@bemaleda_neku
8.8K views18:13
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-10-15 19:03:15 4.  ሌላው የውጊያውን ትምህርት በአንድም በሌላም የሚቃወሙ፥ በተለይ መምህራኑን የሚያጥላሉ ሰዎችን ሲሆን መርዳት ካልተቻለ መረዳት ሲቻል፥ በቀጥታ ደብተራ፣ ሰይጣን፣ ጠንቋይ፣.. እያሉ በማኅበራዊ ሚዲያ አስተያየቶች ላይ መሳደብ የተለመደ፣ ጤናማ ሆኗል፡፡ እንዴት ነው ነገሩ? ይሄን የተማርነው ከማነው? ደብተራስ ማለት ምን ማለት ነው? ሰፊ ትርጉም የያዘ መጽሐፍ ቅድሳዊ፣ ትውፊታዊ ትርጉም እንዳለው እናውቃለን? ..አንድ ሰው በሰይጣን፣ በጋኔን ተይዞ ነው መልካም የማይናገረው ብለን ካመንን፥ ይሄን እምነት እንደምን ባለ ቅንነትና አስተዋይነት ነው የምንገልጠው? የሚያሳድዱአችሁን አሳድዱ ከየትኛው ወንጌል የተነበበ ነው? የሚረግሙአችሁን በእጥፍ እርገሙ በስንተኛው የመጽሐፍ ምዕራፍና ቁጥር ያለ ነው? ደ'ሞስ በእርግጥ ሁሉ ተቃውሞ ማለት የሰይጣን ማለት ነው? ለምሳሌ፥ በአንደኝነት ተራ የተጠቀሰውን፥ በፈውስና በመዳን መካከል ያለውን በተመለከተ የሚሰነዘሩ ትችቶች ግለሰባዊ መልክ ባይይዙ ፍቅርን ቢይይዙ ኖሮ አግባብነት ያላቸው ነበሩ፡፡ ሒሶቹ ተጣመው ቢመጡ እንኳ እኛ አቃንተን መስማት ይገባን ነበር፡፡ ሊታመን የሚችለውን መስማት ደ'ሞ ጳውሎስ እንደሚለው በእግዚአብሔር ቃል በኩል ነው (ሮሜ. 10፡17)፡፡ ግን በሁለተኛው ላይ እንደተገለጸው፥ የወንጌል ፍቅር፣ ንባብ ስለሌለን፥ የምንሰማውን ሁሉ በምን ቃል አንጻርነት እንደምንሰማው የሚመራ መመሪያ የለንም፡፡ ስለዚህ በደፈናው፥ የተቸ ሁሉ ከሰይጣን ነው፡፡ የነቀፈ ሁሉ መተተኛ ነው፡፡ ቆይ፥ ስለ ውጊያው ያልገባቸው የምንላቸውን ስድብ፣ ንቀት፣ እናንተ አትሰግዱም አትጸልዩም እኛ ግን ዓይነት ድምፀት ያለው አነጋገር እያሰማናቸው እንዴት በበጎ ኅሊና እንዲወያዩን እንጠብቃለን? ጌታ "ጽድቃችሁ ከፈሪሳውያንና ከጻፎች ካልበለጠ ከቶ መንግሥተ ሰማያት አትገቡም" አለ፡፡ ታዲያ ክፉ ደጉን በሆነ ልክ በነሮአቸው የቀን ቀን ትንንቅ ምክንያትነት ለይተዋል የተባሉ ምእመናን ካለዩት ያልተሻለ አስተሳሰብ፣ ጠባይ፣ አኗኗር ካሳዩ፥ እንዴት ነው ነገሩ? ..ከዚህ ጋር በተያያዘ መምህራኑም ብትሆኑ ስለተቃዋሚዎች የምታነሱበትን አገላለጽ በጣም ፈትሹ፡፡ የሚሰማችሁ ብዙ ነውና ጥንቃቄ በእያንዳንዱ ትምህርት አሰጣጣችሁ ላይ አይለያችሁ፡፡ ለምሳሌ ደብተራ የሚል ቃል ስትጠቀሙ ምንነቱን አስቀድሞ ማብራራትም ይጠበቅባቸዋል፡፡ ደብተራ ኦሪት ምንድነው? ደባትራን/አገልጋዮች ምንድናቸው? በመጽሐፍ፣ በታሪክ ከየት መጡ? አረማዊ ደብተራ የሚባሉት የተለዩት በምን መለኪያ፣ መስፈርት ነው? ..ይሄን ይሄን አሳውቁ፡፡ ማሳወቅ የማትችሉ የማታውቁትን አታስተላልፉ፡፡ የኢትዮጲያውያንም ጥልቅ ምርምር፣ ዕውቀት የሆነውን ሥነ ፈለክን በደምሳሳው የአጋንንት ነው የሚሉ ነገረ ሰይጣን ተንታኞችን ሰምቼ አዝኛለሁ፡፡ ሁሉን መርምሩ መልካሙን ያዙ የት ገባ? ሳይላመጥ መዋጥስ ከየት ተለመደ? ..እንዲሁ ራሳችሁን ሳታበቁና በአስተውሎት ጸጋ ሳትባረኩ ትምህርት የምትሰጡ አምላክ ባወቀ ለምን እንደምላችሁ ጠንቀቅ እያላችሁ፡፡ መረጃ ስትለቁ ከተለያየ አቅጣጫ አጠናክራችሁና ቢቻል የጸሎት ጊዜ ወስዳችሁ ይሁን፡፡ ካልሆነ ወደ ጭንቅላታቸው የሚሮጡ ድምፆችን ሳያሳርፉ የሚያወጡ ሰዎች በብዙ አብዝተን፥ ስለ መንፈስ ተምረው መንፈስ የሆኑ አመለካከቶችን እንዳናበርክት ያሰጋል፡፡ በእውነት ይታሰብበት! ..በጤና ያክርመን!

@bemaleda_neku
9.6K viewsedited  16:03
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-10-15 18:59:58 የመናፍስት ውጊያ ትምህርት ወዴት እየሄደ ነው? እንዴት ነው ነገሩ?

1.  መናፍስት ፈታኞች ናቸው፡፡ ያስቸግራሉ፣ ያስጨንቃሉ፡፡ የፈተናቸውን ስልት ላላወቀባቸው ደ'ሞ የበለጠ ውስብስብና ምሬት ያልተለየው ኑሮ ኗሪ ያደርጋሉ፡፡ ..ያው ይታወቃል፡፡ ሰው ከጤና ጉዳይ ጀምሮ በተለያየ ዓይነት ችግር ውስጥ አለ፡፡ ሰለዚህ መፍትሔን በጥብቅ ይፈልጋል፡፡ ፈልጎ ያገኝም ዘንድ የተቸገረውን ያህል ዋጋ፣ ድካም ይከፍላል፡፡ ..የውጊያው ዓለም ትምህርት ይሄን ተፈላጊ መፍትሔ ለብዙ ወጣንያን ይሰጣል፤ ሰጥቷልም፡፡ ይሄ የሕይወት ምስክርነት ያለው እውነት ነው፡፡ ..ይሄ እውነት ግን በጥልቅ እውቀት እየተደገፈ አይደለምና፥ የሚመለከታቸው መምህራን የሰዉን አዝማሚያና ግንዛቤ እያስተዋሉ አይደለምና፥ ሰዉም በተቸገረው መጠን ያህል መጥኖ ይሰማልና፥ የትኅርምቱ ሕይወት ሊገሰግስ ከሚገባው [ቢያንስ ሁሉም አማንያን ሊደርሱበት ግድ ከሚለው ከመንፈስ ፍሬያት (ገላ. 5፥22)] መድረሻ፥ ሥጋዊ ክፍተቶቻቸውን ሊሞሉ በሚታገሉ አስተሳሰቦች አቅጣጫ እየሳተ ይስተዋላል (ከፍተኛ የጤናና መሰል ስቃይ ውስጥ ያሉ፣ በበዛ የዋህነት በልባቸው ብቻ የሚመላለሱ፣ በመጽሐፍ አገላለጽ ብዙ ሆነው እረኛ እንደሌላቸው በጎች ተጥለው ተጨንቀው የታዩ ከዚህ አይመደቡም፡፡ እነዚህ ክርስቶስ "በሰላም ሂዱ" እያለ ፈውስን የሰጣቸው ምስኪናን የወንጌል ሰዎች ምሳሌዎች ናቸው፡፡ በቃ ለነርሱ ክርስቶስ ከደዌያቸው ባሻገር የሚታወቅ አይደለም፡፡ እንዲሁ የተደረገላቸውን እያመሰገኑ በበረከቱ ሊኖሩ፣ ሊጠበቁ የተተዉ ናቸው፡፡) እንዴት ነው ነገሩ? የሚሰግዱ ግን ፍቅር ግድ የማይሰጣቸው፥ ጸሎት ቤት ያላቸው ግን በየቀኑ የሚያድግ ትሕትና የሌላቸው፥ ጾም ሱባዔን ከቀደመ አመል ጋር የሚይይዙ፥ ስለ ሰይጣነ ጸሪፍ ተምረው ወዲህ የሚሳደቡ፣ ስድቡም ሲያልፍ ጸጸት በኅሊናቸው የማያልፍ፥ ሃይማኖትን በኑሮአቸው ካለ ችግር አንጻር ብቻ ስለሚኖሩ በመንፈሳዊ ስብዕና የማይኖሩ ምእመናን አሳሳቢ በሆነ ብዛትና ፍጥነት ሲጨምሩ ይታያል፡፡ በድጋሚ፥ እንዴት ነው ነገሩ ?

2.  ስለ ክፉ መናፍስት በሚገባ ማወቅ፣ እነርሱን ስለሚከላከሉበት ስለሚያጠቁበት ስለመንፈሳውያን ጦር ዕቃ ማወቅ፥ ከቀደመ፣ ካለና ከሚኖር ችግር ያላቅቃል ሲሆን ይጠብቃል፡፡ በተጨማሪ፥ ከስውራኑ የጽድቅ ጠላቶች ጋር የመታገሉ ሂደት በራሱ የሚያስተምራቸው፣ የሚያስተዋውቃቸው ለውጦች፣ ትሩፋቶች አሉ፡፡ መልካም! ..ይሄ ግን ራሱ ውጊያን ጨምሮ የእግዚአብሔርን ዘላለማዊ ፈቃድ የምትገልጠው፥ ሰዎችን በጥበብ፣ በቃል አዲስ ስብዕና አድርጋ በምትወልደው ወንጌል ሊደገፍ፣ ሊመሠረትና ሊመራ ይገባዋል፡፡ በአጭር ቋንቋ፥ ወንጌልን፥ እንደ ፖለቲካው ዓለም የሙግት፣ የመነቃቀፍ ይዘት ከሌላቸው ስብከቶች፣ መጽሐፍትና ልቡና በጥልቅ መሻትና ትጋት በተቻለ አቅም መማር ወደ ክርስቶስ ራስ ለማደግ ከሚፈልጉ ሁሉ ይጠበቃል፡፡ ..አሁን አሁን ስለመናፍስት በአንድም በሌላም የማያነሳሱ መንፈሳዊ ትምህርቶች ተከታታይ ሲያጡ ይታያል፡፡ ገና ወደ ውጊያው ያለመጡት ቢሆኑ እሺ! እነዚህ ገና ትሩፋትን በመለማመድ፣ የዓለምን ተቃዋሚ ጠባይ በመለየት፣ መሠረታዊ የሚባሉ የተግባር ትምህርቶችን በመረዳት ላይ ስላሉ ይታለፋሉ፡፡ ሰንበትበት ያሉት ግን፥.. ለነገሩ መች የወጣንያኑን የውጊያ ዓለም በቅጡ ተረዳነውና? ከላይ እንደተባለው የምንሰማው የምናነበው እስከተቸገርነው ርቀት ስለሆነ የትኅርምቱን ኑሮ ራሱ አልተረዳነውም፡፡ ዘላለማዊነት ምንድን ነው? ትንሣኤ ምንድነው? በመከራ መራቀቅ ምንድነው? ክርስቶስን መምሰል ምንድነው? በመንፈሳዊነት ሥር ሰዶ መታነጽ ምንድነው? ዐሥሩ ማዕረጋት ምንድናቸው? በመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት መጠመቅ ምንድነው? ሱታፌ አምላክ ምንድነው? የበዓለ ኅምሳ ኃይል ምንድነው? ..ለብዙዎቻችን ያልታወቁ ናቸው፡፡ በትጋት መጽሐፍትን ማንበብ፣ በጥሞና ነገራትን ማስተዋል፣ መንፈሳዊ ምርመራዎችን በመውደድ ማካሄድ፣ ራስን ደረጃ በደረጃ ማብቃት.. ተዘግቷል፡፡ የዛሬ 8 ዓመት ስለሰማነው ዓይነጥላ፣ ቡዳ፣.. ዛሬም እንደ አዲስ እንሰማለን፡፡ እነርሱ ዙሪያ ያለውጤት እንከራከራለን፡፡ ሌላው ይቅር፥ ስለነርሱም ወይ ጠልቀን ማወቅም አንድ ነገር ነበር፡፡ መናፍስት የግለሰቦችን፣ የማኅበረሰቦችን፣ የሀገራትን ታሪክ፣ ባሕል፣ ልማድ፣ አኗኗር ተከትለው የሚሰሩ የሚንቀሳቀሱ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ባሕር ማዶ ዓይነጥላ የሚባል ነገር ከነጭራሹም አይታወቅም፡፡ በዚህ ስያሜ እዚህ የታወቀው መንፈስ ሌላ ቦታ በሌላ ስያሜ በሌላ ጠባይና ስልት ያደርጋል ያከናውናል፡፡ እኛ ተግድበን አለን፡፡ በተለይ ማንበብ፣ ማስተዋል፣ .. የሉም እስኪባል መንምነዋል፡፡ የማያነብ፣ የማያስተውል፣ የጥሞና ጊዜያትን የማይፈልግ፣ ዕለቱን በየዕለቱ የማይመረምር ደ'ሞ ለውጥን አሰናብቷታል፡፡ የአስተሳሰብ ጥልቀትን አፍኗታል፡፡ እንዴት ነው ነገሩ?

3.  እግዚአብሔር ያስፈጽመኝ የጀመርኩት መጽሐፍ ላይ ከማነሳቸው ሐሳቦች መካከል በሰው ልጅ ፈቃድና በመናፍስት ተጽዕኖ ዙረያ ያለው አንዱ ነው፡፡ ምንድነው ፈቃድ? ፈቃድን ፈቃድ የሚያሰኘው ምንድነው? ፍላጎት፣ ምኞት፣ ውሳኔ፣ ዓላማ፣.. እነዚህ ከፈቃድ ጋር በምን ተያያዙ?.. የሚሉትን የሚመልሱ አንቀጾች ይኖሩኛል፡፡ ይሄ የተነሣበት መሠረታዊ ምክያት፥ የውጊያውን ትምህርት የሚቃወሙ ሰዎች አንዱ መከራከሪያቸው "መናፍስት ሰውን ይቆጣጠራል አይባልም፡፡ እነርሱ ፈቃድን ሊነኩ አይችሉም፡፡" የሚለው ነው፡፡ በእርግጥ የ'ይቆጣጠራል' ቃሉ አበያየኑን እናቆየውና በመጽሐፍ ጽንሰ ሐሳብነት ልክ ናቸው፡፡ እንኳን መናፍስት እግዚአብሔርም ፈቃድን አይነካም፡፡ ልትድን ትወዳለህን? የሚል ጥያቄ የምንጠየቀውም ለዚህ ነው፡፡ የነገረ ድኅነት ማዕከልም ይኸው የእግዚአብሔርና የሰው ፈቃድ ጉዳይ ነው፡፡ ታዲያ ክፉውም ሆነ ቅዱሱ አይነካም ማለት ግን ከፊት ቀድሞ አይመራም፣ ከኋላ ተከትሎ አይስብም ማለት አይደለም፡፡ የዚህ ዝርዝር ከመጽሐፉ የሚኖር ይሆናል፡፡ ..በሌላኛው ጽንፍ ውጊያውን የተማሩ ሰዎች፥ በነርሱና በመናፍስቱ ፈቃድ መካከል ያለውን ልዩነት አጥፍተው ስንፍናቸውን፣ ጥፋታቸውን፣ ፍላጎታቸውን ሲያመካኙ ይገጥማሉ፡፡ የማልጸልየው፣ የማልተጋው፣ ..ተይዤ ነው ዓይነት ሁሉን ድክመት ለክፉዎቹ የሚያሸክሙ አሉ፡፡ ከሳሹን የሚከሱት ማለት ናቸው፡፡ እንዲህማ አይደለም፡፡ መናፍስቱ ራሳቸው እስከየት ርቀት መፈተን እንደሚችሉ ያውቃሉ፡፡ ችግሩ ከላይ እንደተባለው የአእምሮ መጎልመስ፣ የልቡና ኃይል መጠንከር እንዲመጣ ራሳችን ላይ ሆን ብለን ስለማንሰራ አቅማችንን በውል አናውቀውም፡፡ ኅሊናችን ለይቶ ሲከሰን አንሰማውም፡፡ ..በመሠረቱ፥  ከክርስቶስ ጋር በሁለመና ላሉት፥ ክፉ መናፍስት ከእርከን ወደ እርከን የለውጥ መሸጋገሪያ፣ ቸልታ እንዳይመጣ ትጉህነትን ማስታወሻ፣ የባልንጀራን ድካምና መከራ መገንዘቢያ፣.. መሣሪያዎች ብቻ ናቸው፡፡ በተቃራኒው ላሉት አማራሪዎች፣ ማሳበቢያዎች፣ ተስፋ አስቆራጮች ናቸው፡፡ ይሄን በተመለከተ የውጊያው ዓለም መምህራን አስቡበት፡፡ አለበዚያ፥ በግራኛ በቀኝ ከክርስቶስ ጋር የተሰቀሉት ሁለት ወንበዴዎች፥ አንድ ሆነው ሳሉ፥ አንዱ የተሳደበበትን ሌላኛው የተማጸነበትን የፈቃድ ጉዳይ ሳንረዳው፥ ተይዤ ነው እያሉ ተያይዘው የሚጠፉ ሰዎች እንዳይበዙ! በቅን ሀሳብ ይታሰብበት!
7.9K viewsedited  15:59
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-24 13:49:08 "ለእግዚአብሔርሰ አልቦ ዘርእዮ ግሙራ አላ ወልድ ዋሕድ ዘሀሎ ውስተ ሕፅነ አቡሁ ውእቱ ነገረነ - መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው።"
(ዮሐ. ፩፥፲፰)

ሰዎች በተፈጥሮአችን ለእውነት እንገዛለን:: በየትኛውም ዐይነት ኹኔታ ውስጥ ይሁን እውነትን እንወዳታለን፤ እናከብራታለን:: የእውነት ነገር የዘር፣ የሃይማኖት፣ የጾታ መደብ የለውም:: እውነት ድንበር የላትም:: የእውነት ገዢነት በተፈጥሮና በፍጥረታት ሁሉ ላይ ተገልጾ ይታያል:: እንደውም ተፈጥሮን ውብና ተፈላጊ ካደረጓት መካከል እውነትነቷ አንዱ እንደሆነ በብዙዎች ይታመናል::

ታዲያ ሁላችን በሰዋዊ ባሕርያችን እውነትን ስንወዳት፣ ስንገዛላት ከእርሷ ጋር መሆንን አጥብቀን እንሻለን:: ውሸታምም ሆነን ሳለ እንደዋሹን ስናውቅ የምንናደደው በዚህ ምክንያት ነው:: ከዚህ ባሕርያችን የተነሣ እውነትን ያለማቋረጥ እናስሳታለን:: ግን እውነት አትታይም፣ አትጨበጠንም:: በዚህ ወይንም በዚያ አለች ብለን በመቼት አጥር ከልለን ልንወስናት አንችልም:: ስለዚህ የተሻለ የምትገለጽበትን አማራጭ/መንገድ ማግኘት እንፈልጋለን:: ስንሰማው ዕረፍት ሊሰጠንና አሳምኖ ሊያደላድለን የሚችለውን የእውነትን እውነተኛ ትረካ (Theory) እንፈልጋለን (ሳይንስ አስተንትኖቶቹን ተጨባጭ ለማድረግ የሚተጋው ለዚህ ነው፤ እውነቴን ነው ለማለት እንዲቻለው):: ይህም፥ ፍጹሙንና የመጨረሻውን የእውነት ቃል ማለት ነው (ትረካ የቃል ጉዳይ እንደሆነ ያስተውሏል)::

ዮሐንስ ወንጌላዊ፥ ይሄ ሰዎች #ሁሉ እውነትን እንዲገልጥላቸው [አውቀውም ሆነ ሳያውቁት ባሕርያቸውን እየተከተሉ] ሲፈልጉት የኖሩት፣ የሚፈልጉት የእውነት ቃል፥ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ ጽፎአል:: (ቁ. ፩፥፩) የዚህ ቃል ትረካ ሁላችን ልናገኘውና ልንቆይበት የምንፈልገውን፥ ግን ማናችንም ያላየነውን አማናዊ (Actual) እውነት እንደገለጸልን ይናገራል:: ግን ደግሞ [የሚገርመው] ይላል ሐዋሪያው፥ ግን ደግሞ ይሄ ፍጥረታት ሳይቀሩ መገለጡን በናፍቆት የሚጠባበቁት የእውነት ቃል ወደ ዓለም ሲመጣ፥ ዓለሙ አላወቀውም:: ስላላወቀው፥ አልተቀበለውም:: (ቁ. ፲-፲፩) እነሆ የእውነትን ቃል ሊያገኙትና አግኝተውም ሊኖሩበት ያልፈለጉት ሁሉ ዛሬም እውነትን ፍለጋ ላይ ናቸው (የምናያት ዓለም የዚህ ፍለጋ ውጤት ናት):: በተለይ ዙፋኖች (እነ ጲላጦስ) "እውነት ምንድር ናት?" እያሉ አሁንም አሉ:: (ዮሐ. ፲፰፥፴፰) መንግሥታት፣ ተቋማት፣ ግለሰቦችም ቢሆኑ ሙሉና ህያው ወደሆነው እውነት ሊያደርስ የሚችለውን ቃል (ትምሕርት/ዕውቀት) በተለያየ ዓይነት መንገድ እየፈለጉ ናቸው::

እንደሚታወቀው፥ ፍለጋ፥ ዕረፍት ይከለክላል:: ተፈላጊው እስካልተገኘ ድረስ በለመለመ መስክ መካከል ብናቋርጥ እንኳ መኳተናችን እንዳለ ይቀጥላል:: ደግሞ የምንፈልገውን ከየትና እንዴት እንደምንፈልግ ካላወቅን ልፋቱ ይበልጥ አድካሚ ነው:: ነገርየው ወደ መሰልቸት፣ መሰልቸትም ወደ ተስፋ መቁረጥ ሊያመራ ይችላል:: በእርግጥ እያረጀ ያለው ዓለም በዚህ ተስፋ የመቁረጥ ቅንብብ ውስጥ ክብ እየዞረ ይታያል:: አዙሪቱ ከተነሡበት ነጥብ መልሶ ስለሚያስጀምር፥ ከፀሐይ በታች ነውጥ እንጂ ለውጥ እንደሌለ የተረዳው ዓለም፣ እውነተኛውን የእውነትን ትረካ ያጣው ገሐዱ ዓለም፣ እውነትን ስለማግኘት ሲል አስቀድሞ ለዘመናት ሲያበረታታቸው የኖረውን ዕሴቶች፦ ሲፈጽማቸው የቆያቸው ትእዛዛትና ሲጠብቃቸው የነበረውን ሕግጋት፥ ሁሉ (ሁሉ መባሉ ባመዘነ ያለውን ብዛት ስለመግለጽ እንጂ እያንዳንዱን ስለመጠቅለል አይደለም) ክዶ በመቀጠል የዓመፃ ሥርዓት ውስጥ ገብቷል:: እያመፅን ነን::

እውነተኛውን ቃል ወደማወቅ ብንደርስ ግን በእውነት ከባዶቻችን ሁሉ ለመቅለል የተዘጋጁ ነበሩ:: የእውነት ቃልም ሲናገር "እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ፥ ወደ እኔ ኑ፥ እኔም አሳርፋችኋለሁ" የሚለን ለዚህ ነው:: (ማቴ. ፲፩፥፳፰) እውነት የሚነገርበትን የእውነትን ቃል ማግኘት በራሱ ዕረፍት ነው:: ምክንያቱም በምንፈልገውም ሆነ በሚያስፈልገን ሙሉ እውነት ውስጥ ሁሉም ተሟልተው አሉና:: ስለዚህ ምንም ፍለጋ የትም አንሄድም፤ እናርፋለን:: በሌላ አባባል ሸክሞቻችንን እናወርዳለን:: ሸክም ሲባል ሌላ ነገር አይደለም:: እውነትን ፍለጋ ባሕርያችን ስለማንነቱ ለዘመናት ሲባዝን፥ በሂደቱ የገጠሙን እውነት መሳዮች ያከናነቡን ብዙ ድሪቶ አለ:: እርሱ ተጭኖናል:: በአስተሳሰብ ቋት ውስጥ ቀድሞ ገብቶ የተጫነን ብዙ ጉድ አለ:: እውነት መስሎን የተቀበልነው እውነት ያልሆነ ብዙ ውሸት ከኑሮአችን አለ:: ለዚህ ማስረጃው መቅበዝበዛችን ነው:: ከዕረፍት ለጥቃ የምትደመጥ ሰላማዊ ደስታ ማጣታችን በሚዋሸን ዓለም ስለመከበባችን ይናገራል:: መቼም ደስታ ፍለጋ ብዙ እየሆንን ነው:: ነገር ግን የሚሆንብን እንጂ የሚሆንልን ነገር እምብዛም ነው::

አላርዝመው:: የምነግራችሁ ምስክርነቴን (ዕረፍቴን) ነው:: ዮሐንስ በሌላ ቦታ "ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያው የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውንም እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን" እንደሚለው መሆኑ ነው:: (፩ኛ ዮሐ. ፩፥፩) ከመጀመሪያው የነበረው የእውነት ቃል የሕይወትም ቃል ነውና በሕይወታችን ውስጥ እውነቱን ተርኮልናል:: ጳውሎስ "የተሰወረ የጥበብና የእውቀት መዝገብ ሁሉ በእርሱ ነውና" እንደሚለው ማንም ያላየውን፣ የተሰወረውን ሁሉ ገላልጦ ነግሮናል:: (ቆላ. ፪፥፫) ከሰማነው፥ እንደሰማነው እናያለን፤ ካየነው፥ እንዳየነውም እንመላለሳለን:: ዕረፍቱ በዚህ መመላለስ አለ:: ይሄ ዕረፍት ከውጭ የምንቀበለው ሳይሆን ከውስጥ የምንከተለው በመሆኑ በየትኛውም ኹኔታ ውስጥ እንዴትም ብንሆን ባለመናወጥ ያጸናናል:: ክፉን እንዳንፈራ ያበረታናል:: (መዝ. ፳፪፥፪) በዚህ ስለዚህ ከዕረፍት ውኃ ዘንድ የሚመራን መልካሙ እረኛችን እርሱ እንደሆነ ያስመሰክረናል:: (፩ኛ ዮሐ. ፬፥፲፬) ነገሩን በከተማ ስብከት ዓይን ባናነበው ጥሩ ነው:: በእውነት ውስጥ ያለቺው ዝምተኛዋ ዕረፍት ወዲያም አለ ወዲህ የተፈጥሮአችን ምጥ ናት:: ከሃይማኖት ሸሽተን ከሥነ ልቦና፣ ከፍልስፍና፣.. የምንፈልገው ያው እርሷኑ ነው:: እስቲ እንስማ:: የእውነትን ቃል ፈልገን፥ እስቲ የእውነት እንረፍ!

@bemaleda_neku
377 viewsedited  10:49
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-24 13:48:52
በእንተ ዕረፍት !
375 views10:48
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-11 00:01:20 ቀናት አዲስ የሚሆኑት በእግዚአብሔር በኩል ነው እነሆ አዳዲስ "የሚመስሉንን" ቀናት ለመጀመር አንድ ልንል ነው፡፡ በእርግጥ በጊዜ አቆጣጠር ሥርዓታችን መሠረት አዲስ ዘመን መጥቷል፡፡ ከዘመነ ማቴዎስ ወደ ዘመነ ማርቆስ ተሻግረናል (ተመስገን!)፡፡ እንዴት ነው ታዲያ ኑሮአችንስ? አዲስ ዓመት ሲመጣ አዲስ ተስፋ፣ አዲስ እቅድ፣ አዲስ አኗኗር አብሮ ይመጣል እያልን መልካም ምኞት እንሰንቃለን፤ እንደዛም…
2.4K views21:01
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-06 16:49:10 እነሆ ከማርቆስ ቤት ደጃፍ ቆመናል፡፡
ከትንሣኤው ቀጥሎ ዕርገቱ ይመጣል፡፡ በዕረገቱ ከአባት ዘንድ እንደወረደው መልሶ ወደ አባቱ ይወጣል፡፡ ከአብ ቀኝ ሆኖም ዝም አይልም፡፡ ሁሉን የሚያውቅ ሁሉን የሚገለጥ አጽናኝ ይልክልናል፡፡ (ዮሐ.16፥7) እስከዛም ድረስ በሰላም ቤት ቆዩ ሲል አሳስቦን ነበረ፡፡ (ሉቃ. 24፥49) እነሆ በሰላም ውስጥ ነን /ሰላም ለእናንተ ይሁን/፡፡

ሰው ቤተ መቅደስ ነው፡፡ (1ኛ ቆሮ. ምዕ 3) ቤተ መቅደስም ሲሆን ከመቅደሱ ያለ ቅድስት አለው ማለት ነው፡፡ (ሕዝ. ምዕ 41) ወደዚህ ወደ ራሱ ቅድስት የደረሰ በዋናው ቅዱስ ይሳብ ዘንድ አለው፡፡ (1ኛ ጴጥ. 1፥15) በአንቀጸ መጽሐፍ አገላለጥ፡ በበዓለ ኀምሳ በ120ው ቤተሰብ ላይ ከወረደው ወይን ጠጅ ለመጠጣት መንፈሳዊ ማንነት ያስፈልጋል፡፡ (ሐዋ. ምዕ 2) ማንነቱ በእምነት ያለ እውነት፥ በእውነትም የሚገለጽ ቅንነት ነው፡፡ ራእየ ዮሐንስ፡ ይህንን ማንነት ሊውጥ አፉን ከፍቶ ስለሚመጣ ቀይ ዘንዶ የሚለን ይኖራል፦

    "ሌላም ምልክት በሰማይ ታየ፤ እነሆም ታላቅ ቀይ ዘንዶ፤ ..ዘንዶውም ሴቲቱ በወለደች ጊዜ ሕፃንዋን እንዲበላ ልትወልድ ባላት ሴት ፊት ቆመ፡፡ አሕዛብንም ሁሉ በብረት በትር ይገዛቸው ዘንድ ያለውን ልጅ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ልጅዋም ወደ እግዚአብሔርና ወደ ዙፋኑ ተነጠቀ። ..በሰማይም ሰልፍ ሆነ፤ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ። ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ፥ አልቻላቸውምም፥ ..ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ፤ ወደ ምድር ተጣለ መላእክቱም ከእርሱ ጋር ተጣሉ።"

ወንዱ ልጅ ወደ እግዚአብሔር ሲነጠቅ በአንጻሩ ዘንዶው እስከ ወዳጆቹ ወደ ታች ተጥሏል፡፡ የተጣለውም ወደ ምድር ነው፤ ወደ ሥጋ!

እንግዲህ በሥጋ ለሥጋ ብቻ የሚኖሩት የወጡ ሲመስል እየወረዱ ናቸው፡፡ ቁልቁለቱን ተያይዘውታል፡፡ የሰማዩ እውነት ሽቅብ በወጣበት ልክ እነርሱም ወደ ሐሰታቸው ጥግ "እየወጡ" ነው፡፡ ነገሩ፡ ክፋትም በመጨረሻ ብቃቱ ወደ መገለጽ ይሄዳል እንደማለት ነው፡፡ ተፈቅዶለታልና ተዉት፤ ክፉ የሚችለውን ያህል ይክፋ (ራእ. 22፥11)፤ ..

ወሳኙ ይሄ ነውና እንድገመው፡፡ ሰውነት ቤተመቅደስነት ነው፡፡ የዚህ ቤተመቅደስ ውጪያዊ ቅጥር ሥጋ ነው፡፡ መድሀኒቱ የሚታየውን ቤተ መቅደስ (ከሥጋ የተወለደውን ሥጋ) አፍርሱት ስለማለቱ ወንጌል ያስታውሰናል፡፡ (ዮሐ. 2፥19) በሥጋ ዕውቀትና ሕግ ወደ ረቂቁ አማናዊ ሥርዓት አይደረስም፡፡ ምክንያቱም ከላይ የተጠቀሰው ዘንዶ በልጅነቱ እባብ ሳለ ነድፎ የመረዘው የሥጋን ፈቃድ ነው፡፡ (ሮሜ. 7፥18) ይሄ ፈቃድ ካስገኘው ፈቃድ ወጥቶ ከሚያጠፋው ጋር በመተባበር፥ ከውስጠኛው ቅጥር ያለቺውን የአምላክ እፍታ ሸፍኗል፡፡ ስለዚህ መጋረጃነቱ ሊገፈፍ (ሊፈርስ) ይገባዋል፡፡ (ቆላ. 2፥11) ይሄም መገለጥ በመስቀል ተከናወነ፡፡ እነሆ ነፍስም "አባት ሆይ፥ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ" በሚል የኛን ባሕርይ በለበሰ ታላቅ ጸሎት ነጻ ወጣች፡፡ (ሉቃ. 23፥46) አሜንታዎች ሆይ፥ በሉ ስለዚህች ታላቅ ጸሎት እጅ ንሡ!

እናንተ፡ ጸሎቲቱን አሜን የምትሏት አማኞች ስትኖሩ፡ ደግሞም ውጪያዊ ቅጥራችሁን ታፈርሱም ዘንድ እንግዲያስ ያስፈልጋችኋል፡፡ አፍርሱና የነፍስን አርነት አውጁ፡፡ ለዚህ ዓለም ሥጋዊ ሥርዓት ምውታን ሁኑ፡፡ የዘንዶው ትልቁ መናገሻ የሥጋ ጉድለት (ድክመት) ነው፡፡ ለሚታየው መሞት እንደሚወራው ቀላል እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡ ለዚህም ነው መድኃኒቱ "ባለሸክሞች ሆይ፥ እስቲ ወደ እኔ ኑ" የሚለን፡፡ በእርሱ ከተሆነ እንደርሱው መሞት ይቻላል፡፡ የሞቱም ቁልፍ የተዘጉ ማኅተሞችን ተራ በተራ ይከፍታል፡፡ ሞቱን በሚመስል ሞት እየሞትን የምንፈታው፣ የምንተረትረው የየራሳችን ጥቅል ተቀምጦልናል፡፡ ጥቅሎቹንም ፈትቶ የማንበቡ ሂደት ወደ ውስጠኛው ቅጥር እያስገባ ከመቅደሱ አስኳል ያደርሳል፡፡ ውስጠኛይቱ ቅጥር ነፍስ ናት፡፡ ነፍስም ከሰማይ የሆነች ሰማያዊ ናት፡፡ ስለ ሰማይ ደግሞ ከላይ ያጣቀስነው የራእዩ መጽሐፍ እንደገና እንዲህ ይላል፦

      "ሰማይና በውስጡ የምታድሩ ሆይ፥ ደስ ይበላችሁ፤ ለምድርና ለባሕር ወዮላቸው፥ ዲያብሎስ ጥቂት ዘመን እንዳለው አውቆ በታላቅ ቍጣ ወደ እናንተ ወርዶአልና።"

ክፉው ብቻ ሳይሆን፡ እኛም ትንሽ እንደቀረ አውቀን ጠብቁ ካለው ቦታ ደስ ይበላችሁን ይዘን በደስታ ቆመናል፡፡ ስሙ በቃላችን ከፍ ከፍ ላለለት እርሱ በእውነትና በመንፈስ ሰግደናል፡፡ (ሉቃ. 24፥52) መጠበቂያ ቦታውም ከመጀመሪያው ጀምሮ የነበረውን የሕይወት ቃል ጸንቶ መጠበቅ (መታዘዝ) ነው፡፡ ብንወደውስ የሚለውን ሰምተናል፡፡ እንደሰማን ሊያሳየን ትእዛዙ ተቀጥሮአል፤ አሁን እዚያ ነን፤ በማርቆስ ቤት ነን፤ በኢትዮጵያ!

@bemaleda_neku
2.0K viewsedited  13:49
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-06 16:48:47
መዝ. 68፥31
2.0K viewsedited  13:48
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-27 12:09:35 ለሊቱን ሁሉ ሲንበላወሱለት ያነጉበትን የዓሣ ሥራቸውን ትተው ነው የተከተሉት:: ክርስቶስ አጠገባቸው ሆኖ ሲያስተምር እንዳይሰሙ ያደረጋቸውን መረብ ትተው ነው የተከተሉት:: በሌላ አባባል ፈቃዳተ ሥጋቸውን ትተው "ስለምትበሉት ስለምትጠጡትና ስለምትለብሱት አትጨነቁ" እያለ የሚነግራቸው አስተማሪያቸውን ተከትለው ነው በሚሄድበት ሊሄዱ የተከተሉት::

የሥጋ ጉድለቶች በሙሉ ስብዕና ክርስቶስን ወደ መከተል ዱካ እርምጃ የሚያስጀምሩ ጥሪዎች ናቸው:: ጉድለታችንን በሚሞላ አምላክ ላይ ትውክልታችንን የምናስደግፍባቸው መሠረቶች ናቸው:: በንቁ ጉባዔ ስናጤናቸው: የተለያዩ የሥጋ ጉዳቶችን የሚያመጡ የዲያብሎስ መናፍስትን በኃይለ እግዚአብሔር እንደምንቋቋማቸው የምንረዳባቸው: የቱ ጋር ምን እያሰብን እንደቆምን ራሳችንን የምንመረምርባቸው መድኃኒት ክርስቶስን የመከተያ መነሻ ምክንያቶች ናቸው:: ክርስቶስ መረባችንን ሲሞላ ካየን በኋላ ግን ጉድለቶቻችንን እዛው ባሉበት ጥለናቸው የምንሄድ እንጂ አንጠልጥለናቸው በጎደሉ ቁጥር ስንሞላቸው የምንኖር አይደለንም:: [ስለዚህም አይደል ሥጋውን ሞልቶ ነፍሱን ያጎደለ ምን ተጠቀመ መጽሐፍ የሚለው? (ማቴ. ፲፮፡፳፮)]

መምህሩ "ንቁ፥ በሃይማኖት ቁሙ" ሲሉ ጉድለቶች በእግዚአብሔር ጸጋ እንደሚሞሉ በንጹሕ ዓይኖች ለሚያዩ ገልጠው አሳዩ:: ቀጥሎ ያለው በሃይማኖት ቆሞ የመጎልመስና የመጠንከር ሂደት ግን ተማሪዎቻቸው በፈቃዳቸው ሊቀጥሉት የሚገባው ጉዳይ ነው:: አንዴ ወደ ትሕርምት ሕይወት ተጠርቶ የገባ ሰው: ትሕርምቱን የሚይይዘው እየሞሉ የሚጎድሉ ጉድለቶቹን እንደ መነሻ ጥሪው ደጋግሞ እየሞላቸው ሊሄድ ሳይሆን ይልቅስ ሁሉን (ፈቃደ ሥጋን) እየተወ እየተወ ነፍሱን በማሰለጠን ክርስቶስን ሊመስልበት ነው::

በተለይ በተለይ: የመምህርን ፍኖት የተከተላችሁ ወጣት መምህራን አስቡበት! መናፍስቱ ዘመንን በሚገባ በመዋጀቱ ረገድ የተዋጣላቸው ናቸው:: የዛሬ ፲ ዓመት የነበረው የክፉ መንፈስ ውጊያ እንደ ሰሞኑ አይደለም:: ክፉዎቹ ራሳቸውን ያሻሽላሉ:: የትውልዱን አዝማሚያ ያስተውላሉ:: መንፈሳዊ ፍሰቶችን በማጤን ይከታተላሉ:: የሰዎችን ጠቅላይ የአመለካከት ኹናቴ ይመዝናሉ:: ለምሳሌ: የውጊያውን ዓለም እያወቁ ያሉ: የንቁን ደውል እየሰሙ ያሉ ሰዎች እየበዙ ስለመሆናቸው ሲያዩ: የፈተና አቅጣጫዎቻቸውን በዚህ ንቃት ልክ ያስተካክላሉ:: በመሆኑ የምእመናን መንፈሳዊ ሕይወት ትሕርምትን ጉዞው ሳይሆን መደምደሚያው እንዲያደርግ ስልት ነድፈው ይንቀሳቀሳሉ:: ይህም ውጤት አስገኝቶላቸው: ውጊያ የተማሩ ብዙዎች በመንፈሳዊ ልምምዶች በመታገዝ በነፍስ ማሳ ላይ የሚበቅሉ የመንፈስ ፍሬዎችን ከማፍራት ተዘናግተዋል:: ሰይጣናትና አጋንንትን ለማስቆም እንጂ በሃይማኖት ዕውቀትና ምግባር ሥር ሰዶ የሚያድግ የማንነት ጉልምስናን ግብ ከማድረግ ተሰናክለዋል:: በመከራ ምክያትነት መጠንከርን ከጽኑ መሻት ዝርዝራቸው ውስጥ አስወግደዋል (ነገሩ ቀድሞውኑ ከዝርዝሩ ሲኖር ነው ተወገደ የሚሰኘው):: በዚሁ ከቀጠለ: መንፈሳዊ ሕይወትን የሚለማመዱ ሰይጣናት እንደ ጠቋር ያሉት: ጸሎት ቤት ያላቸው የሚሰግዱ ዓመፀኞችን ወደማስገኘት እንደሚተጉ አልጠራጠርም::

በማኅበራዊ ድረገጾች የምናሳየው ጠባይ ብዙዎቻችንን አስገምቶናል:: በትሕርምቱ ሕይወት ውስጥ አለን የምንባል: ክፉ መናፍስት ላይ ነቅተናል የምንባል ሰዎች በእጅ ስልኮቻችን ምን እንደምናደርግና በውሎአችን ውስጥ እንዴት ባለ አኳኋን ቀኑን እንደምናሳልፍ እኛው እናውቃለን:: በውጊያው ላይ ካልነቁ ሰዎች ሳይሸሹ ዘወር ያሉ ዝንባሌዎቻችን መስገድና መጸለይ እንጂ ስብዕናይቱን መልበስ እንዳልጀመርን ይናገራሉ:: መናፍስትን ማስወጣት እንጂ የመናፍስት መደበቂያና መገለጫ የሚሆኑ አስተሳሰቦችን፣ ልምምዶችንና አዝማሚያዎችን ከኑሮአችን ማስወጣት አልቻልንበትም::

ከመሠረቱ: የውጊያው ሕይወት ያልተስተካከሉ እኛነቶቻችንን በፈተናዎች አማካኝነት እያስተካከልን ወደ ሰውነት ልዕልና የምናድግበት እንጂ የመናፍስቱን ስም፣ ዓይነትና ስልት አውቀን በትናንት ማንነታችን ላይ ያለ ለውጥ ተመልሰን እዛው የምንረግጥበት አዙሪት አይደለም:: ጳውሎስ "የሥጋ ብልቶቻችሁን ግድሉ" ላለው ትእዛዝ ታዘን: ፈቃዳተ ሥጋን ለፈቃዳተ ነፍስ የምናስገዛበት የመጋደል ሂደት እንጂ የተዘጉ ሱቆቻችንን ስለማስከፈት የስግደትና የጸሎት መጽሐፍ የምናማርጥበት የሥጋ መበልጸጊያችን አይደለም:: ከምንም በላይ: በትሕርምቱ ሕይወት ውስጥ ያሉ ክርስቶሳውያን በመጽሐፈ ገላትያ ላይ እንደተጠቀሱት ያሉ የመንፈስ ፍሬዎችን ማፍራት ካልቻሉ: ድካማቸው ሁሉ ከንቱ ነው (ለምሳሌ ፍቅር አንዱ ፍሬ ነው፤ ፍቅር ሳይኖርህ የጸሎት ሥዕለ አድኖ እስኪያወራህ ድረስ ብትተጋ እንኳ ትሩፋትህ ሲባዛ በዜሮ ነው (፩ኛ ቆሮ. ፲፫፡፪)):: (ገላ. ፭፡ ፳፪)

ይህን በተመለከተ ኃላፊነት የምትወስዱት እንግዲህ የውጊያውን ትምህርት ከንቁ ጉባዔ አስከትላችሁ እያስተማራችሁ ያላችሁ በጎ አገልጋዮች ትሆናላችሁ:: በወንጌል ሰቅ ወገባችሁን በመታጠቅ: ትውልዱ የሚፈልገውን ሳይሆን ለትውልዱ የሚያስፈልገውን (እግዚአብሔር የሚፈልገውን): ከምንምና ከማንም በላይ አስቀድሞ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጸድቁንም የሚፈልጉ የነፍስ ባለጸጋዎችን ታበቁ ዘንድ ከባድ ተልዕኮ ይጠብቃችኋል:: ለዚህ አደራ ደግሞ የሚስማማ ማስተዋል፣ ጽሩይ ጠባይ፣ ትጋትና ውዳሴ የተጸየፈ ዕውቀትን ያለማቋረጥ የሚጨምር ማንነት ስለመያዛችሁ በየቀኑ ልታረጋግጡ ያስፈልጋችኋል:: በተለይ ደግሞ አሁን እንዳለንበት አገራዊ ፈተና: ምእመናን ካሉበት ጠባብ ዛቢያ ሰፋ ብለው: በመከራ ምጥነት አዳዲስ ስብዕናዎችን እየወለዱ ኢትዮጲያዊ ነፍስን የሚያክሙ ሰዎችን የማፍራት ልዩ አጀንዳ ልትቀርጹ ይገባችኋል:: መከራ ሲያገኛቸው ለውጥ ሊመጣ እንደሆነ የሚያስተውሉ፣ ይሄን ዓለም ከነግሳንግሷ የናቁ፣ በመንፈስ ፍሬዎች አጊጠው እስከ መጨረሻው የሚጸኑ፣ ሲሆን ተንከራትተው: ዋጋ ከፍለው: ሕይወት ሰጥተው አገር ያስረከቡንን የአባቶቻችንን አስደናቂ ዕውቀቶች (ቢያንስ መጽሐፍቶቻቸውን) በመፈተሽ የዓለምን ጠኔ የሚፈውስ ጠበል በየድርሻቸው የሚያዋጡ ምእመናን ስለማብዛት ራሳችሁንም ሆነ ትምእርቶቻችሁን አሰናዱ:: በተረፈ ከመከራ ለመገላገል ሲል ትሕርምትን እንደ መድኃኒት ቤት የሚቆጥር አመለካከት የሚዋጋቸው ሰዎች: በተግባራዊ ዕውቀት ሊታረሙ ያልቻሉ እንደሆነ: እንደተባለ እነ ጠቋር በዚህ እየሰገደ በዚያ የሚሳደብ መንፈሳዊ ሰይጣን ሆነው የነቁ እንቅልፋሞች እንደሚያደርጉን አኳኋናችን ያሳብቃል:: ያቆየን!

@bemaleda_neku
4.0K views09:09
ክፈት / አስተያየት ይስጡ