2022-08-29 11:17:23
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በድሬዳዋ አገልግሎት መስጠት ጀመረ
ነሐሴ 23፤ 2014 ዓ.ም.
(አዲስ ዘይቤ፡ አዲስ አበባ) ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በድሬዳዋ ከተማ የሙከራ ስራውን መጀመሩን አስታውቋል። ደንበኞችም የፈልጉትን ስልክ ቁጥር መርጠው ሲም ካርድ መግዛት እንደሚችሉ አስታውቋል።
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ እንደገለፀው በድሬዳዋ በጀመረው የሙከራ ትግበራ የ2G፣ 3G እና 4G ኔትዎርኮችን ያስጀመረ ሲሆን የተቋሙ መለያ ከተለጠፈባቸው መደብሮች ደንበኞች ሲም ካርድ መግዛት ይችላሉ ብሏል። ከሲም ካርድ በተጨማሪም የስልክ ቀፎ እንደሚሸጥ ተገልጿል።
ሲም ካርዶቹ የደንበኛነት ማስጀመሪያ ጥቅል እንዳላቸው የተገለፀ ሲሆን የአየር ሰዓቱ ሲያልቅ በተመሳሳይ ከሳፋሪኮም ኢትዮጵያ የሽያጭ ማዕከላት እና መደብሮች መግዛት እንደሚቻል አስታውቋል።
በተጨማሪም የተሻለ አገልግሎት ለማቅረብ የሚረዳ ‘700’ አጭር ቁጥር የደንበኞች አገልግሎት የጥሪ መስመር ድርጅቱ ያቀረበ ሲሆን በአማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ ትግርኛ፣ ሶማልኛ እና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች ድጋፍ ማግኘት ይቻላል ተብሏል።
የሳፋሪኮም ደንበኞች የኢንተርኔት ዳታ መጠቀም፣ ከሳፋሪኮም ኢትዮጵያ እና ከኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞች ጋር የድምፅ እና የፅሁፍ መልዕክት መለዋወጥ እንዲሁም ዓለም አቀፍ ጥሪዎች ማድረግ እንደሚችሉ ተገልጿል።
_____
ለወቅታዊ እና ለፈጣን መረጃዎች የአዲስ ዘይቤ የማህበራዊ ሚዲያዎችን ይቀላቀሉ።
Twitter : https://bit.ly/3uQBnvj
Facebook : https://bit.ly/2SeU3Ev
Telegram : https://bit.ly/3JX93LY
Website : https://bit.ly/3JOUavm
YouTube : https://bit.ly/37rIyBa
749 views08:17