2021-12-21 04:23:15
ታህሳስ 12
ዕረፍቱ አአባ ሳሙኤል ዘዋልድባ
ውኃውን ወይን ድንጋዩን ዳቦ አድርገው
ልጆቻቸውን የመገቡት፣ዕድሜያቸውን ሙሉ የድንጋይ ቆብ
ያደርጉ የነበሩትና አራዊት ሁሉ የተገዙላቸው፣ከ24ቱ ካህናተ
ሰማይ ጋር የሥሉስ ቅዱስን መንበር ያጠኑት አቡነ ሳሙኤል
ዘደብረ ዋሊ ዕረፍታቸው ነው፡፡
✞ አባ ሳሙኤል አባታቸው እስጢፋኖስ እናታቸው አመተ ማርያም
ይባላሉ፡፡ በ12 ዓመታቸው ሹም በተባለው ባሕር ገብተው ሲጸልዩ
ባሕሩ በብርሃን ተከቦ ይታይ ነበር ፡፡
ከባሕሩም ወጥተው ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው እያለቀሱና
እያዘኑ ሲጸልዩ ካህናቱ "ይህ ህፃን የእኛ ኃጢአት እየታየው ?
ወይስ ምን ኃጢአት ኖሮበት ነው እንዲህ የሚያዝነው እና
የሚያለቅሰው ?እያሉ ያደንቁና ይገረሙ ነበር፡፡
✞ አባ ሳሙኤል እናታቸው ቤተሰቧንና ቤት ንብረቷን ትታ
ከመነኮሰች በኃላ እርሳቸውም ካልመነኮስኩ በማለት አባታቸውን
ቢለምኑ እምቢ ስላለቸው በራሳቸው ፈቃድ ከአንድ ሽማግሌ ጋር
ወደ አባ መድኃኒነ እግዚእ ገዳም ደብረ በንኮል ገብተው
መነኮሱ፡፡
በዚያም ነፍሳቸውን "ነፍሴ ሆይ ! እነሆ ለክርስቶስ ታጨሽ፣
የቅዱሳንን ቀንበር እነሆ ተሸከምሽ የመላእክትን ንፅህና ትጠብቂ
ዘንድ ዛሬ በእግዚአብሔርና በቅዱሳኑ ሁሉ ፊት ቃልኪዳን ገባሽ ፣
ቃልኪዳንሽን ብትጠብቂ መላእክት ይደሰቱብሻል ፣ ባትጠብቂ ግን
አጋንንትን ይዘባበቱብሻል . . . .እያሉ ብዙ መከራን በራሳቸው ላይ
በማብዛት 7 ዓመት በዚያች ገዳም ኖሩ፡፡ እህልም አይቀምሱም
ነበር ይልቁንም የሚሰጧቸውን እንጀራ ለሕፃናት እና ለውሾች
እየሰጡ አሠር ይመገቡ ነበር፡፡ ዳግመኛም በሌላ ጊዜ ቅጠልን
እየቀቀሉ እስከ 5 ቀን ከድነው ያስቀምጡታል እስከሚተላም ድረስ
ይጠብቁትና ያን ይመገባሉ፡፡ አባታቸውም ልጁን አባ ሳሙኤልን
ተከትለው ወደ እርሱ መጥተው በአባ አድኃኒ እጅ መነኮሱ፡፡
✞ አባታችን አባ ሳሙኤል በሕይወተ ስጋ ሳሉ እጅግ ድንቅ ድንቅ
የሆኑ ተዓምራትን አድርገዋል ፡፡
☞እንደ ሙሴ ባሕርን የከፈሉበት ጊዜ አለ፣ በልዑል ዙፋን ፊት
እየቀረቡ
ከቅዱሳን መላእክት ጋር የሚያመሰግኑበት ጊዜ አለ፣ ከ24ቱ
ካህናተ ሰማይ ጋር ሆነው የሚያጥኑበት ጊዜ አለ ፣ በሰማያዊት
ኢየሩሳሌምም ሆነው ከነ ቅዱስ ጼጥሮስ እና ከሁሉ ቅዱሳን
ጻድቃን ሰማዕታት ጋር በአንድ ላይ ማዕድ የሚቀርቡበት ጊዜ አለ
፣ በእጃቸው የያዟቸው መፃህፍቶች ምንም ሳይርሱ ትልቅ ወንዝን
በውስጡ እያቋረጠ የሚሻገርበት ጊዜ አለ ፣ እመቤታችንንም
ሲያመሰግናት ከምድር ወደ ላይ 1 ክንድ ያህል ከፍ የሚሉበት
ጊዜ አለ ፣ በቤትም ውስጥ ሆኖ ምስጋናዋን ሲጀምሩ የቤቱ
መሰረት እየተናወጠ ዝናብ እንደያዘ ደመና ቤቱ ከምድር ከፍ ብሎ
የሚቆምበት ጊዜ አለ ፣ መንፈስ ቅዱስም በብርሃን ክንፍ
እንደወሰዳቸው ወደ ተለያዩ ገዳማት ያደርሳቸውና ስጋ
ወደሙን እንዲቀበሉ ያደርጋቸው ነበር፡፡ መልአኩ ቅዱስ
ሚካኤልም የሁልጊዜ ጠባቂያቸው ነውና በሁሉም ነገር
ይራዳቸውና እንደ ጓደኛም ያማክራቸው ነበር፡፡
✞ አባ ሳሙኤልን የዱር አራዊትም ሁሉ ይገዛላቸው ነበር ፡፡
ታላቅ የሆነ ዘንዶ ፣ ነብር ፣ ጅብ ፣ ቶራህ ፣ ዝሆን ፣ አንበሳና
ሌሎችም የዱር አራዊት ሁሉ እየመጡ እግራቸውን እየላሷቸው
ወደ ቦታቸው ይመለሱ ነበር፡፡ ከገዳም ወጥተው መሄድ በፈለጉ
ጊዜ አንበሶችን እንደ ፈረስና በቅሎ ይጋልቧቸዋል
መፃህፍቶችንም ይጭኑባቸዋል፡፡
✞ ዋልድባ የተመሰረተው በቀደምት ጥንታውያን አበው ቢሆንም
አባ ሳሙኤል ሲገቡበት ምድረ በዳ ሆኖ ጠፍቶ ቋያ በቅሎበት
የወባ ትንኞች መፈልፈያ ሆኖ ነበር፡፡ አባታችን ግን የተበታተኑትን
መነኮሳት ሰብስበው ዋልድባን እንደገና አደራጅተውና አድሰው
አቀኑት፡፡ የተባህትዎ ኑሮንም አጠናከሩበትና ገዳሙን የመናንያን
አበው መሰብሰቢያ አደረጉት፡፡
❖ አባታችን ዋልድባን እንደ መሶብ አንስተው አስባርከዋታል፡፡
☞ አባ ሳሙኤል ጊዜያቸው ደርሶ ከማረፋቸው በፊት ቅዱስ
ሚካኤል ነሐሴ 16 ቀን ወደ ገነት ነጥቆ ወስዶ ከዕረፍታቸው በኃላ ከልጆቻቸው ጋር የሚኖሩበትን ስፍራ አሳይቷቸዋል፡፡በገነት
ያሉ ቅዱሳንን ሁሉ ካሳያቸው በኃላ በእግዚአብሔርም ዙፋን ፊት
ቀርበው ምስጋና ቃልኪዳንን ተቀብለው ወደ በዓታቸው ተመልሰው
ታህሳስ 12 ቀን በታላቅ ክብር አርፈው ነፍሳቸውን ጌታችን በእጆቹ
ተቀብሏታል፡፡
☞ የአቡነ ሳሙኤል በዓለ ዕረፍት በሚከተሉት ቦታዎች በዋነኛነት
ይከበራል፡፡
1. በሁሉም የዋልድባ ገዳም ክፍልች (በውስጡ ባሉት 3ት
ገዳማት፣ የተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት፣ ጸሎት/ስዕል/ ቤቶችን፣
የአትክልት ቦታዎችንና ሞፈር ቤቶች)፤ እነዚህም፡-
1.1. ዋልድባ አብረንታንት ገዳም (የአብረንታንት መድኀኔዓለም
ገዳም)
1.2. ዋልድባ ዳልሽህ ገዳም
1.3. ዋልድባ ሰቋር ገዳም (የኪዳነምሕረት፣ የቅዱስ ጊዮርጊስና
የመድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያንን ያካተተ)
1.4. አቴና (መቃብረ ሳሙኤል)፤ ሌሊቱንና ቀኑን ሙሉ ገድላቸው
እየተነበበ
1.5. አባ ናፃ የአቡነ ተሥፋ ሐዋርያት ገዳም
1.6. ደንደሮቃ ቅዱስ ሚካኤል ቤ.ክ
1.7. ማይገባ ቅዱስ ሚካኤል ገዳም
1.8. ማይ ሃርገጽ ቅ/ጊርጊስ ቤ.ክ
19. ዕጣኖ ማርያም ቤ.ክ
1.10. ማይ ለበጣና ሌሎችም የስዕል ቤቶች፣ የአትክልት
ቦታዎች
2. በተወለዱበት በርዕሰ አድባራት ወገዳማት አኵሱም ጽዮን
ማርያም፤
3. ምንኵስናን በተቀበሉበት በደብረ በንኰል አቡነ መድኀኒነ
አግዚእ ገዳም
4. በቆብ ወንድማቸው በአባ ያሳይ መንዳባ ገዳም
5. በቆብ አያታቸው በአቡነ ተክለሃይማኖት ደብረ ሊባኖስ ገዳም
በውዳሴና በቅዳሴ (ከጥንት ጀምሮ)
6. አቡነ ሳሙኤል በመሠረቷቸው ገዳማት
6.1 በደብረ ዐባይቡነ ሳሙኤል ገዳም /ሽሬ አጠገብ/ ፣ እጅግ
ደማቅ በኾነ ኹኔታ
6.2 በአብጠራ (አብጠራህ) አቡነ ሳሙኤል ገዳም /ደባርቅ/፣
6.3 ደብረ ገነት አቡነ ሳሙኤል ገዳም /አዲስ አበባ አቃቂ
አጠገብ/) በታላቅ ድምቀት
6.4 ጎንደር አዘዞ አባ ሳሙኤል
በተጨማሪም በስማቸው በታነጹ አብያተ ክርስቲያናት ይከበራል፤
ለአብነትም፤
7. በአዲስ አበባ ወረገኑ ቅዱስ ሚካኤል እና ጻድቁ አቡነ
ሳሙኤል
8. በአዲስ አበባ ሲምሲ ሚካኤል (በድርብነት)
9. በአዲስ አበባ ሳሙኤልና አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም (ጋራ
መድኀኔዓለም ሳይደርሱ)
10. አዲስ አበባ አቡነ ሳሙኤል፤ ሳሪስ አቦ አጠገብ
ባርከኒ አባ እንሣእ በረከተከ በእንተ ሰላማ ለቅድስት ቤተ
ክርስቲያን አባ ሳሙኤል/፫/ ባርከኒ እንሣእ በረከተከ፡:;
✞ የጻድቁ አባ ሳሙኤል ረድኤት በረከት ምልጃ ጸሎት ከሁላችን
ሕዝበ
ክረርስቲያን ከሀገራችን ከኢትዮጵያ ጋር ይሁን አሜን!!!
<<ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>
500 viewsDesalegn Dagne ✥ድንግል ሆይ ሁሉን ከሚያስብ ሁሉን ከማይዘነጋ ከልጅሽ አሳስቢ✥, 01:23