2023-04-30 13:48:51
ምንም ነኝ ግን አማራ ! ለዚያውም ደሜ አረንጓዴ
(ባለቅኔ ሙሉጌታ ተስፋዬ!)
==============
ምንም ነኝ ግን አማራ ...
ሰዋሰው ... የሰው እኩል ...
በወለባ ... የማልኩል
በስሜት የማልኮለኩል
ምንም ነኝ ... ግን አማራ ... የሰው አቻ ...
የማልንጠረበብ እንደ ቅምብቻ
ምንም ነኝ ... ግን አማራ ...
የፈጠረኝን አምኜ ...
በጎቼን ከተኩላ ጋር የማሰማራ ...
አማራ ነኝ የጠራሁ ...
ኩራት እንጂ ሞት ያልፈራሁ
አማራ ነኝ መቃ አንገት ...
ራሴ ከብዶኝ የማልንገታገት ...
የሰው ጣባ ሥር የማልለገት ...
ዙርያ ገባውን ቃኝቼ ...
ትሻልን ከትብስ አገናኝቼ
አይበጆን ከነመናጆው ባሕር ዙልማ ሸኝቼ ...
የቀኑን እያንቀራጨሁ ...
ደሞ ሌሊቱን እየፈጨሁ ...
ለጎጆዬ የታጨሁ ...
ባሰኝ ብዬ ያልጫጨሁ ...
በወለምታ ያልተቀጨሁ ...
ልጄ ለሰማእትነት ተመርጦ ባንዳ ባረር ቢቀነጥሰው
ሞተ ብዬ ... ደረት ጥዬ ፊት ያልነጨሁ ...
ባለፈው ያልተቆጨሁ ...
አማራ ነኝ ዓይኔን ብከድንም ... እንቅልፍ አላውቅም
ማማ ላይ ነው አዳሬ ...
ገና አባርራለሁ ዋኔ እኔ አለቅም።
ዓይኔ ደጀን ...
ልቤ ግሸን ...
ደሜ አረንጓዴ ...
ጓንዴዬ ጓዴ ...
ቃሌ ደም ... ምግባሬ ደም ...
እንኳን ለቃጣኝ ... ላሰበኝ የማልቀደም ...
ለትንሳዔ የምታደም ... የትም የማልጋደም ...
የትም የማልስደመደም
ማንም እንዳስመለከተው ... ያሻውን ስም ቢያወጣልኝ
እድሜ ለዓባይ ጣና ልጅ ...
ያኔ የማስቆርሰው ድፎ ዳቦ አያጣልኝ ...
ሰምና ወርቅ ቅኔ ...
ጠኔ ያጥን መጥኔ ...
ይኸው ነው ሥርወ ውልደቴ
አማርኛ ነው ውጥኔ ...
አማራ ነው ምጥኔ ...
እንኳን ሰው ወፍ አልምጄ ...
እንኳን ሌላ ጥላ አጥምጄ ...
…
በፍቅር ተገድጄ ...
ውሌን ሳልስት ...
ጉልበቴን ሳልሰስት ...
የልቤን በልቤ ቅስት ሳልሰድር ...
ተኝቼ የማላድር ...
ቼ በወሎ ፈረስ ካይኔ ልቤ ድረስ እያልኩ ...
አዘቦት አልቦዘንኩ ባል አላበልኩ
የቀላወጠው ወጥሮት ... ክንዱን በኔ ሊፈትን
ገና ሲያስተነትን ...
ከነገር ቀደም ሳይመክር በፊት ...
ባባቴ ጋሻ በናቴ ወንፊት
ወደፊት እንጂ ... ምን አለ ሌላ ...
እንኳን መብላት ማብላት ቀርቶበት ...
ለታጠረ በእምነቱ ኬላ
ነፍሴ አውጪኝንማ ማን አስቦት
ዘር ከልጓም ስቦት ...
እንደ ቅዱስ ላሊበላ ንጉስ
ሹመት አይጠናኝ ... አይጠፋኝ ጉግስ
ግብር ጥዬ እንኳ ባልደግስ ...
እንኳን ለጠላቴ
ለወዳጄስ ቢሆን ደም እንጂ ሌላ አለግስ!
ድኃ ነን ብለን ስንል እኮ ... በሰው ልጅ ፍቅር ተጠልፈን ...
እህል ተጠይፈን ...
ለሞት ተሰልፈን ነው እንጂ ...
የምንበላው ቢገደን ... መለኮት ባሕሪም አላነሰን
ክፉ ጥፉ ብሎ እንደ ጨው ዘር የትም አልነሰነሰን ...
ሳይንትና ተንታ ... ዋ ክምበል ያድርገኝ
ምን አገር ቢሰፋ እንዳማራ አይገኝ ...
ቢሆንም አይደል ወይ ጨዋታው ...
አገሩን ... ልብ ውልቅ ድምብልቅ
እስክስታ እሚያስመታው
እና አማራ ነኝ ... መከራ የመከረኝ
መስእዋትነት ያጠነከረኝ ... ፍቅር የተዘከረኝ ...
ብፈራ እንኳ ፍቅርን ነው እንጂ ... በሌላ አልጠረጠርም
ማንም እንዳሻው ለክቶ ... እንዳሻው ሊቆርጠኝ ቢያልም ...
ከልክ አልፌ አላጥርም
ጉራም ቢሆን ልቀናጣ ...
ስሞ ባያሳድገኝ... ነክሶ እሚያነቃኝ አላጣ ...
ያው ወንድሞቼ ይመስክሩ ...
በናት ጡት ወተት ባይሰክሩ
የዛሬ ሃያ አመት ተክራርዋ ወርደውም ባልመከሩ ...
ግቻ ነክሰው ... ጦር ባይሰብቁ
ለዛሬዋለትም ባልበቁ ...
ለዚያውም ውለታ ሳይጠይቁ ...
ትሁት ነኝ እንኳ ባልል እንደ ጠሎተ ሐሙስ ...
ሸቀንና ሰቀቀን ላራግፍ ...
ጦም ሽሬ የማልገድፍ ...
ግን አማራ ነኝ...
እኔው ገምቼ ...
እኔው ዘምቼ ...
እኔው ሞቼ
ክፉ መሻቴን እና ምኞቴን ተጠይፌ ስጋዬን ልሰቅል
ድፍት የምል እንደ ብቅል ...
ጣብያ ሳላቀላቅል!
ኮርማ ሳላዳቅል!
በአ ቅ ል!
እና አማራ ...
የፈጠረውን አምኖ በጉን ተኩላ ጋር ካሰማራ ...
እስቲ ደሞ በልብ እንደመሙላታችን ... ለደራ ሳይሆን
ካይንህ ይፍሰስ ይልቅ ...
እንደው ላይን ላይደምቅ
ፈፋው እምቅ ...
በጠመቅ ...
አምባውን እንደሹሩባ ... በክትር ሰርቶ ...
ለሽማግሌ ጥላ ... ለእንቦሳ መገሌ ...
ለልጅ ሰተቶ ...
መውጫው ጠፍቶን እንዳንንገዳገድ
ደሞ ጨዋታ ... አንድ ለመንገድ ...
እሰጠው ባጣስ ... ለምን ጦም ልደር
እሳትና ጢስ ጠፍቶ ... ከመንደር ...
ንሳማ ጎበዝ ... ንሳ ተነስነስ ...
ከስፍርህ ጎለህ ከሰው አትነስ!
ንሳማ ጎበዝ ... ንሳ አታደግድግ ...
ወገብን ጠበቅ ... ባንጀት ድርብ ድግ ...
እንኳን እቁቡ ... እድሩ ፈርሶ ...
የወላድ ማህፀን ... በዋይታ ታርሶ ...
አማንስ ቢሆን ... ለተቀመጠ ...
እያላመጠ ... እየገላመጠ ...
እየተርመጠመጠ ... እየተዳመጠ
እድሜውን ይፈጃል እንጂ በከንቱ ...
ማን ይለዋል አንቱ ...
ንሳማ ጎበዝ ... ንሳ ተነስነስ ...
ከስፍርህ ጎለህ ከሰው አትነስ!!
793 views10:48