2022-03-22 22:02:12
ሁሉን ወሬ ላውራ አትበል ፣ የደበቁህን ምስጢር
አታውጣጣ ፣ የሰማኽውን ወሬና የተገለጠልህን ምስጢር
ምን መፍትሔ ሰጠኸውና ? ያየህውን ሥራ ሁሉ እሰራለሁ
የሰማኸውን ትምህርት ሁሉ እማራለሁ አትበል ። ይህ
የተሰወረው የቅንዓት ጠባይ ነውና ። ሁሉን ልያዝ ማለትም
ዝንጉ አድረጎ እንዳያስቀርህ ሁሉም ውስጥ ልኑር አትበል ።
፡
ቂም አፍን የሚያመር ፣ ልብን የሚያነቅዝ ፣ ተግባርን
የሚያልፈሰፍስ ነውና ለበደለህ ሰው ቅያሜህን ግለጥለት ፤
ቂመኝነት በክፉ መሸነፍ እንጂ ጀግንነት አይምሰልህ ።
፡
ከህሊናህና ከመንፈሳዊ አማካሪህ ሳትመክር ምንም ነገር
አትወስን ፤ አጥርተህ ሳትሰማ ቃል አትግባ ። መከራ ካልደረሰ
በቀር ባል በሌለበት ቤት ውስጥ ከሚስቲቱ ጋር ብቻህን
አትቀመጥ ።
:
የሚበልጥህ ልኩራብህ እንዳይልህ ፣ ያነሰህ ልድረስብህ
ብሎ እንዳያጠፋህ የሀብትህን ልክ እንዳታወራ ፤ በገዛ አፍህ
ባንዱ ትከብራለህ ባንዱ ትቀላለህና።
፡
በጣም በማክበርህ እንዳታመልከው ፤ በጣም በመናቅህ
እንዳታዋርደው ሠው እንዳንተ መሆኑን እወቀው ።
፡
የእኔ መናገር ምን ይለውጣል? ብለህም ስህተትን አትለፍ
፤ የእኔ አስተዋፅኦ ምን ይጠቅማል ? ብለህም ስጦታህን
አትጠፍ ።
፡
መልካም ቃል ከስጦታ ይበልጣልና መልካም ቃል ተናገር
፤ ማንኛውም ስጦታ ከልመና ወንበር አያስነሣም ። የተስፋ
ቃል ግን እንደሚያስነሣ አውቀህ ለሰዎች የተስፋ ቃል
ስጣቸው ።
፡
ትምህርት ለዕውቀት ያዘጋጃል እንጂ ዕውቀትን
አይጨርስም ። ዕውቀትህን የምትይዝበትን ሥነ-ሥርዓት ግን
ያሳይሃል ። አእምሮህን ለማረቅ ትምህርት ፣ ሰውነትህን
ለመግዛት ትዕግስት ፣ ከማንም ጋር ለመኖር ሥነ-ሥርዓት
ያስፈልግሃል ። ለህሊናህ እረፍት ግን እምነት ያሻሃል ።
ተከታይ ለማበጀት ደግሞ ግልጽ መሆንና ታማኝነት ግድ
ይልሃል ።
፡
አንተው እውነትን ጠልተሃት ዘመኑ እውነትን ጠልቷል
አትበል ። ዘመን እኔና አንተ ነን ፤ በራሱ ክፉና ደግ የሆነ ዘመን
የለም።
፡
መልካም ምክር ብትሰማ ሕይወት ቀላል ይሆንልሃል ።
ትክክለኛም ውሳኔ ከመልካም ምክር ነውና..!!
@yewuketmaed
1.5K viewsedited 19:02