2023-04-27 14:10:17
ስለ #ሒጃብ የተከፈለ መስዋዕትነት
ይህ ለሒጃቧ ስትል የተሰዋችው ለኒቃቧ ስትል የሞተችው የአንደሉሷ ሙስሊም ሴት እውነተኛ ታሪክ ነው። ከስላና ተቃጥላ ስለሒጃብ ስለክብሯ የወደቀች ድንቅ ሴት! ታሪኳ ሲደመጥ የብዙዎች ቀልብ አንብቷል። ስቃያቸው በስቃይዋ ተደምጧል። ለሒጃባቸው ክብር ያልሰጡ እንስቶች ይገሰፁበት ዘንድ ታሪኳን እንካችሁ
ክስተቱን በአንደበቷ እንዲህ ትተርከው ይዛለች።
"የትውልድ ቀዬዬ አንደሉስ ምድር ነው። በሃያዎቹ የዕድሜ እርከን ውስጥ የምገኝ በሰውነት ቅርጼ ሞላ ደልደል ያልኩ ለግላጋ እንስት ወጣት ነኝ። ግና ይህን ሰውነቴን በጅልባብ ሸፍኜና ጠብቄ ሒጃቤን በአግባቡ እለብሳለሁ። የአንደሉስ ሙስሊሞች የስቃይን ፅዋ በመስቀላዊያኑ እጅ ሲጎነጩ እኔም አልቀረልኝም። ለሁለት ዓመታት የለበስኩትን ጅልባብ ሳላወልቅ ሳላጥብና ሳልቀይር እሥር ቤት ከረምኩ። በወታደሮች ግልምጫና ድብደባ መደፈርና መወገር ብዙ መከራዎችን አልፌ የመጨረሻዋ ዕለት ላይ ደረስኩ።
የለበስኩት ጅልባብ ተሰብስቦ ጉልበቴ ጋር ደርሷል። ሰውነቴ በጭቃ ተለውሶ በእግረ ሙቅ ተጠፍሬያለሁ። እጄ የፊጥኝ ታስሮ አንገቴ ላይ በጠለቀው ሠንሠለት እየተጎተትኩ ወደፊት እነዳ ይዣለሁ። በብረት ፍርግርጉ ኋላ ሳልፍ ታሳሪዎቹ በሾሉ ዓይኖቻቸው አፍጥጠው እየተመለከቱኝ የስድብ ናዳ አወረዱብኝ ተፉብኝ። አፈር እየበተኑ ድንጋይ ወረወሩብኝ። የእሥር ቤቱ ጠባቂዎች ጅራፍ በእጃቸው ይዘው ከበቡኝ።
ቀሳውስቱ በአንድነት ቆመው መዝሙራቸውን ያሰማሉ። ባለሥልጣናትና ግብዣ የተደረገላቸው እንግዶች በክብር ወንበራቸው ላይ ተቀምጠው በሚደርስብኝ ስቃይ ለመደሰት ወደ እኔ በትኩረት ይመለከታሉ። ከአንድ ግንድ ጋር ታስሬ ማገዶ በዙርያዬ ተበትኗል። ዘይትና ጋዝ ተርከፍክፎበታል።
ከቀሳውስቱ አንዱ ወደእኔ ተጠጋ። ሁለት ምርጫ አቀረበልኝ። ጅልባቤን አውልቄ በህዝብ ፊት ይቅርታ እጠይቅ ዘንድ አሊያም ተቃጥዬና ሰውነቴ ነዶ በመሞት መካከል ምርጫ ሰጠኝ። ሒጃቤን እንጂ ሌላን አልመረጥኩም። ከፈለጋችሁ አቃጥሉኝ አልኩ ስለሒጃቤ መሞቴ ለኔ ክብር መሆኑን አላወቁም። አልንበረከክም ፈፅሞ የጌታዬን ትዕዛዝ አልጥስም ብትፈልጉ ሰውነቴን ቆራርጡት ቢያሻችሁም አካሌን አንድዳችሁ አክስሉት። አዎ! በፍፁም በሒጃቤና በክብሬ አልደራደርም። የክብር መገለጫዬ በከፍታ የሚውለበለብ ኢስላማዊ ዓርማዬ ነው ብዬ መለስኩለት።
ቄሱ የእሳቱን ነበልባል አንስቶ እንጨቱን ለኮሰው። ሰውነቴ መቃጠል ጀመረ። በቀላሉ እንድሞት አልፈቀዱልኝም እሳቱን አጠፉልኝ። ወደእሥር ቤቱ ወሰዱኝ። ይህ የእሥር ቤቱን አጥር ተደግፌ የፃፍኩት እውነተኛ ታሪኬ ነው...." ይህን ማስታወሻ የእስር ቤቱ ግርግዳ ላይ አስፈራው ተገኘ።
በነጋታው ጠዋት በተመሳሳይ ቦታ የፊጥኝ ታስራ ተሰቃይታ በእሳት ነደደች። ዛሬ ግን እንደትላንቱ አላጠፉላትም። ለዓመታት የኖረችበት ስቃይ እነሆ አበቃ። ግና ነጻነቷን እንደሰጧት አላወቁም።
እኔ ለጻፍኩት እጄ ተንቀጠቀጠ። የጋለ ስሜቴ አንደበቴን ቆለፈው። አጀብ ለእኛ ክብር ስንቶች አልቀዋል።
አላህ መልካም ስራዋን ተቀብሎ ቀብሯን ኑር ማረፊያዋን ፊርደውሰል አዕላ ያድርግላት።
Mahi Mahisho
22 views11:10