Get Mystery Box with random crypto!

ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy

የቴሌግራም ቻናል አርማ zephilosophy — ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy
የሰርጥ አድራሻ: @zephilosophy
ምድቦች: ያልተመደበ
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 19.37K
የሰርጥ መግለጫ

ፍልስፍና  እውነትን በመፈለግ- ሀሳዊ እምነቶችን በማጋለጥ እና ጭፍን አመለካከቶችን በጥበብ በመመርመር ወደ ላቀ አሰተሳሰብ ያሻግራል።
በዚህ ቻናል አለም ላይ ያሉ ፍልስፍናዎች ፤ ርዕዮት አለሞች ፤  ሀይሞኖቶች እና አስተሳሰቦች በነፃነት ይዳሰሳሉ።

Ratings & Reviews

3.67

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

2

3 stars

1

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 17

2022-07-07 23:09:42
መጽሐፍ ውስጥ የተሰወረው መዝገብና ኃብት!

“አንድን ነገር ከጥቁሮች ለመሸሸግ ከፈለጋችሁ በመጽሐፍ ውስጥ አስቀምጡት”

“If You want to hide something from a black person, put is in a book”

ይህንን ከዚህ በፊት ሰምታችት ይሆናል፡፡ ይህ አባባል ጥቁሮች ማንበብ እንደማይወዱ፣ በዚያም ምክንያት ብዙ ነገር እንደሚቀርባቸውና ሕይወታቸውን ወደላቀ ደረጃ ማድረስ የሚችልን እውቀት ችላ በማለት ኋላ ቀር እንደሆኑ ለማሳየት የሚጠቀሙበት አባባል ነው፡፡

ይህ አባባል በእኔና በእናንተ ላይ አየሰራም! ምክንያቱም እናነባለን! እውቀትን እንቀስማለን! እንለወጣለን! እናድጋለን!

ሁሉም ሰው ግን ይህንን አይለማመደውም፡፡ ላለማንበብ ደግሞ የማይሰጠው ምክንያት የለም፡፡ ማንበብ ስጀምር እንቅልፍ እንቅልፍ ይለኛል፤ ምንም የሚነበብ ጠቃሚ ነገር የለም፤ ማንበብ እጀምርና መቀጠል ግን አልችልም፣ ማንበብ እጀምርና የተወሰኑ ገጾች ካነበብኩኝ በኋላ ያነበብኩትን አላስታውሰውም . . . እና የመሳሰሉት ምክንያቶች የተለመዱ ናቸው፡፡

አንብቡ! እደጉ! ተሻሻሉ! ተለወጡ! እናንተ ለእናንተ ካላነበባችሁለት ማንም ለእናንተ አያነብላችሁም!

ዶ/ር እዮብ ማሞ
@Zephilosophy
@Zephilosophy
5.1K viewsedited  20:09
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-07 09:21:24 ደስተኛ አለመሆንን ለምን እንመርጣለን?
...የቀጠለ

ሰዎች ደስተኛ ከሆኑ በገንዘብ ልትደልሏቸው አትችሉም፤ መላ ህይወታቸውን ገንዘብ በማከማቸት አያጠፉምና፡፡ ለእነሱ ጠቅላላ ህይወትን ገንዘብ ለማከማቸት ሲባል ማባከን እብደት ነው፡፡ ሰውየው ሲሞትኮ ገንዘብ አብሮት አይሞትም።ይህ ፍፁም እብደት ነው። ደስተኛ ካልሆናችሁ በስተቀር ይህ እብደት አይታያችሁም።

ሰዎች ደስተኛ ከሆኑ የህብረተሰብ ጠቅላላ ቅርፅም ይቀየራል። ይህ ህብረተሰብ በስቃይ ነው የሚኖረው። ለዚህ ህበረተሰብ ስቃይ ትልቅ ኢንቨስትመንት ነው።ልጆቻችንን ስናሳድግ ከመጀመሪያው ጀምሮ ወደ ስቃይ እንዲያደሉ እናደርጋቸዋለን፡፡ ስለዚህ ሁልጊዜ የስቃይን መንገድ ይመርጣሉ፡፡

ሁለም ሰው ማለዳ ከዕንቅልፉ ሲነሳ ምርጫ አለው። ንጋት ላይ ብቻ አይደለም በእያንዳንዱ ቅፅበት የስቃይን ወይም የደስታን መንገድ የመምረጡ እድል አለ፡፡ ይሁንና ዋጋ ሰላለው ሁልጊዜ የስቃይን መንገድ ትመርጣላችሁ:: ልምዳችሁ የዘውትር ተግባራችሁ ሆኗልና ሁልጊዜ ስቃይን ትመርጣላችሁ። በመሰቃየት ብቁ ሆናችኋል፤ መንገዳችሁ ሆኗል፡፡ አዕምሮአችሁ የመምረጥን እድል ሲያገኝ ወዲያውኑ ወደ ስቃዩ መንገድ ያደላል::

ስቃይ ቁልቁለት፤ ደስታ ደግሞ ዳገት ይመስላሉ። ደስታ የማይደረስበት ተራራ ቢመስልም ግን እውነት አይደለም:: እውነታው ከዚህ ተቃራኒ ነው። ደስታህ ቁልቁለት ነው ፤ ስቃይ ደግሞ ዳገት ነው። ስቃይ የማይደረስበት አስቸጋሪ ነገር ቢሆንም እናንተ ደርሳችሁበታል፤ የማይቻለውን ችላችኋል፤ ምክንያቱም ስቃይ ኢ -ተፈጥሯዊ ነውና፡፡ ሁሉም ሰው ስቃይን ባያፈልግም ሁለም ሰው እየተሰቃየ ነው::

ህብረተሰቡ በዚህ ረገድ ትልቅ ስራ ሰርቷል:: ትምህርት ፣ ባህል፣ የባህል ተቋማት ፣ ወላጆች፣ መምህራን. . . ሁሉም ትልቅ ስራ ሰርተዋል፡፡ ከደስታ ፈጣሪዎች፣ የሚሰቃዩ ፍጥረታትን አስገኝተዋል፡፡ ሁለም ሰው ሲወለድ ደስተኛ ሆኖ ነው፤ ሁሉም ህፃን ሲወለድ አምላክ ሆኖ ነው:: ሁሉም ሰው ሲሞት ደግሞ እብድ ሆኖ ነው:: ህፃንነትን መልሶ ማግኘት፣ መልሶ መያዝ የእናንተ ሃላፊነት ነው:: በድጋሚ ህፃን መሆን ከታደሉ ስቃያ ይጠፋል፡፡


ከአንድ ነገር ጋር ስትዋሃዱ ደስተኛ ትሆናላችሁ፡፡ ራሳችሁን እንድ ነገሩ: ስትነጥሉ (ከደስታ ቢሆን እንኳን) ትሰቃያላችሁ::ስለዚህ ቁልፉ ይህ ነው:: የራስ ኩራትን (ለራስ የሚሰጥ ከፍተኛ ግምትን) ይዞ መነጠል የሁሉም ስቃይ መነሻ ነው::

ህይወት ከምታመጣው ነገር ጋር አንድ ሆናችሁ ፣ ራሳችሁን በመተው የምትፈስሱ፣ ከሚመጣው ነገር ጋር የምትዋሃዱ ከሆነ ግን ሁሉም ነገር አስደሳች ይሆናል፡፡

ምርጫው እለ፡፡ እናንተ ግን ምርጫ መኖሩን አላስተዋላችሁም:: የተሳሳተውን መንገድ መምረጥን ልማዳችሁ አድርጋችሁታል፡፡ የቀረ ምርጫ መኖሩን አታስተውሉም::

ንቁ ሁኑ:: የስቃይን መንገድ በመረጣችሁ ጊዜ ሁሉ ምርጫውን የመረጣችሁት እናንተ መሆናችሁን አትዘንጉ:: ‹‹ምርጫውን የመረጥኩት እኔ ነኝ፣ ሃላፊነቱም የእኔ ነው፣ ይህ ሁሉ የእኔ ስራ ነው።"ብላችሁ ማሰባችሁ በራሱ ጠቀሜታው ላቅ ያለ ነው:: ይህን ስታደርጉ ወዳያወኑ ልዩነቱ ይገለፅላችኃል:: የአዕምሮአችሁ ባህርይ ይለወጣል። ወደ ደስታ የሚወስደው መንገድ ቀላል ይሆንላችኋል፡፡

አንዴ ምርጫችሁ ይህ እንደሆነ ካወቃችሁ ሁሉም ነገር ጨዋታ ይሆናል:: ስለዚህ መሰቃየት ከፈለጋችሁ ተሰቃዩ፡: ያን ምርጫ የራሳችሁ መሆኑን በመገንዘብ ምንም ወቀሳ አታቅርቡ። ሀላፊነቱ የሌላ የማንም አይደለም ፤ ይህ የራሳችሁ ድራማ ነው:: ያንን የስጋት መንገድ ከመረጣችሁ፣ በዚህ የስቃይ ህይወት ውስጥ ማለፍ ከፈለጋችሁ
ምርጫው ፣ ጨዋታችሁ የራሳችሁ ነው ማለት ነው:: የምትጫወቱት እናንተ ናችሁ፡፡ እናም በደንብ ተጫወቱት ከዚህች ቅፅበት ጀምሮ ግን ደስተኛና በሀሴት የተሞላ ለመሆን ደጋግማችሁ ጣሩ::

ደራሲ ኦሾ
ምንጭ አካለ አእምሮ
@Zephilosophy
@Zephilosophy
4.3K views06:21
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-06 21:27:40 ደስተኛ አለመሆንን ለምን እንመርጣለን?

የሰው ልጅ ከተጋፈጣቸው ውስብስብ ችግሮች መሃል እንዱ ይህ ነው፡፡ በንድፈ - ሃሳብ ደረጃ ሳይሆን በጥልቀት መመርመር አለበት። ይህ ጉዳይ እናንተንም የሚመለከት ነው:: ሁሉም ሰው ወደ ሃዘን፣ ድብርት፣ ስቃይ የሚወስደውን የተሳሳተ መንገድ ይመርጣል፡፡ ለዚህም ቀድመው የታወቁ ምክንያቶች አሉ።

የመጀመሪያው በጣም አስፈላጊ የሆነ ሚና የሚጫወተው የሰው ልጆች አስተዳደግ ነው:: «ደስተኛ ካልሆናችሁ አንድ ነገር ታገኛላችሁ፡፡ ደስተኛ ከሆናችሁ፤ ሁልጊዜ አንድ ነገር ታጣላችሁ» የሚል አስተዳደግ፡፡

አንድ ህፃን ይህን ልዩነት የሚገነዘበው ከመጀመሪያው ጀምሮ ነው:: ደስተኛ ባልሆነ ጊዜ ሰው ያዝንለታል ፤ ስለዚህ ርህራሄን ያገኛል፡፡ ሁሉም ሰው ሊወደው ይጥራል፤ ስለዚህም ፍቅርን ያገኛል፡፡ ከዚህ ያበልጥ ደግሞ ትኩረታቸውን በእሱ ላይ ያደርጋሉ፤ ስለዚህም ትኩረትን ያገኛል። ትኩረት ልክ እንደ አልኮል የሚያነቃቃ የራስ ኩራት ምግብ ነው:: ሃይል ይሰጣችኋል፤ እንድ የሆነ ሰው የሆናችሁ ያህል ይሰማችኋል፤ ስለዚህም ትኩረት ማግኘት በእጅጉ ትፈልጋላችሁ::

አንድ ሰው ሲመለከታችሁ አስፈላጊ የሆናችሁ ያህል ይሰማችኋል፡፡ ማንም ስው ዞር ብሎ የማይመለከታችሁ ከሆነ ግን እዚያ የሌላችሁ ያህል፣ ምንም እንዳልሆናችሁ ይሰማችኋል፡፡ ሰዎች ሲመለከቷችሁ፣ ሲጠነቀቁላችሁ በሃያል ትሞላላችሁ! ትነቃቃላችሁ፡፡
በማንኛወም ግንኙነት ውስጥ ለራስ የሚሰጥ ግምት (የራስ ኩራት) አለ:: ሰዎች ትኩረት በሰጧችሁ ልክ የራስ ኩራታችሁ ይጨምራል፡፡ ማንም የማያተኩርባችሁ ከሆነ የራስ ኩራታችሁ ይጠፋል:: ሁሉም ሰው ሙሉ በሙሉ የረሳችሁ ከሆነ እንዴት የራስ ኩራት ሊኖር ይችላል? እናንተ የገዛ ራሳችሁ እንደሆናችሁ እንዴት ሊሰማችሁ ይችላል።

ስለዚህም የማህበረሰቦች፣ የማህበራት፣ የክለቦች አስፈላጊነት ይመጣል፡፡ በመላው ዓለም ብዙ ክለባት አለ፣የክለባቱና የማህበራቱ ቀጥር በሚሊዮን የሚቆጠር ነው:: እነዚህ ማህበራትና ክለባት የተፈጠሩት በየትኛውም መንገድ ትኩረት ለማያገኙ ሰዎች ትኩረት ለመስጠት ነው::
አንድ ህፃን ከመነሻው ጀምሮ ይህን ፖለቲካ ሊማር ነው የሚያድገው:: «የተሰቃየህ ከመሰለህ ይሄን ጊዜ ይታዘንልሃል፧ ሁሉም ሰው ትኩረቱን ወዳንተ ያዞራል» የማለት ፖለቲካ:: የታመምክ ምሰል - ይሄኔ እስፈላጊ ሰው ትሆናለህ:: አንድ ህመምተኛ ህፃን አምባገነን ይሆናል ፤ መላው ቤተሰብም ትዕዛዙን ያከብራል - እሱ ያለው ሁሉ ደንብ ነው::

ደስተኛ ሲሆን ግን የሚያደምጠው የለም።ጤናማ ሲሆን የሚጨነቅለት አይኖርም፤ ፍፁም ሲሆን ማንንም ትኩረቱን አይሰጠውም፡፡ በዚህም ከመጀመሪያ ጀምሮ የህይወትን፣የሀዘንን የስቃይ፣ የጨለመ መንገድ መምረጥ እንጀምራለን:: ይሄ አንድ እውነታ ነው።

ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ ከዚሁ ጋር የሚያያዝ ነው:: ደስተኛ ስትሆን የመፈንደቅ፣ የሃሴት ስሜት ሲሰማችሁ ሁሉም ሰው ይቀናባችኋል፡፡ ቅናት ማለት ሁሉም ሰው የወዳጅነት ሳይሆን በተቃራኒ ስሜት ይመለከታችኋል ማለት ነው:: ሁለም ሰው ጠላታችሁ ይሆናል፡፡ ስለዚህም በሰው ዘንድ ጥላቻን ላለማትረፍ ደስተኛ አለመሆንን፣ አለመሳቅን ትመርጣላችሁ::


ሰዎችን ሲስቁ ተመልከቷቸው:: በተጠና ሁኔታ ነው የሚስቁት፡፡ ሳቃቸው ከሆዳቸው፣ ከማንነታቸው ጥልቀት የሚወጣ አይደለም:: በመጀመሪያ ይመለከቱዋችኋል ! ከዚያም ያመዛዝናሉ. . . ቀጥሎ ይስቃሉ፡፡ ሲስቁም እስከተወሰነ ደረጃ ነው . ሰዎች መታገስ እስከሚችሉበት፣ እስከማያገለዋቸው፣ የቅናት ስሜት እስከማይፈጥሩበት መጠን ድረስ፡፡

ፈገግታዎቻችን ሳይቀሩ የተመጠኑ ናቸው፡፡ ሳቅ ጠፍቷል! ሃሴት በፍፁም የማይታወቅ ሆኗል፤ መፈንደቅ አያፈቀድም፡፡ እየተሰቃያችሁ ከሆነ ማንም ሰው አብደዋል ብሎ እያስብም፡፡ መፈንደቅ፣መደነስ ሲያምራችሁ ግን ሁሉም ሰው እብድ እንደሆናችሁ ያስባል፡፡

ዳንስ የተወገዘ ነዉ ! ዘፈን ተቀባይነት የለውም፡፡ ደስተኛ ሰው ስናይ አንድ የሆነ ችግር እንዳለበት እናስባለን፡፡ የምንኖረው በምን አይነት ህብረተሰብ ውስጥ ነው? ሰው ሲሰቃይ ሁሉም ነገር መልካም እንደሆነ ይታሰባል፡፡ ህብረተሰቡ በመላ ከሞላ ጎደል በስቃይ ውስጥ ያለ ነውና የሚሰቃየው ሰው ከህብረተሰቡ ጋር ይጣጣማል ፤ እንዱ የህብረተሰቡ አባልም ይሆናል፡፡ አንድ ሰው ሲፈነድቅ ስናይ እብድ እንደሆነ እናስባለን፤ የእኛ ወገን እንዳልሆነ እናስባለን ፤ እንደዚያም ሆኖ የቅናት ስሜት ይሰማናል፡፡

ስለምንቀና እንቃወመዋለን፡፡ ስለምንቀና በተቻለን አቅም ወደ ቀድሞ ሁኔታ - እንዲመለስ እንጥራለን፡፡ የቀድሞ ሁኔታው ትክክለኛ እንደነበር እናስባለን:: የስነ እዕምሮ ተመራማሪዎችና ሃኪሞችም ያ ሰው ወደ ትክክለኛ ሁኔታ እንዲመለስ ይረዱታል፡፡

ህብረተሰቡ ደስታን አይፈቅድም:: ፍንደቃ ታላቁ እብዮት ነው፡፡ እደግመዋለሁ ፤ ፍንደቃ ታላቁ አብዮት ነው:: ሰዎች ደስተኛ እንዲሆኑ መላው ህብረተሰብ መለወጥ አለበት፤ ምክንያቱም ይህ ማህበረሰብ በስቃይ ውስጥ ያለ ነውና::

ሰዎች ደስተኛ ከሆኑ ለጦርነት ወደ ቪየትናም ወይም ወደ ግብፅ ወይም ወደ እስራኤል ልትወስዷቸው አትችሉም:: በፍጹም! ይህን ሃሳብ ስታቀርቡሏቸው የማይረባ ሃሳብ ነው!» ብለው ይስቁና ያጣጥሉዋችኋል፡፡

ይቀጥላል..

ደራሲ ኦሾ
ምንጭ አካለ አእምሮ


@Zephilosophy
@Zephilosophy
3.8K views18:27
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-05 18:02:07 ጭፍን እምነትን አውልቃችሁ ጣሉ

ምንጭ ፦ የፍልስፍና ሀሁ
ፀሀፊ ፦ በላይ ደስታ

መሪር ሀሳቦችን ለማንሳትና ለመወያየት ካልደፈራችሁ? ሗላ ቀር የሆነውና ከቤተሰቦቻችን የወረስናቸው ልማዶችና አስተሳሰቦች እርስ በእርስ አባልተው ይጨርሱናል፡፡ ስለእውነት ነው የምላችሁ፣ እንደሰው ተፈጥረን እንደድመት የምናልፍ ከንቱዎች እንሆናለን። በየጎጡ ጎራ እየሰራን እንለያያለን:: እምነታችን ሁሉንም የዓለም ህዝብ ካልቀየረ ብለን አክራሪነት ውስጥ ተቻኩለን እንወተፋለን። በንቁ ሀሳባችን ካልተመራን፣ ያው መሪያችን ልማድ ሆኖ መቅረቱ ግልጽ ነው፡፡

በሀሳብ፣ ልማድና እምነት መካከል ሰፊ ርቀት አለ፡፡ በሀሳቡ የሚያምን ሰው ይልቃል። በእምነቱ የሚያምን ግን አዲስ ሀሳብ አይፈጥርም፡፡ ቀድሞ የተፈጠረውን ስርዓት ተቀብሎ ወደ ልጁ ሰፈር ያደርሳል። እንደዱላ ቅብብል ማለት ነው። የዱላ ቅብብል ተወዳዳሪ ስለዱላው ምንም የሚያስበው የለም፡፡ ዱላው ብረት ይሆን እንጨት አያስብም። የሱ ስራ፣ ከኋለኛው አጋሩ የተቀበለውን ዱላ ይዞ ወደ ፊት መሸምጠጥ ብቻ ነው። ከዚያ ከፊቱ ለሚጠብቀው ሯጭ እስኪያቀብል ሳያባራ ይሮጣል፡፡

በእምነትና በባህላዊ ስርዓት ውስጥ የሚኖሩ ህዝቦችም እንዲሁ ናቸው። ከአባቶች የወረሱትን እምነትና ትዉፊት የሙጥኝ ብለው ወደፊት ይሮጣሉ። ለቀጣዩ ትዉልድ እስኪያስረክቡና ህይወታቸው እስኪያልፍ የሚያስቡት አዲስ መንገድ አይኖርም፡፡ አእምሯቸው በጥልቀት እንዲያስብ ፈቃድ አይሰጡትም፡፡ ለዚህ ነው፣ ብዙ እምነት ውስጥ የሚኖሩ ህዝቦች ስልጣኔን የሚሸሹት።

እምነትን ብቻ የሁሉ ነገር ምንጭና መንገድ አድርጎ የሚቆጥር ህዝብ ያየለበት ማህበረሰብ ወይም ሀገር፣ ኋላቀርነቱ እዚያው ኋላ እንደቀረ የሚኖር ይሆናል። ትልቁ ፈተና ደግሞ፣ እምነት ውስጥ የተኛ ህዝብ ኋላ ቀርነቱን እንደጸጋ ማየቱ ነው፡፡ የትኛውም የኑሮ ገጠመኝ ማለትም ድህነት፣ አለመማር፣ አለማወቅ፣ የበታች መሆን፣ ስደት፣ በሽታ፣ ጦርነትና መሰል እልፍ ወረርሽኞች እግር ተወርች አስረውት ጭምር አያዝንም፡፡ እልህ ውስጥ አይገባም፡፡ ለምን እንዲህ ተፈተንኩ ማለትን አይፈልግም፡፡

"የፈጣሪ ፈቃድ ነው ብለን ዝም አልን” በሚል የተለመደ ዋሻ ውስጥ ይደበቃል፡፡ ይህን ለማረጋገጥ፣ ዛሬም ወደ ራሳችን ማየት ነው፡፡ እየወደቅንም ፈጣሪ የምንለውን ሀይል አመስጋኞች ነን። ብንራብ፣ ብንጠማ፣ ፈተናዎች ቢደራረቡብን፤ ጦርነት ውስጥ ብንናጥ ሁሌ እያመሰገንን እናልፋለን፡፡ ለምን በዚህ ሁኔታ ውስጥ ገባን? እንዴትስ መውጣት እንችላለን? ብለን አንጠይቅም። ምክንያቱም "ሁሉም ነገር የፈጣሪ ፈቃድ ነው” በሚለው ራሳችንን እናታልላለንና።

መፍትሔ የምንጠብቀው ከጸሎትና ከፈጣሪ ነው። እጆቻችንን ወደ መሬት አዙረን መዶሻና አካፋ አንይዝም፡፡ ምንም ሳንይዝ አየሩ ላይ ወደ ሰማይ አንጋጠን እንለምናለን። በዛ ጥፋታችን ለፈረሰ ቤት ጥገና የምንጠይቀው ፈጣሪን ነው:: ይህ መንገድ ለሁሉም ነገር መፍትሄ አይሆንም፡፡

ፍጹም አማኝ ሆኖ የተሰባሰበ ህዝብ ስልጣኔ የማይሰራው ለምን እንደሆነ ግልጽ ነው። የተሰባሰበው ሰማያዊ መንግስትን እያሰበ እንጂ፣ በእጁ የጨበጠውን የምድር ህይወት ከግምት አያስገባም፡፡ እየኖረ በመሆኑ ግን፣ የግድ መንግስት ይፈጥራል። የሚፈጥረው የመንግስት አይነት ግን ምድር ላይ ያለውን እውነት ያማከለ አይሆንም፡፡ የተዘበራረቁ መልኮች ይኖሩታል፡፡

የራሱን የህይወት መንገድ እንዲፈጥር ነጻነትን ያልተማረ ህዝብ፣ ጥያቄ አይጠይቅም፤ የተለየ ሀሳብም አያስብም፡፡ ሀሳብ የሚያድገው ደግሞ በፍልስፍና ነው ! በፍልስፍና አስተሳሰብ ያልተገራ ህዝብ በነጻነት ውስጥ ሆኖ የእውቀት ልዩነት የሚፈጥር የሀገር ቅርጽ አይወልድም፡፡ በጥንት ልማድና አሁን ባለው የሀገር ቅርጽ መሃል የተለየ ማንነት አይኖርም።

በልማድና በእምነት ውስጥ ብቻ የሚኖር ህዝብ አንደኛው ችግር ይኼው ነው፡፡ ከዘመን መለወጥ ጋር የሚያድግ ርዕዮት አይፈጥርም፡፡ የእርሱ ጉዳይ ዶግማዎችን እንዳሉ ማስቀጠል ነው፡፡ የባህል ዱላ ቅብብል ላይ የተገደበ ስርዓት ነው የሚፈጥረው፡፡ ባህል ግን ብቻውን ስልጣኔ አይሆንም ፤ ስልጣኔንም አያመጣም፡፡ ባህል የቡድን ባህሪ እንጅ የግለሰብ አስተሳሰብ አይደለም፡፡ የሳይንስ ወይም የፍልስፍና ተግባር ደግሞ ዶግማዎችን ብቻ ማስቀጠል አይደለም።

ኢትዮጵያ ዘመናትን ያስቆጠሩ ሥነቃላዊና የፅሁፍ ፍልስፍናዎች ባለቤት ናት። ከአስራ ሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በፊት፣ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች በተለየ መልኩ በርከት ያሉ የፍልስፍና ስራዎችን በመስራት በቀዳሚነት የምትጠቀሰው በጥንታዊው የግእዝ ቋንቋ ከተጻፉት የፍልስፍና ስራዎቿ መካከል ከፊሎቹን በትውልድ ካናዳዊ፣ በምርጫ ደግሞ ኢትዮጵያዊ የሆነው ፕሮፌሰር ክላውድ ሰምነር ወደ እንግሊዝኛ ቋንቋ በመተርጎም፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲታወቁ እድርጓል። ሌሎች በርካታ በግዕዝና በአረብኛ ቋንቋዎች የተፃፋ የጽሁፍ ስራዎች በጥንታዊ ቤተእምነቶችና ቤተመዛግብት ውስጥ ተቀምጦ አንስቶ የሚመረምራቸውን የሀገራቸውን ጠቢብ በመጠባበቅ ላይ ናቸው።

ፍልስፍና በጥቅሉ የተጻፉትንና በቃል ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፋትን የማህበረሰብ ወጎች፣ ልማዶች፣ ጥበቦች፣ የእውቀት ዘርፎችንና አስተሳሰቦችን፤ በግለሰብ ፈላስፋዎች፣ በአንድ ዘመን ተሰርተው በጽሁፍ የተላለፉትን ስራዎች የሚመለከት ምጡቅ የጥበብ ዘርፍ ነው። በቃል ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፉ ማኅበረሰባዊ ፍልስፍናዎች፤ በተረትና ምሳሌ፣ በምሳሌያዊ አነጋገሮች፣ በዘይቤዎች፣ በቅኔዎችና በወጎች ሊገለጡ ይችላሉ።

ሀገራችን ኢትዮጵያ፣ ገና ያልተጠኑ የበርካታ ጥንታዊ ስነ ጽሁፎች ባለቤት ናት፤ ማጥናትና መመርመር አቅቶን ሌሎች አጥንተው የቅጂ መብቱን ከመውሰዳቸውና የታሪክ ክፍትት ተፈጥሮ በመጪው ትውልድ ተወቃሾች ከመሆናችን ሰፊት፣ ከትምህርት ቤት ጀምሮ፣ በወጣቶች አዕምሮ ውስጥ የምርምር ሀሳቦችን በማንሳትና የዘርፉ ምሁራንም ተገቢውን ጥናትና ምርምር በማካሄድ፣ በየደረጃው ያሉ የትምህርት ተቋማትም፣ የፍልስፍና ጥበብን በትምህርትና በምርምር ስራቸው ውስጥ በማስገባት፣ ወጣቶች ከተለመደው አስተሳሰብ ወጥተው፣ በተለያዩ የፈጠራ አስተሳሰቦች ውስጥ እንዲመሰጡ ማበረታት ወቅቱ የሚጠይቀው አቢይ ስራ ነው፡፡

እየኖርን ባለነውም ሆነ ወደፊት በምንኖረው ዘመን፣ ለአንድ ሃገር አስፈላጊና ወሳኝ ነገሮች ናቸው ተብለው ከሚታመንባቸው ጉዳዮች መካከል፤ ለዘመኑ የሚመጥን የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂና የፈጠራ ውጤት ሊያመነጭ የሚችል ተመራማሪ ትውልድ ማፍራት መቻል ነው፡፡ አዳዲስ የሳይንስ ግኝቶችንና የተራቀቁ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ሊያመነጩ የሚችሉ ጠይቂ አዕምሮዎች እንዲፈጠሩ ደግሞ፣ በነባሩ ባህላዊ አስተሳሰብ ውስጥ ያሉ ዜጎች፣ አዲሱ ትውልድ፣ የምርምር ሀሳቡን በሚያምንበት መንገድ ያለገደብ፣ እንዲያራምድና እንዲያዳብር መፍቀድ መቻል አለባቸው።

@Zephilosophy
@Zephilosophy
5.9K views15:02
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-04 22:23:05 ላኦ ዙ (Laozi) ማን ነው?

ምንጭ ፦ የፍልስፍና ሀሁ
ፀሀፊ ፦ በላይ ደስታ

ከመጀመሪያዎቹ የቻይናውያን ፈላስፎች አንዱ፣ የታኦይዝም ትምህርቶች መሥራች ላኦ ዙ ነው ተብሎ ይታሰባል፡፡ በቁሳዊ ቅንጣቶች ላይ የተመሰረቱ የሚታዩ የተፈጥሮ ክስተቶች የእርሱ አስተምህሮ መሰረቶች ናቸው፡፡ እንደተገለጸው፣ ላኦ ዙ የቻይና ጥንታዊ ፈላስፋ እና የታኦይዝም መስራች አባት ነው፡፡ “ላኦ ዙ” የሚለው ቃል የእንግሊዝኛ ትርጉም ጥንታዊ ፈላስፋ እንደማለት ነው፡፡ "የጥንቱ ሕፃን" ተብሎም የሚታወቅ እንደሆነ ተጽፏል። በጥልቅ ጥበቡና በታዋቂ ተጫዋችነቱ በታኦኢስት የቻይና ነገስታት ዘንድ በሰፊው ይታወቃል፡፡

ስለ ላኦ ዙ ታሪካዊ ሕይወት እምብዛም የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ የሚታውቀው ነገር ቢኖር፣ ትክክለኛ ስሙ ሊ ኸር ሲሆን፣ በደቡባዊው የዙፋን ዘውድ ቤተሰብ ውስጥ የተወለደ መሆኑ ነው፡፡ በእድሜ ትልቅ ሰው በነበረበት ጊዜ፣ በመንግሥታዊው ቤተ መንግሥት ግቢ ውስጥ የቤተ-መጻህፍት ባለሙያ በመሆን ከማገልገሉ በተጨማሪ አነስተኛ የመንግስት ቦታን ይዞ እንደነበር ተጽፏል፡፡

በአጠቃላይ ሲታይ በቻይና ንጉሳዊ አገዛዝ ታሪካዊ ሂደት ውስጥ፣ የታኦይዝም ፍልስፍና አንደኛው መንገድ፣ ሀገርን ማስተዳደር ጥበብ ላይ የተመሠረተ ነው። ከሰራቸው ታዋቂ የጥበብ ስራዎች መካከል፤ ግዛትን ለማስተዳደር የተገለጹ አራቱ ጥበቦችንና መንገዶችን የተመለከቱ ነበሩ። እነሱም፣ የንጉሠ ነገሥት መንገድ፣ የንጉሠ ነገሥታዊ መንገድ፣ የንጉሳዊ መንገድ እና የሄግሜኒንግ መንገድ የተሰኙት እንደሆነ ተዘግቧል።

በማሰላሰል ላይ የተመረኮዘ፣ ሙሉ በመሉ ኦፊሴላዊ ያልሆነ ዶክትሪን የሚያስተምረው ላኦ ዙ፣ በዘመናዊው አነጋገር ምስጢራዊ እና ጸጥተኛ መሆንን የሚያስተምር አስተሳሰብ እንደነበረው አሁን ካሉ የጽሑፍ ምንጮች ለመረዳት ተችሏል። “ሰው በራሱ ውስጥ ካሉ ውሸቶች ሁሉ ራሱን በማውጣት እውነትን ያገኛል” የሚለው አስተሳሰቡ የሚታወቅበት አስተሳሰቡ ነው:: ላኦዙ በአስተምህሮው እንዲህ ሲል ተናግሯል “ከሰማይና ከምድር በፊት የነበረ ማለቂያ የሌለው ፍጡር አለ፡፡ እንዴት የማይደፈር፣ እንዴት የተረጋጋ! እሱ ብቻውን የሚኖር እና የማይለወጥ ነው። ሁሉንም ነገር ያንቀሳቅሳል፣ ግን አይጨነቅም። እንደ ሁለንተናዊ እናት ልንቆጥረው እንችላለን፡፡ ስሙን አላውቅም፡፡ ታኦ ብዬ እጠራዋለሁ” በማለት አስተምሯል፡፡

የፍልስፍና እሳቤዎቹ

"እኔን ማወቅ ከፈለግህ፣ በልብህ ውስጥ አንተነትህን ተመልከት።"

"አንድ ሀገር በጥበብ ከተመራች ኗሪዎቿ ባላቸው የረኩ ይሆናሉ፡፡ "

"የሰውን ልጅ ለመረዳት አለምን ተረዳ፣ አለምን ለመረዳት ደግሞ ሰማየ ሰማያትን እወቅ።"

"ሙሉ ለመሆን ከፈለግህ ጎደሎ ለመሆን ፍቀድ፣ ቀጥ ያለ ለመሆን ካሻህ ጎባጣ ለመሆን ፍቀድ፣ እንዳትጠግብ ከፈለግህ ለመራብ ፍቀድ፣ ለመወለድ ከፈለግህ ለመሞት ፍቀድ፣ እንዲሰጥህ ከፈለግህ ያለህን ስጥ።"

"አብረቅርቆ ለመታየት የሚሞክር የራሱን ብርሀን ያደበዝዛል፣ ለራሱ የማይገባውን ክብር የሚሰጥ እውነተኛ ማንነቱን ያጣል፡፡"

"ሁሉም ነገር የተገኘው ከመሆን ነው፣ መሆን እራሱ የተገኘው ደግሞ ካለመሆን ነው፡፡"

"ጥሩ ተጓዥ የተወሰነ መድረሻ የለውም፣ ጥሩ አርቲስት ምእናቡ ወደ ወሰደው ይሄዳል፤ ጥሩ ሳይንቲስት አእምሮውን ለሆነውና ለሚሆነው ሁሉ ክፍት ያደርጋል፡፡"

"መደበኛ ህልሞችህንና ከንቱ ሀሳቦችህን ተዋቸው፣ አለም ራሷን ታስተዳድራለችና፡፡"

"ህጉን ስትተወው ሰዎች ሀቀኛ መሆን ይጀምራሉ፣ ምጣኔ ሀብትን ስትተወው ሰዎች ሀብታም መሆን ይጀምራሉ፣ ሀይማኖትን ስትተወው ሰዎች በመንፈስ መርካት ይጀምራሉ፡፡"

"ሁሉም ነገር እንደሚለወጥ ከተረዳህ፣ እንዲኖር የምትፈልገው ነገር አይኖርም።"


"ሁለት ተቃራኒ ነገሮች ሲጋጩ አሸናፊነት የምትሄደው መረታትን ወደተቀበለው ጎራ ነው።"

"እውነተኛ ቃላት ማራኪ አይደሉም፣ ማራኪ ቃላትም እውነተኛ አይደሉም።"

"አለም ብጽእት ናት፣ ልትሻሻል አትችልም፤ ከነካሃት ታወድማታለህ፣ እንደ እቃ ከቆጠርሀት ታጠፋታለህ።"

"ከማጣት ብዙ ይገኛል፤ ከማግኘት ብዙ ይታጣል፡፡"

"ሀያልነት የፈለገውን ያህል ምክንያታዊ ቢሆንም፣ አጥቂውን መልሶ ማጥቃቱ አይቀርም፡፡"

"ሁሉም ወንዞች ከተራሮች ፈልቀው ወደ ባህር የሚፈሱት፣ ባህሩ ዝቅ ብሎ ስለሚገኝ ነው።"

"ዳዋው መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው ዘላለማዊ ነው፡፡"

"ታላቁ ዳዋ ወደ ሁሉም ይፈሳል፣ ሁሉም ነገሮች ከእርሱ የተፈጠሩ ናቸው፤ ይሁን እንጂ አልወለዳቸውም፡፡"

"ዳዋውን ማእከል ያደረገች፣ ወደ ፈለገችው ቦታ ያለስጋት ትሄዳለች፡፡"

"የሰው ልጅ በአምላኩ ስራ ጣልቃ ይገባል፣ ሰማይ ይቆሽሻል፣ መሬት ሀብቷ
ያልቃል፣ ሚዛኑ ይዛባል፣ ፍጥረታትም ይጠፋሉ፡፡"


"የጦር መሳሪያዎች በበዙ ቁጥር፣ የሰዎች ደህንነት ስጋት ላይ ይወድቃል፣
ለዜጎች ብዙ ድጋፍ ባደረግህ ቁጥር የሰዎችን ራስ የመቻል ጉዞ ይቀንሳል።"

"አንዲት ሀገር ትልቅ ሀይል ሲኖራት እንደ ባህር ትሆናለች፣ ሁሉም ወንዞች ወደ እርሷ ይፈሳሉ።"



@Zephilosophy
@Zephilosophy
3.8K viewsedited  19:23
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-03 22:25:49 መሲህ መሆን የሚችል መሪ አለን ወይ?
አንድ ሰው ስንት ነው?

ደራሲ እንዳለጌታ ከደራሲ ቡርሀን አዲስ ጋር ያደረገው እጅግ አስገራሚ ቆይታ

ክፍል-2
@Zephilosophy
@Zephilosophy
3.8K viewsedited  19:25
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-03 22:21:16 መሲህ መሆን የሚችል መሪ አለን ወይ?
አንድ ሰው ስንት ነው?

ደራሲ እንዳለጌታ ከደራሲ ቡርሀን አዲስ ጋር ያደረገው እጅግ አስገራሚ ቆይታ

ክፍል-1
@Zephilosophy
@Zephilosophy
3.5K viewsedited  19:21
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-03 07:30:36 ኮንፊሺየስ ማን ነው?

ምንጭ ፦ የፍልስፍና ሀሁ
ፀሀፊ ፦ በላይ ደስታ

ጥበበኛው ኮንፊሺየስ፣ በቻይና የፍልስፍና እና የጥበብ ታሪክ ውስጥ ትልቁን ስፍራ የያዘ ሰው እንደሆነ ይታመናል። እውነተኛ ስሙ ኮንግ ኩዊ የሆነው ኮንፊሺየስ፣ የመሳፍንት ዘር ከሆነው ከኮንግ ጎሳ፣ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ551 ተወልዶ በ479 የሞተ ስለመሆኑ ተጽፏል፡፡ ጥንታዊ የግሪክ መዛግብት እንደሚያስረዱት፣ የኮንፊሺየስ አባት፣ ሉ ለተባለቸው ግዛት ገዢ እንደነበርና በተወለደ በ3ኛ አመቱ እንደሞተም ተገልጽዋል፡፡ ከንፊሺየስ በ19 አመቱ ትዳር መስርቶ የአንድ ወንድ እና የሁለት ሴት ልጆች አባት ለመሆንም በቀቷል።

ኮንፍሺየስ ቤተሰብ ከመሰረተ በኋላ፣ በአስተማሪነት ስራ ተቀጥሮ ቤተሰቡን ማስተዳደር መጀመሩንና በአስተማሪነቱም ከአንደኛው ግዛት ወደሌለኛው ግዛት እየተዘዋወረ የጥበብን ስራን ሲያስተምር ስለመቆየቱ የተለያዩ ጸሀፊዎች ዘግበዋል፡፡ እየተዘዋወረ በሚያስተምረው ትምህርት የተሳቡ አያሌ ተከታዮችን ማፍራት ከመቻሉም በላይ፣ የሚያስተምረው የጥበብ ትምህርት በብዙዎቹ የሀገሬው ሰዎች ዘንድ ተቀባይነት ማግኘት ቻለ፡፡

በወቅቱ በነበረው አስተዳደር መዳከምና የባህል ውድቀት ተከትሎ፣ ኮንፊሺየስ የቻይና ህዝብ ከጥፋት መዳኛው ብቸኛው መንገድ ባህልንና ሞራልን በአግባቡ መስበክና ሙዚቃን ማስፋፋት እንደሆነ እምነት አደረበት::

ኮንፊሽየስ በ50 ዓመት እድሜው፣ ዞንግዱ በተባለ ግዛት ውስጥ በዳኝነት ስራ ተሰማርቶ እንደነበረ፣ በመቀጠል በጦር መሪ ሆኖ ህዝብን ከማስተዳደር በተጨማሪ፣ ህብረተሰቡ ተገቢውን ፍትህ እንዲያገኝ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ስራ እንደሰራ ተዘግቧል። ኮንፊሺየስ፤ ከጊዜ በኋላ በግዛቱ ከነበሩት ገዢዎች ጋር በሀሳብ ባለመስማማቱ ሀላፊነቱን በመተው፣ በተለያዩ ግዛቶች እየዞረ ማስተማሩን ቀጠለ:: ከቦታ ቦታ በሚንቀሳቀስበት ጊዜ በተለያዩ ግዛቶች የተመለከተው የአስተዳደር ስርአት መበላሸት፣ ከገዢዎች እውቀት ማነስ መሆኑን በመገንዘብ ቀሪ ዘመኑን የጥበብ መጻኅፍትን በማንበብ እና በመፃፍ ለማሳለፍ “ወደሉ” ተብላ ወደምትጠራዋ የትውልድ መንደሩ መሄድን መረጠ። ለረጂም ጊዜ በዚች መንደር ውስጥ የጥበብ ስራውን እየቀመረ ከኖረ በሗላ ከክርስቶስ ልደት በፊት በ479 ህይወቱ ማለፉ በውክፔዲያ ሚዲያ ተመዝግቦ ይገኛል።

ኮንፊሽየስ፣ የፍልስፍና ስራዎቹን በጽሁፍ አስፍሮ ስለማስተላለፉ የተዘገበ ታሪክ አልተገኘም። አስተምሯቸዋል ተብለው የሚታሰቡ ቁምነገሮች በተለይ የጥበብና የፍልስፍና እሳቤዎቹ፣ እሱ ባስተማራቸው ደቀመዛሙርት ተጽፈው ለትውልድ የተላለፉ ስለመሆኑ ግን በሰፊው ተዘግቧል፡፡ በተለይ “chunqiu” የተሰኘውና ከክርስቶስ ልደት በፊት፣ ከ722 እስከ 481 የነበረውን የቻይናውያን ታሪክ ተዘግቦበት የሚገኘው የታሪክ መጽህፍ ስለኮንፊሽየስ ጥበብና አስተምህሮ በሰፊው-- እንደዘገበው ተጽፏል።

የኮንፊሽየስ ትምህርቶች ከሀይማኖታዊ ይዘታቸው ይልቅ በተግባራዊ የህይወት ልምምድና በስነ ምግባር ላይ ያተኮሩ ነበሩ። የቆየውንና የተበላሸውን የቻይናዊያን ግብረገባዊ እውቀት በእርሱ ትውልድ ለመመለስና ለማስተካከል የደከመ ስለመሆኑ ተዘግቧል። በእርሱ እሳቤ፣ የመልካም ተግባራት ምሳሌ ናቸው በሚላቸው፤ ጻድቅነት፣ ሩህሩህነት፣ ጥበበኛነት፣ ትሁትነትና ታማኝነት ላይ በማተኮርና ማህበረሰቡን በማስተማር በግዛቱ የነበሩ ህዝቦች በተጠቀሱት እሴቶች እንዲቀረጹ በማድረጉ፣ የእርሱ አስተሳሰቦች አሁንም ድረስ በቻይናውያን ዘንድ ሰፊ መሰረት እንዲኖራቸው ያስቻለ ጥበበኛ ሰው ስለመሆኑ ብዙዎች ጸሀፊዎች ይስማማሉ፡፡

@Zephilosophy
@Zephilosophy
4.9K viewsedited  04:30
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-29 21:31:03 የወቅቱ አምላክ ሰው ሆኗል

ደራሲ እንዳለጌታ ከደራሲ አለማየሁ ገላጋይ ጋር ያደረገው እጅግ አስገራሚ ቆይታ

ክፍል-2
@Zephilosophy
@Zephilosophy
5.1K viewsedited  18:31
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-28 21:27:07 መጥፊያችን ደርሷል

ደራሲ እንዳለጌታ ከደራሲ አለማየሁ ገላጋይ ጋር ያደረገው እጅግ አስገራሚ ቆይታ

ክፍል-1
@Zephilosophy
@Zephilosophy
5.3K viewsedited  18:27
ክፈት / አስተያየት ይስጡ