Get Mystery Box with random crypto!

ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy

የቴሌግራም ቻናል አርማ zephilosophy — ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy
የቴሌግራም ቻናል አርማ zephilosophy — ፍልስፍና ለላቀ አስተሳሰብ Philosophy
የሰርጥ አድራሻ: @zephilosophy
ምድቦች: ያልተመደበ
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 19.37K
የሰርጥ መግለጫ

ፍልስፍና  እውነትን በመፈለግ- ሀሳዊ እምነቶችን በማጋለጥ እና ጭፍን አመለካከቶችን በጥበብ በመመርመር ወደ ላቀ አሰተሳሰብ ያሻግራል።
በዚህ ቻናል አለም ላይ ያሉ ፍልስፍናዎች ፤ ርዕዮት አለሞች ፤  ሀይሞኖቶች እና አስተሳሰቦች በነፃነት ይዳሰሳሉ።

Ratings & Reviews

3.67

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

2

3 stars

1

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 14

2022-09-19 16:34:10 ከፊታችን ባለው ሃይለኛ ጎርፍ አለመወሰድ ይቻላል?
(ተስፋኣብ ተሾመ)

እጅግ ፈታኝ ዘመን ላይ ተገኝተናል። አለማችን እጅግ  ፈጣን እና ኢ- ተገማች በሆነ ለውጥ ውስጥ እያለፈች ነው። የለውጥ ጎርፍ! ብዙሃኑን ጠራርጎ ሊያጠፋ የሚችል የለውጥ ጎርፍ!

ከሆነ ዘመን በፊት አንድ አባት ለልጁ የሚያስተምረው መስረታዊ ክህሎት ጠቃሚነቱ አመታትን ምናልባትም ክፍለ ዘመንን ይሻገራል።
ከሆኑ አመታት  በፊት ወላጅ ለልጁ ስለግብርና ወይም ስለማህበረሰቡ ህግጋት ቢያስተምር የትምህርቱ ጠቃሚነትና አስፈላጊነት ዘመናት የሚሻገር ይሆናል።

ከሆኑ አመታት በፊት የነበረ ትውልድ የአያቱን መንገድ በጥቂት ማሻሻያ ብቻ መድገም ይኖርበታል። መንግስታዊ አወቃቀር ለአመታት ተመሳሳይ ነበር፥ ኢኮኖሚው የሚመራበት መንገድ፥ ፖለቲካው፥ ወዘተ ኹሉ ተገማች ነበር።
ትላንት ጥቂት ክህሎቶችን በጥንቃቄ መማር ለነገ ትልቅ ስንቅ ይሆናል። ዛሬ ግን ይህ ነበር ሆኗል።

ልጆች ሳለን እጅግ ተፈላጊ የነበሩ የትምህርት ዘርፎች ድንገት ከገበያ ወጥተው የማይፈለጉ ሆነው ጠበቁን። ኢንጂነር ለመሆን እያለመ ተማሪ ቤት ያቀና ትምህርቱን ሲያገባድድ ህልሙ በነፋስ የሚወሰድ የገላባ ክምር ሆኖ ይጠብቀዋል። የተማረው የማይፈለገውን ሞያ ሆኖ ያገኘዋል።

በዚህ ዘመን ገበያው አክብሮ የተቀበላቸውን ሞያዎች ድንገት ገፍቶ ይጥላል። ቴክኖሎጂው ኢ ተገማች ነው። ፖለቲካው ይለዋወጣል።

በአባቶቻችን ዘመን መማር ትልቅ ቁም ነገር ነበር። ዛሬ ግን ሌላ ነው። የእድሜ ዘመን ተማሪ እንድንሆን ተፈርዶብናል። ወይም ተፈርዶልናል። ተምሮ ብቁ መሆን ብሎ ነገር የለም። በየቀኑ ለመማር የማይተጋ ይከሽፋል። ከዘመን እኩል ለመሮጥ በየጊዜው ራሱን የማያድስ ፥ ራሱን አፍርሶ የማይሰራ ሰው ይመክናል።

አለም በማያቋርጥ ለውጥ እያለፈች ነው። ለውጥ የተፈጥሮ ሕግ ነው። ይኽ ሁሉ ቢሆንም የዘመናችን ለውጥ ፈጣንነት እጅግ ፈታኝ ነው። ዛሬ ዋጋ የሚሰጠው ነገር ነገ ዋጋ አልባ ሆኖ ይጠብቀናል። ልጅ ሳለን የተከበረ የነበረ ሞያ አድገን ስንደርስበት ገበያው ገፍቶት እናገኛለን።

ምን በጀን? ባንወድ እንኳን ለውጥን መከልከል አንችልም። ይኽን ዘመን መዋጀት ከፈለግን በየለቱ ራሳችንን አፍርሰን ለመስራት መፍቀድ አለብን። በየቀኑ ራሳችንን ማስተማር ግዴታ  ነው። አዎ በየቀኑ ሳንሰለች መማር አለብን
ደግሞም እጅግ አስፈላጊ ክህሎቶችን እንለይ።
ዮቫል ሃራሬ 'ጥልቅ አሳቢነትን፥ ተግባቦትን፥ ፈጠራን፥ የማስተባበር ክህሎትን ተማሩ' ይላል።

ይህ በዘመናችን ማዕበል እንዳንወሰድ ይረዳናል።


@Tfanos
@Zephilosophy
@Zephilosophy
2.8K views13:34
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-12 20:59:39 ባለፉት ሁለት ዓመታት ገደማ የወረቀት ዋጋ ከልክ በላይ መናር የዕትመት ዋጋ ጣሪያ እንዲነካ አድርጎታል :: በዚህም የተነሳ የአንድ መጽሐፍ መሸጫ ዋጋ የዚያን ያህል እንዲጨምርና እንዲወደድ አድርጎታል :: የወረቅት ዋጋ መወደድ እና የዕትመት ዋጋ መናር በግላቸው ተበድረውም ይሁን አጠራቅመው ወይንም ንብረት ሽጠው አሳትመው ለነጋዴዎች ያከፋፍሉ የነበሩ ደራሲዎች ህልማቸውን እያጨለመ ነው :: በትንሽ ካፒታል ይንቀሳቀሱ የነበሩ መጽሐፍ ነጋዴዎች ከስራው ቀስ በቀስ ወጥተው እየመነመኑ ነው :: ከዚህ አልፎ ጥሩ ይንቀሳቀሳሉ የሚባሉ መጽሐፍ ሻጮችና አሳታሚዎችን በእጅጉ እየፈተነ ይገኛል ::

የመጽሐፍ ንባብ ባህላችን ገና ዳዴ እያለ ባለበት ሰዓት ይህን አይነት በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ የሆነ ድርብርብ ችግር ሲመጣበት ይበልጡኑ በቋፍ ላይ የነበረው የንባብ ባህላችንን ልክ እንደዳይኖሰር ከሀገራችን እንዳያጠፋው ስጋታችን ነው :: ይህ ነገር በምን መልኩ ሊስተካከል እንደሚችል ከጉዳዩ ጋር ቀጥታ ግንኘነት ያላቸው ሰዎች ከሚመለከተው አካል ጋር ተመካክረው አስተያየት ቢሰጡበትና መፍትኤ ቢሰጥበት መልካም ነው ብለን እናስባለን ::
4.9K views17:59
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-12 16:31:42 የተመስጦ  ዋናውን ገጽታ የበለጠ እያሰላሰልክ ስትሄድ፤ አንተ አለቃ፣ አእምሮህ ደግሞ ባሪያ ይሆናል፤ ሁልጊዜም መሆን ያለበት እንደዚህ ነው። አእምሮ ማለቂያ በሌለው መከራ ውስጥ የሚያሳልፍህ አስፈሪ ጌታ ቢሆንም፣ በተወሰነ መንገድ ከያዝከው ግን የምትፈልገውን ማንኛውንም - ነገር ልታደርግበት የምትችል ድንቅ ባሪያ ይሆናል። በዚህ ጊዜ በደንብ ልትቆጣጠረው ትችላለህ
ማሰብ ከፈለግክ ማሰብ ትችላለህ፧ ማሰብ ካልፈለግክ ደግሞ አታስብም፡፡ መሆን የሚገባውም እንደዚህ ነው፡፡

አሁን እጄን ማንቀሳቀስ ከፈለግኩ እጄን አንቀሳቅሳለሁ፤ ካልፈለግኩ ደግሞ አላንቀሳቅስም፡፡ ሰውነትህ ሁልጊዜ ዝም ብሎ የሚንቀሳቀስ ፡ ከሆነ፣ እብድ እየሆንክ ነው ማለት ነው። በአእምሮህ ላይም ተመሳሳይ ነገር እየሆነ ከሆነ ማለትም ማሰብህን ማቆም እየፈለክ ደጋግመህ በማይረቡ ሀሳቦች ውስጥ የምተዘፈቅ ከሆነ ፣ ሰዎች ሊያዩት በቀላሉ ስለማይችሉ እብድ ሆኗል አትባልም እንጂ ፣በበቂ  ሁኔታ ራስህን  ስትመለከት  ግን እያበድክ እንደሆነ ትገነዘባለህ።


አእምሮህ ተመስጦ አይወድም። መቀመጥና ማሰላሰል ስትፈልግ አእምሮህ ያንን እንዳታደርግ ሁሉንም ነገር ያደርጋል። በመጀመሪያ" ነገ ታደርገዋለህ” ይልሃል። “ነገ” የአእምሮ ጥልቅ ማታለያ ነው።ነገ ደግሞ በፍጹም አይመጣም፡፡ ሰዎች በሕይወታቸው ውስጥ ሊያደርጓቸው የሚገቡ ብዙ ነገሮችን “ነገ” ብለዋል፡፡ ለራሳቸው ደስታ ሳይቀር “ነገ” ይላሉ፡፡

ለተመስጦ ወይም ለማሰላሰል ስትቀመጥ የአእምሮ “ነገ” የሚለው  ዘዴ ካልትሳካና “አይ፣ ነገ አይሆንም፤ ዛሬ ለማድረግ ቆርጫለሁ” ካልክ፣ ሁለተኛ ዘዴውን ይሞክራል፡፡ ሳምንቱን ሙሉ ለማስታወስ ስትሞክር የነበረው የስልክ ቁጥር ድንገት ብልጭ ይልልህና ወደ  ስልክህ ትሮጣለህ ተመስጦውም ያበቃል፡፡

ይህንንም - ከተቋቋምክና ወደ ስልኩ ሳትሮጥ ተመስጦህን ከቀጠልክ፣ በሁለት እና ሶስት ደቂቃዎች ደርዘን የሚሆኑ የተለያዩ የሰውነትህ ክፍሎች በድንገት ያሳክኩሀል፡፡ ለዚህ ምክንያቱ አእምሮ ሰውነት ከተረጋጋ እርሱም እንደሚረጋጋ ስለሚያውቅ ነው፡፡ አእምሮ ይህ እንዲሆን ከፈቀደ ደግሞ ባርያ እንደሚሆን ያውቃል፡፡

ራስህን ብታስተውል፤ ስትቆም፣ ስትቀመጥና ስትናገር ሰውነትህ ምን ያህል አላስፈላጊ እንቅስቃሴዎችን እንደሚያደርግ ታያለህ። ሕይወትህን ስትመለከት ምናልባት ከግማሽ በላይ ጊዜ የወሰዱት እነዚህ ነገሮች እንደሆኑ ትገነዘባለህ፡፡ በሰውነትህ ውስጥ አንተ  ግድ የማትሰጣቸው ብዙ አላስፈላጊ ሀሳቦችና እንቅስቃሴዎች አሉ። ነገር ግን ሰውነት መረጋጋት ከቀጠለ፣ አእምሮም ቀስ በቀስ መርገብ ይጀምራል።

ይህን ማድረግ ከቻልክ፣ አእምሮ የሚያደርገውን  የማያቋርጥ ሩጫ ገታህ ማለት ነው።እናም አእምሮ በድንገት የተለየና ድንቅ ባሪያ ይሆናል።

ምንጭ የህይወት ኬሚስቲሪ(ሳዱጉሩ)
ተርጓሚ- ሀኒም ኤልያስ


@Zephilosophy
@Zephilosophy
4.8K viewsedited  13:31
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-12 16:27:54
3.7K views13:27
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-12 10:18:19 ግራ ዘመን
(ተስፋኣብ ተሾመ)

ላይ ላዩን ሲታይ የኛ ዘመን ጥሩ ይመስላል። በትክክል ግን ግራ አጋቢ  ዘመን ነው። የማይጨበጥ ዘመን!

ዛሬ ላይ አላስፈላጊ መተራመስ ውስጥ ነን፥ እርጋታ የለም፥ የጋራ እሴት የለም።  ግለሰባዊነት ማበቡ ያልበቁ ግለሰቦች እንዳሻቸው እንዲፈነጩ አድርጓል። ያልተማሩቱ መምህራን የሚሆኑበትን እድል አግኝተዋል። ራሱን ለመግዛት ያልታደለ የመንጋው አውራ ለመሆን በሚያደርገው ትግል የተነሳ መንጋው ታምሷል። እውነተኛ ተመሪ ልከኛ መሪ የለም። ልክ ያልሆነ ቦታ መቀያየር ተፈጥሯል

በመረጃ ጎርፍ ብንጥለቀለቅም እውቀት አልሆነንም። ጥራዝ ነጠቅ አደረገን እንጂ!
በየሴኮንዱ ከሚለቀቀው መረጃ መኻከል እውነት የሆነውን የመለያ ጥበብ አላዳበርንም። ትርምስ ብቻ።

ዘመናችን ግራ አጋቢ ነው። በግራ አጋቢ ዘመን በግራ መጋባት እየተራመስን ነው። ትርምስ ብቻ!

ዘመን መዋጀት ይኹንልን!


@Tfanos
@Zephilosophy
3.9K viewsedited  07:18
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-10 22:50:05 አዕምሮ የሚላሽቀው ለምንድነው?

በራሱ አስተሳሰብ መረብ የማይጠመድ፣ ስላለፈው ቅፅበት በየቅፅበቱ የሚሞት አእምሮ አይናጋም ፤ አይላሽቅም

ምንጭ ፦ ውስጣዊን ማንነት ማወቅ (ክሪሽና ሙርቲ)
ትርጉም ፦ ተስፋሁን ምትኩ

አንድ ዕለት ማለዳ አንድ አስክሬን ሊቃጠል በሸክም ሲሄድ አየሁ። በአንድ ደማቅ ጨርቅ ተጠቅልሏል፡፡ አራት በህይወት ያሉ ሰዎች ዜማ ባለው እንቅስቃሴ ተሸክመውት ይጓዛሉ:: አንድ አስከሬን በሌላ ሰው ላይ ምን አይነት ስሜት ይፈጥር ይሆን ስል አሰብኩ፡፡ ለምን መበላሸት ኖረ ብላችሁ አስባችሁ አታውቁም? አንድ አዲስ ሞተር ትገዙና በጥቂት ዓመታት ውስጥ ከጥቅም ውጭ ይሆናል፡፡ አካልም ይበላሻል፣ ግን አዕምሮስ ለምን ይበላሻል ብላችሁ ትንሽ ገፋ አድርጋችሁ አትጠይቁምን? ውሎ አድሮ አካል መሞቱ አይቀርም፤ የአብዛኞቻችን አዕምሮ ግን ቀድሞውንም ሞቷል፤ መበላሸቱ አስቀድሞ ተከስቷል። አዕምሮ የሚላሽቀው ለምንድነው? የአካል ክፍሎች የሚላሽቁት ያለማቋረጥ ስለምንጠቀምባቸው ነው። በሽታ፣ አደጋ፣ እርጅና፣ መጥፎ ምግብ፣ የተዛባ ውርስ - ልሽቀትንና የአካልን ግምት የሚያስከትሉት እነዚህ ናቸው፡፡ አዕምሮስ የሚላሽቀው፣ የሚያረጀው፣ የሚከብደው፣ የሚደነዝዘው ለምንድነው?

አንድ አስከሬን ስትመለከቱ ይህን ጥያቄ አንስታችሁ አታውቁም? አካሎቻችን የግድ መሞት ቢኖርባቸውም አዕምሯችንስ ለምንድነው የግድ መበላሽት የሚኖርበት? የአዕምሮ መላሸቅ የሚታየው በሸመገሉ ሰዎች ላይ ብቻ ሳይሆን በወጣቶች ላይም ጭምር ነው:: የወጣቶች አዕምሮ ሲደነዝዝ፣ ሲከብድ እናያለን። አዕምሮ ለምን እንደሚላሽቅ ካወቅን ምናልባትም አንድ የማይጠፋ ነገር እናገኝ ይሆናል። ይህን ስናውቅ ምናልባትም ዘላለማዊ ስለሆነው፣ መጨረሻ ስለሌለው፣ ጊዜ ስለማይገድበው፣ መዛባት ስለሌለበት፣ እንደ አካል በስብሶና ተቃጥሎ ወደ ወንዝ ስለማይጣለው ህይወት አንድ ነገር እንገነዘብ ይሆናል፡፡

አዕምሮ የሚላሽቀው ለምንድነው? አስባችሁበት ታውቃላችሁ? ልጆች ሳላችሁ በማህበረሰባችሁ፣ በቤተሰቦቻችሁ፣ በሁኔታዎች እንድትደድቡ ካልተደረጋችሁ አዲስ፣ ጉጉ፣ ንቁ አዕምሮ ይኖራችኋል፡፡ ከዋክብቱ ለምን እንደሚኖሩ፣ አዕዋፋቱ ለምን እንደሚሞቱ፣ ቅጠሎች ለምን እንደሚረግፉ አውሮፕላኖች እንዴት እንደሚበርሩ ማወቅ ትፈልጋላችሁ። ብዙ ነገሮችን ማወቅ ትሻላችሁ፡፡ ግና የማወቅ፣ የመመርመር ፍላጎታችሁ ተዳፍኖ ይቀራል፣ አይደለም? በፍርሃት፣ በባህል ጫና፣ ህይወት የሚባለውን ልዩ ነገር ለመጋፈጥ - የሚያስፈልገውን አቅም በማጣት ይሸፈናል፡፡ የማወቅ ጉጉታችሁ በአንድ ስል ቃል፣ በአንድ ኮስታራ አስተያየት፣ በፈተና ፍርሃት ወይም በወላጅ ማስፈራሪያ ወዲያውኑ ሲጠፋ አላስተዋላችሁምን? ስሜታዊነት ጠፍቶ አዕምሮ ሲደነዝዝ አልታዘባችሁም ወይ?

ሌላኛው የድንዛዜ መንስኤ ማስመሰል ነው:: ባህሉ አስመሳይ እንድትሆኑ አስተምሯችኋል፤ የትናንተ ሸክም ከመንገዱ ጋር እንድትጣበቁ አስገድዷችኋል፡፡ አዕምሮ የሚጣበቅበት ነገር ሲያገኝ ደግሞ የደህንነት ስሜት ይሰማዋል ፤ ያለ መታወክ፣ በጥርጣሬ ሳይያዝ በሰላም መሮጥ እንዲችል ራሱን ወደለሰለሰው መንገድ ያስጠጋል። እስኪ በዕድሜ የገፉ ሰዎችን ተመልከቷቸው ፤ አዕምሯቸው እንዲረበሽ አይፈልጉም ፤ የሞት ሰላምም ቢሆን ሰላምን ይፈልጋሉ። እውነተኛው ሰላም ግን ፍፁም የተለየ ነው::

አዕምሮ ከአንድ መንገድ ጋራ ራሱን ሲያመቻች ደህንነቱን ሽቶ እንደሆነ አላስተዋላችሁምን? ለዛም ነው አንድ ሃሳብ፣ አንድ ምሳሌ፣ አንድ መምህር የሚከተለው፡፡ ደህንነቱ እንዲጠበቅ ፣ እንዳይረበሽ ስለሚፈልግ ያስመስላል፡፡ በታሪክ መፃህፍቶቻችሁ ውስጥ ስለታላላቅ መሪዎች፣ ቅዱሳን፣ አርበኞች ስታነቡ እነሱን ለመምሰል ነሽጧችሁ አያውቅም? በዓለም ላይ ታላላቅ ሰዎች የሉም ለማለት አይደለም፤ ነገር ግን ደመነፍሳዊ ፍላጎታችን ሰዎቹን መምሰል፣ እንደ እነሱ ለመሆን መጣር ነው። እንዲህ ሲሆን አዕምሮ ራሱን ማጡ ውስጥ ያስገባና ይላሽቃል።

ከዚህም በላይ ማህበረሰቡ ንቁ፣ ጠያቂ፣ አብዮታዊ ግለሰቦችን አይፈልግም - ምክንያቱም እነኚሀን አይነት ሰዎች ከማህበረሰቡ ልማድ ከማፈንገጥ አልፈው እንዳይሆን አድርገው ያፈራርሱታል። ለዛም ነው ማህበረሰቡ አእምሯችሁ ከልማዱ ጋር እንዲጣጣም የሚፈልገው፤ ለዛም ነው ትምህርት ተብያችሁ እንድታስመስሉ፣ እንድትከተሉ፣ እንድትጣጣሙ የሚያበረታታችሁ፡፡

አእምሮ ማስመሰሉን መተው ይችላልን? ልማድ መፍጠሩን ማቆም ይችላል ወይ? በልማድ የታሰረው አዕምሮ ከልማዱ ነፃ ሊወጣ ይችላልን?

አእምሮ የልማድ ውጤት ነው፤ የባህል፣ የጊዜ ውጤት ነው የተደጋጋሚ፣ የትናንት ተቀጥላ ጊዜ። አእምሯችሁ በትናንት እና የትናንት ነፀብራቅ በሆነው በነገ ላይ ተመርኩዞ ማሰቡን ማቆም ይችላልን?አዕምሮ ከልማዶችና ልማዶችን ከመፍጠር ነፃ ሊሆን ይችላል ወይ? ይህን ችግር በጥልቀት ብትመለከቱት ይህን ማድረግ እንደሚችል ትገነዘባላችሁ። አዕምሮ አዳዲስ ቅርፆችን፣ ልማዶችን ሳይፈጥር በማስመሰል ወጥመድ ውስጥ ሳይወድቅ ራሱን የሚያድስ ከሆነ ትኩስ፣ ለጋ፣ የዋህ ሆኖ ከመቆየት አልፎ ግንዛቤው ወሰን አይኖረውም::

እንዲህ አይነቱ አዕምሮ የማከማቸት ሂደት አይኖረውምና አይሞትም። ልማድና ማስመሰል የሚፈጥረው የማከማቸት ሂደት ነው። የሚያከማች አዕምሮ ይላሽቃል፣ ይሞታል፡፡ የማያከማች፣ የማይሰበስብ፣ በየቀኑ፣ በየደቂቃው የሚሞት አዕምሮ ግን አይሞትም፤ የትየለሌ ቦታ አለውና፡፡

ስለዚህም አዕምሮ በሰበሰባቸው ነገሮች፣ በልማዶቹ፤ በማስመሰሉቹ፣ ለደህንነቱ ሲል በተጠጋቸው ነገሮች በሙሉ መሞት አለበት፡፡ እንዲህ ሲሆን በራሱ አስተሳሰብ መረብ አይጠመድም፡፡ አዕምሮ ስላለፈው ቅፅበት በየቅፅበቱ ሲሞት አዲስ ይሆናል፤ አይላሽቅም ወይም - በጨለማ ማዕበል አይናጋም፡፡

@Zephilosophy
@Zephilosophy
2.0K views19:50
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-08 22:11:08 የእውቀት የተሳሳተ እይታ

የሰው አይምሮ የሚገኝበት ሁነት ልክ እንደተረበሸ የንብ ቀፎ ነው፡፡ ቀፎዎቻቸው እንደተነካባቸው ንቦች በሚራውጡ እሳቤዎች የተሞላ ነው፡፡ ሰው በነዚህ እሳቤዎች ተከቦ በስጋትና በውጥረት እየኖረ ነው፡፡ ህይወትን ለማወቅ አይምሮ ልክ ሞገድ እንደሌለው ሃይቅ ፀጥተኛ መሆን አለበት፡፡ ከህይወት ጋር ለመተዋወቅ አይምሮ አቧራ እንደሌለው መስታወት የጠራ መሆን አለበት፡፡

አይምሯችን እንደ ንፁህ መስታወት ወይም ፀጥተኛ ሃይቅ ሳይሆን እንደ ተረበሸ የንብ ቀፎ ነው፡፡ በዚህ አይምችን አንድን የሆነ ነገር ማወቅ፣ ማግኘት ወይም የሆን ነገር መሆን እንደምንችል ካሰብን ትልቅ ስህተት እየሰራን ነው:: .

ከዚህ ከፍተኛ የእሳቤዎች ፍሰት ነፃ መሆን በጣም አስፈላጊ ነው። በተወዛገቡ አሳቤዎች መሞላት የጤና ሳይሆን የበሽታ ምልክት ነው፡፡ አይምሮ ሙሉ በሙሉ ንፁህና ጤነኛ ሲሆን እሳቤዎች ይጠፋሉ፡፡ እሳቤዎች ይጠፉና ንቃተ ህሊና ብቻ ይቀራል። እየኖርን ያለነው በእሳቤዎች አጨቅ ውስጥ ነው፡፡ ከጠዋት እስከ ማታ፣ ከማታም እስከ ጠዋት፣ ከልደት እስከ ሞት ኑሯችን በእሳቤዎች አጨቅ ውስጥ ነው፡፡

ከዚህ የእሳቤዎች አጨቅ ነፃ የምንሆነው እንዴት ነው? ከእሳቤዎች ነፃ መሆን ሁለተኛው እርምጃ ነው፡፡ የመጀመሪያው እርምጀ የእሳቤዎች ስብስብ አለመፍጠር ነው። በአንድ በኩል ከእሳቤዎች ነፃ ለመሆን እየሞከራችሁ በሌላ በኩል ደግሞ እሳቤዎችን የምትሰበስቡ ከሆነ ከእሳቤዎች ነፃ ለመሆን ትቸገራላችሁ፡፡ ከዛፍ ቅጠሎች ነፃ ለመሆን እየሞከርን የዛፉን ስሮች ውሃ ማጠጣታችንን ከቀጠልን እንዴት ከቅጠሎቹ መላቀቅ እንችላለን? ስሮቹን ውሃ ስናጠጣ በስሮቹና በቅጠሎቹ መሃል ጥልቅ ዝምድና እንደሚኖር የተገንዘብን አይመስልም፡፡ ስሮቹና ቅጠሎቹ የተለያዩ ይመስላሉ፡፡ ቅጠሎቹ ግን ከስሮቹ የተለዩ
አይደሉም፡፡ እናም ለስሮቹ የምንሰጠው ውሃ በቀጥታ ወደ ቅጠሎቹ ይወጣል፡፡

ብዙ እሳቤዎችን እየሰበሰብን ስሮቻቸውን ውሃ እናጠጣለን፡፡ በእነዚሁ እሳቤዎች አይምሯችን ረፍት አጥቶ ሲረበሽ ደግሞ እሳቤዎቹን ፀጥ የሚያሰኝ መንገድ ለማግኘት እንጥራለን። ዛፉ ቅጠሎች ማብቀሉን እንዲያቆም ለስሮቹ ውሃ መስጠታችንን ማቆም አለብን፡፡ የእሳቤዎቻችንን ስሮች እንዴት ውሃ ማጠጣት እንዳለብን ልንገነዘብ ይገባል። ይህን ከተረዳን እሳቤዎቹን ማቆም እንችላለን፡፡ ከዛም ቅጠሎቹ የሚረግፉበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም፡፡

እሳቤዎቻችንን ውሃ የምናጠጣው እንዴት ነው?

በሺዎች ለሚቆጠሩ አመታት እውቀት የሚገኘው የሌሎች ሰዎችን እሳቤዎች በማጠራቀም እንደሆነ ስናስብ ኖረናል፡፡ ይህ ግን ሙሉ በሙሉ ውሸትና ስህተት ነው። የሌሎች ሰዎችን እሳቤዎች በማጠራቀም እውቀትን ያገኘ አንድም ሰው የለም፡፡ እውቀት የሚመነጨው ከውስጥ ነው፡፡ እሳቤዎች የሚመጡት ደግሞ ከውጭ ነው፡፡ እውቀት የራሳችን ሲሆን፣ እሳቤዎች ደግሞ ከሌሎች የምንዋሳቸው ናቸው፡፡ እውቀት ውስጣችሁ ተደብቆ የሚገኘው እውነት የሚገለጥበት የህልውናችሁ ምት ነው፡፡ እሳቤዎች ሌሎች የተናገሯቸው ነገሮች ስብስብ ናቸው፡፡

ከሌሎች የምናገኘው ሁሉ እውቀታችን አይሆንም፡፡ አለማወቃችንን የመደበቂያ መንገድ ይሆናል፡፡ የአንድ ሰው አለማወቅ ከተደበቀ ደግሞ ሰውየው እውቀት ሊያገኝ አይችልም፡፡ ከሌሎች የቃረምናቸው እሳቤዎች እውቀታችን እንደሆኑ ስለምናስብ በመላው እኛነታችን ሙጭጭ እንልባቸዋለን፡፡ እሳቤዎቻችን ላይ ጥብቅ ከማለት ውጪ ልናስወግዳቸው የሚያስችለን ድፍረት የለንም፡፡ እውቀታችን እንደሆኑና ካጣናቸው አላዋቂ እንደምንሆን ስለምናስብም እንንከባከባቸዋለን፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው የቱንም ያህል እሳቤዎቹን የሙጥኝ ቢል በእሳቤዎቹ አማካኝነት አዋቂ አይሆንም፡፡

አንድ የውሃ ጉድጓድ የሚቆፍር ሰው በቅድሚያ አፈርና ድንጋዮችን ያወጣል፤ ከዛም ከጉድጓዱ ጐኖች ውሃ ይመነጭና ጉድጓዱን ይሞላዋል፡፡ ውሃው ቀድሞውኑ እዛው አለ፡፡ ከሌላ ቦታ የመጣ አይደለም፡፡ ጥቂት ድንጋዮች እና ጥቂት የአፈር ሽፋኖች ብቻ መወገድ አለባቸው፡፡ ያገዱት እንቅፋቶች በተወገዱ ጊዜ ውሃው ይመነጫል፡፡ ውሃውን ከሌላ ቦታ ማምጣት አስፈላጊ አይደለም፤ ቀድሞውኑ እዛው አለ፡፡ እንዳይመነጭ ያገዱት እንቅፋቶች ብቻ መውገድ አለባቸው፡፡

እውቀት ያለው በውስጣችን ነው፤ ከሌላ ቦታ መምጣት የለበትም፡፡ ምንጮቹ በውስጣችን ተደብቀው አሉ፡፡ በመሃል ያሉት እንቅፋቶች በቁፋሮ መወገድ ብቻ አለባቸው። ከዛም የእውቀት ምንጭ መፍለቅ ይጀምራል::

የውሃ ጉድጓድ መስራት ይቻላል፤ እንደዚሁም የውሃ ኩሬ መስራት ይቻላል፡፡ የውሀ ኩሬ መስራት ግን የተለየ ነው፡፡ የውሃ ኩሬ ለመስራት የውሃ ምንጮችን መፈለግ አይጠበቅባችሁም፡፡ የውሃ ኩሬ በአሰራሩ ከውሃ ጉድጓድ ሙሉ በሙሉ የተቃረነ ነው፡፡ የውሃ ኩሬ ለመስራት ድንጋዮችና አፈር ቆፍራችሁ ማውጣት አያስፈልጋችሁም፡፡ አፈርና ድንጋዮቹን ከሌላ ቦታ አምጥታችሁ ግድግዳ መገንባት አለባችሁ፡፡ ግድግዳው ተገንብቶ ሲጠናቀቅ ከሌሎች ሰዎች የውሃ ጉድጓዶች ውሃ በማምጣት ኩሬውን ትሞላላችሁ፡፡ ከላይ ሲታይ የውሃ ኩሬው የውሃ ጉድጓድ ይመስላል፡፡ ይሁን እንጂ በውሃ ኩሬና በውሃ ጉድጓድ መሃል ያለው ልዩነት የምድርና የሰማይ ያህል ነው፡፡

የመጀመሪያው ልዩነት የውሃ ኩሬ የራሱ የሆነ ውሃ የለውም፡፡ ኩሬ ውስጥ ያለ ውሃ ሁሉ ከሌላ ቦታ የመጣ ሲሆን ብዙም ሳይቆይ መሰንፈጥ ይጀምራል። ምክንያቱም በውሰት የመጣው ህያው ሳይሆን ሙት ነው፡፡ የኩሬ ውሃ ምንም የማይንቀሳቀስ ሲሆን ወዲያው በስብሶም መከርፋት ይጀምራል፡፡

የውሃ ጉድጓድ ግን የራሱ ምንጭ አለው፡፡ ውሃውም ረግቶ የቆመ አይደለም፡፡ የራሱ የሆነ ፍሰት አለው፡፡

የውሃ ኩሬ ውሃው በሆነ ሰው እንዳይወሰድበት ይፈራል፤ ምክንያቱም ውሃው ከተወሰደ ባዶውን ይቀራል። የውሃ ጉድጓድ ደግሞ የሆነ ሰው ውሃውን እንዲወስድለት ይፈልጋል፤ ምክንያቱም በሌላ ትኩስና ንፁህ ውሃ ይሞላል፡፡ የውሃ ጉድጓድ ከውቅያኖስ ጋር የተያያዙ ጅረቶች አሉት፡፡ ሲታይ ትንሽ ቢመስልም ውስጥ ለውስጥ ግን ከየትየለለው የተያያዘ ነው፡፡ የውሃ ኩሬ የቱንም ያህል ትልቅ መስሎ ቢታይ ከምንም ጋር ግንኙነት የለውም፡፡ ጅረቶች የሉትም:: ከየትየለሌው የሚገናኝበት መንገድ የለውም፡፡ የውሃ ኩሬ ስለ ውቅያኖስ የሚያውቀው ነገር የለም፡፡

የሰው አይምሮ እንደ የውሃ ጉድጓድ ወይም የውሃ ኩሬ ሊሆን ይችላል፡፡ ሊሆን የሚችለው ከሁለቱ አንዱን ብቻ ነው፡፡ አይምሮው የውሃ ኩሬ የሆነበት ሰው ደግሞ ቀስ በቀስ ማበዱ አይቀርም፡፡ 

የሁላችንም አይምሮዎች የውሃ ኩሬ ሆነዋል፡፡ የፈጠርነው የውሃ ጉድጓድ ሳይሆን የውሃ ኩሬ ነው፡፡ ከመላው ዓለም ነገሮችን እንሰበስባለን፡፡ በዚህም የተማርን እንደሆንን እናስባለን፡፡ ስህተታችን ልክ እንደ የውሀ ኩሬው ነው፡፡ የውሃ ኩሬው የውሃ ጉድጓድ እንደሆነ ያስባል፡፡ በርግጥ በሁለቱም ውስጥ ውሃ ስለሚታይ ያሳስታል፡፡


ምንጭ ፦ የነፍስ መንገድ (ኦሾ)
ትርጉም ፦ መርሻ በነበሩ
@Zephilosophy
@Zephilosophy
2.8K viewsedited  19:11
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-04 14:43:58 ከእኔነት ነፃ መሆን

ምንጭ ፦ የነፍስ መንገድ (ኦሾ)
ትርጉም ፦ መርሻ በነበሩ

በሰው ህይወት ውስጥ ታላቁ ሙዚቃ ሊፈልቅ የሚችለው ልብ በአግባቡ የተቃኙ ክሮች ሲኖሩት ነው፡፡ ልቡን ያጣ ማህበረሰብ ጥሩ፣ እውተኛና ውብ የሆኑትን ክሮች ሁሉ አጥቷል፡፡ እውነት፣ ውበትና አምላካዊ ባህሪያት ወደ ህይወታችን እንዲገቡ ከፈለግን የልብን ሙዚቃ አፍላቂ የሆኑትን ክሮች በአግባቡ ከመቃኘት ውጪ ሌላ መንገድ የለም፡፡

እነዚህን የልብ ሙዚቃ አፍላቂ ክሮች በአግባቡ ለመቃኘት የሚያስችለው መንገድ ፍቅር ነው፡፡ ፍቅርን “ፀሎት ወይም እግዜርን የማግኛው መንገድ” ብዬ የምጠራውም ለዚህ ነው፡፡ ከፍቅር ያልሆነ ፀሎት ውሸትና የማይጠቅም ነው፡፡ ፍቅር አልባ የፀሎት ቃላት ዋጋ የላቸውም፡፡ ወደ አምላክ ለመጓዝ የፈለገ ሰው ያለ ፍቅር ሊሳካለት አይችልም፡፡ ልባዊ ሙዚቃን የሚያፈልቀው ፍቅር ነው፡፡ ስለፍቅር የተወሰኑ ነገሮችን ልንገነዘብ ይገባል፡፡

የመጀመሪያው “እናውቀዋለን” የሚል ስለ ፍቅር ያለን የተሳሳተ እይታ ነው፡፡ ይህ የተሳሳተ እይታ በእጅጉ የሚጐዳ ነው፤ ምክንያቱም ቀድሞውኑ እናውቀዋለን ብለን የምናስበውን ነገር ለማግኘት ወይም ለመቀስቀስ በጭራሽ ጥረት አናደርግም።

ፍቅርን ያወቀ መለኮትን የማወቅ አቅም እንዳለው አናውቅም፡፡ ፍቅርን ካወቅን በህይወታችን ሳናውቀው የሚቀር ምንም ነገር አይኖርም፡፡ አሁን ባለንበት ሁኔታ ግን ምንም አናውቅም፡፡ ሁሉም ነገር ገና የሚታወቅ ነው፡፡

ፍቅር እንደሆነ የምናስበው ፍቅር ላይሆን ይችላል። ፍቅር ብለን የጠራነው ፍቅር ሳይሆን ሌላ ነገር ነው፡፡ ስለፍቅር ጠንቅቀን እናውቃለን የሚል የተሳሳተ እይታ እስካለን ድረስ ፍቅርን ፈልገን ልናገኘው አንችልም፡፡ በቅድሚያ ልገነዘበው የሚገባን ፍቅርን በጭራሽ እንደማናውቀው ነው::

ከእኩለ ቀን በኋላ ሙቀቱ አይሎ በነበረበት አንድ ቀን እየሱስ ከርስቶስ በአንድ የአትክልት ስፍራ ውስጥ ከነበረ ዛፍ ስር ጥላ ለማግኘት ቆመ፡፡ ከሙቀቱ ሃያልነት የተነሳ ደክሞት ነበር። እናም ዛፉ ጥላ ስር ተኛ፡፡ ቤቱ፣ የአትክልት ስፍራውና ዛፉ የማን እንደሆነ እንኳን አላወቀም ነበር:: የአትክልት ስፍራው በጊዜው እጅግ በጣም ቆንጆ የሆንችው የመቅደላዊት ነበር፡፡

መቅደላዊት በመስኮቷ አሻግራ ስትመለከት አንድ በጣም የተለየ ሰው ዛፍ ስር  ተኝቶ አየች፡፡ እንዲህ አይነት በጣም ቆንጆ ሰው አይታ አታውቅም፡፡ አካላዊ ውበት እንዳለ ሁሉ የነፍስ ውበትም አለ፡፡አካላዊ ውበት ብዙውን ጊዜ ሊታይ ይችላል፤ የነፍስ ውበት ግን እጅግም አይታይም፡፡ የነፍስ ውበት ሲገለጥ በጣም አስቀያሚ አካል እንኳ እጅግ በጣም የሚያምር አበባ ይሆናል፡፡ ብዙ ሰዎች ወደ ቤቷ ጐራ ስለሚሉ ብዙ ቆንጆ ወንዶችን አይታለች፡፡ ወደ ቤቷ ለመግባት አስቸጋሪ ነበር፡፡ ልክ በአስማት የሆነ ይመስል መቅደላዊት ወደ ዛፉ ተሳበች፡፡

እየሱስ ተነስቶ ሊሄድ አካባቢ ነበር፡፡ እረፍቱን አጠናቋል። መቅደላዊት ግን ወደ እሱ ቀረበችና፡- “እባክህ ወደ ቤቴ ገብተህ እረፍ፡፡ ስትል ጋበዘችው፡፡

ክርስቶስም፡- “አሁን እረፍቴን ጨርሻለሁ፡፡ የመሄጃ ጊዜዬ ነው፡፡ ነገር ግን ዳግመኛ በዚህ መንገድ የማልፍና የደከመኝ ከሆነ በእርግጠኝነት አንቺ ቤት ውስጥ አርፋለሁ፡፡” ሲል መለሰላት፡፡

በዚህም መቅደላዊት የተሰደበች ያህል ተሰማት፡፡ ታላላቅ ልዑሎች ቤቷ የመግባት እድል ሳያገኙ ከበሯ ተመልሰዋል፡፡ ይህን ተራ የመንገድ ሰው ወደ ቤቷ ገብቶ እንዲያርፍ ስትጋብዘው ፈቃደኛ አልሆነም፡፡ ይህ ለመቅደላዊት ስድብ ነበር፡፡ እናም፡- “ይህን ማድመጥ አልችልም፡፡ ወደ ቤቴ መምጣት አለብህ፤ ይህን ያህል እንኳ ለፍቅሬ ስትል ማድረግ አትችልም? ለጥቂት ቅፅበታት እንኳ ቤቴ ውስጥ እረፍት አታደርግም?” ስትል ስሜታዊ ሆና ጠየቀችው፡፡

ክርስቶስ ግን፡- “ስለ ጋበዝሸኝ ብቻ ወደ ቤትሽ ገብቻለሁ፤ ምክንያቱም ከልባዊ ስሜቶችሽ ውጪ ምን ቤት አለሽ? ይህን ያህል ፍቅር እንኳ አታሰየኝም ወይ? ብለሽ ጠይቀሽኛል። እንደሚወዱሽ የገለፅልሽ ብዙ ሰዎች አጋጥመውሽ ይሆናል፡፡ አንዳቸውም ግን አይወዱሽም ነበር፡፡ በውስጣቸው የሚወዱት አንቺን ሳይሆን ሌላ ነገር ነበር፡፡ ማፍቀር የሚችለው በልቡ ውስጥ ፍቅር የሞላ ሰው ብቻ ነው፡፡ እኔ ደግሞ አንቺን በእውነት ሊወዱሽ ከሚችሉ እና ከሚወዱሽ ጥቂት ሰዎች አንዱ መሆኔን ላረጋግጥልሽ እችላለሁ፡” ሲል መለሰላት፡፡

በውስጣችን የፍቅር ፍሰት ስለሌለ ማናችንም ማፍቀር አንችልም፡፡ አንድን ሰው እንደምናፈቅረው ስንናገር በእርግጥ ፍቀር እየሰጠነው ሳይሆን ፍቅርን እንዲሰጠን እየጠየቅነው ነው፡፡ ሁላችንም ፍቅር እንዲሰጠን እንጠይቃለን፡፡ ታዲያ ፍቅር እንዲሰጠው የሚጠይቅ ሰው እንዴት ፍቅርን ሊሰጥ ይችላል? ለማኞች እንዴት ንጉሶች ሊሆኑ ይችላሉ?

አንዳችን ካንዳችን ፍቅርን እንጠይቃለን፡፡ ፍቅርን ከሌላው የምንጠይቅ ለማኞች ነን፡፡ ሚስት ከባሏ ፍቅርን ትጠይቃለች፤ ባል ከሚስቱ ፍቅርን ይለምናል፡፡ እናት ከልጇ፣ ልጅም ከእናቱ ፍቅርን ይጠይቃሉ፡፡ ጓደኛ ከጓደኞቹ ፍቅርን ይፈልጋል፡፡ ፍቅር እንዲሰጠን የምንለምነው ጓደኛችን ራሱ ፍቅርን ከእኛ እየለመነ መሆኑን ባለመገንዘብ ሁላችንም አንዳችን ከአንዳችን ፍቅርን እንጠይቃለን፡፡ መለመኛ ከረጢታቸውን ይዘው ፊት ለፊት ተፋጠው እንደቆሙ ለማኞች ነን፡፡

አንድ ሰው ፍቅርን ሌላው እንዲሰጠው እስከጠየቀ ድረስ እሱ ራሱ ፍቅርን መስጠት አይችልም፡፡ ምክንያቱም የእሱ ከሌላው ፍቅርን መጠየቅ የሚያመለክተው በውስጡ ምንም የፍቅር ምንጭ አለመኖሩን ነው፡፡ ያ ካልሆነ ለምን ፍቅርን ከውጪ ይጠይቃል? ፍቅርን ከሌላው የመጠየቅ ፍላጐት በላይ የሆነ ሰው ብቻ ፍቅርን መስጠት ይችላል፡፡ ፍቅር ማካፈል እንጂ ልመና አይደለም፡፡ ፍቅር ንጉስ እንጂ ለማኝ አይደለም፡፡ ፍቅር የሚያውቀው መስጠትን ብቻ ነው፡፡ ስለ ልመና የሚያውቀው ነገር የለም፡፡

በእርግጥ ፍቅር እናውቃለን?

ሌላው እንዲሰጠን የምንጠይቀው ፍቅር ፍቅር ሊሆን አይችልም፡፡ በዚህ ዓለም ፍቅርን ከሌላው የሚጠይቅ በጭራሽ አያገኝም፡፡ እጅግ በጣም ወሳኝ ከሆኑ ዘላለማዊ የህይወት ህጎች አንዱ ፍቅርን ከሌላው የሚጠይቅ መቼም ፍቅር እንደማያገኝ መሆኑን አስታውሱ።

ፍቅር የሚመጣው በልመና አይደለም፡፡ ፍቅር መዝነብ የሚጀምረው ፍቅር መጠየቅ ባቆመ ሰው ቤት ላይ ነው፡፡ ፍቅርን ፍለጋ ለሚዞር ሰው ቤት ላይ ግን ጠብ የሚል የፍቅር ዝናብ የለም፡፡ በጠያቂ ልብ ውስጥ የፍቅር ፍሰት የለም፡፡ ጠያቂ ልብ ፍቅር ወደ ውስጡ ሊዘልቅ የሚያስችል ክፍተት የለውም፡፡ ፍቅር ወደ ውስጡ ሊዘልቅ የሚችለው አካፋይ ወይም ሰጪ ልብ ውስጥ ነው::

ፍቅር በራችንን አንኳኩቶ ያውቃል? በጭራሽ! ምክንያቱም ገና ፍቅር መስጠት አልቻልንም:: ማስታወስ ያለባችሁ የሰጠነው ሁሉ ወደ እኛው ተመልሶ እንደሚመጣ ነው። ይህም ከዘላለማዊ የህይወት ህጐች አንዱ ነው::

መላው አለም ከገደል ማሚቱ የተሻለ አይደለም፡፡ ጥላቻ እንሰጣለን፤ ጥላቻም ወደኛው ተመልሶ ይመጣል፡፡ ቁጣ ስንሰጥም ቁጣው ተመልሶ ወደኛው ይመጣል። ሌሎችን እንሰድባለን ከዛም ስድብ ወደኛው ተመልሶ ይመጣል። እሾህ ስንሰጥ እሾህ ወደ እኛው ተመልሶ ይመጣል። የምንሰጠው ሁሉ በተለያዩ መንገዶች ወደ እኛው ተመልሶ ይመጣል፡፡ ፍቅርን ካካፈልንም እንደዚሁ በተለያዩ መንገዶች ወደ እኛው ተመልሶ ይመጣል፡፡ ስፍር ቁጥር በሌላቸው መንገዶች ፍቅር ወደ እኛ ተመልሶ ካልመጣ ፍቅር እንዳልሰጠን ማወቅ አለብን፡፡

@Zephilosophy
@Zephilosophy
674 views11:43
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-29 22:41:27 የብቸኝነትና የባዶነትን ስሜት መጋፈጥ


በውስጣቸው ከራሳቸው ጋር ብቻቸውን የሆኑ፣ አዕምሮና ልባቸው ከብቸኝነት ስቃይ የፀዳ ሰዎች እውነተኞች ናቸው

ምንጭ ፦ ወስጣዊ ማንነትን ማወቅ ( ክሪሽና ሙርቲ)
ትርጉም ፦ ተስፋሁን ምትኩ

አዝናኝና አስከፊ ነገር በሞላበት ዓለም ሁሉም ሰው ተሳታፊ ከመሆን ይልቅ ተመልካች መሆኑ አያስገርምምን? አብዛኞቻችን ትንሽ ነፃ ጊዜ ስናገኝ አንድ የሚያስደስተን ነገር እንፈልጋለን፡፡ አሜሪካ ውስጥ ከሆንን ቴሌቪዥን ወይም ሞባይል እንከፍታለን ወይም ወሬ እንጀምራለን፤ አለዚያም መፅሀፍ ወይ መፅሄት እናነሳለን፡፡ የመደነቅ የመዝናናት፣ ራሳችንን የመርሳት የማያቋርጥ ፍላጐት አለን፣ ብቸኝነትን፣ ጓደኛ ማጣትን፣ ሳይረበሹ መቆየትን እንፈራለን፡፡ ሳናወራ ወይም ሳንዘፍን በፀጥታ በመስክ ወይም በጫካ ውስጥ እየተራመድን ስለ ራሳችንና በውስጣችን ስላለው ነገር የምናስተውል ጥቂቶቻችን ነን፡፡ አብዛኞቻችን እንዲህ ማድረግ የሚሳነን ስልቹዎች ስለሆንን ነው፤ በመማር ወይም በማስተማር፣ በቤት ጣጣ ወይም በስራ ተጠምደናል፡፡ ስለዚህም ነፃ ጊዜ ስናገኝ በቀላሉ ወይም በከባዱ መደነቅን እንፈልጋለን፡፡ እናነባለን ወይ ወደፊልም ቤት እንሄዳለን - ወይ ወደአንዱ ሃይማኖት እንዞራለን። ሃይማኖትም አንደኛው ዓይነት ከስልቹነት የማምለጫ መንገድ ሆኗል፡፡

ይህን ሁሉ ተገንዝባችሁ እንደሆነ አላውቅም:: አብዛኞቹ ሰዎች በአንድ ነገር ተጠምደዋል - የተወሰኑ ቃላትን በመደጋገም፣ በዚህ ወይም በዚያ ጉዳይ በመስጋት - ምክንያቱም ከራሳቸው ጋር ብቻቸው መሆንን ስለፈሩ። የሚረብሻችሁ ነገር ሳይኖር ብቻችሁን ለመሆን ብትሞክሩ ምን ያህል ከራሳችሁ መውጣት እንደምትፈልጉና ማንነታችሁን ለመርሳት እንደምትሹ ትገነዘባላችሁ። ለዛም ነው ይህ ግዙፍ የደስታ መዋቅር፣ ፈጣን ረብሻ ስልጣኔ የምንለው ነገር አካል የሆነው:: አስተዋዮች ከሆናችሁ የዓለም ህዝቦች ይበልጥ እየተረበሹ እንደመጡ፣ ውስብስብና ዓለማዊ እየሆኑ እንደሄዱ ትመለከታላችሁ። የደስታው መብዛት፣ የሚታተሙት መፃህፍት መከመር፣ የጋዜጦች በስፖርታዊ ጉዳዮች መሙላት - እነዚህ ሁሉ ያለማቋረጥ መደሰትን እንደምንፈልግ ያመለክታሉ፡፡ ውስጣዊ ባዶነት ስላለብን ግንኙነቶቻችንና ማህበራዊ ለውጦቻችን ከገዛ ራሳችን ለማምለጥ እንደ መሳሪያ እንጠቀምባቸዋለን፡፡ ብቸኝነት የወረራቸው ብዙ ሰዎች እንዳሉ አስተውላችኋልን? ከብቸኝነታቸን ለማምለጥ ተሽቀርቅረን ፣ ግብዣ ወዳለበት እንሔዳለን፣ ቴሌቪዥን እናያለን፣ ሞባይል እንነካካለን፤ እናወራለን ወዘተ፡፡

ብቸኝነት ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? አንዳንዶቻችሁ ቃሉን ባታውቁም ስሜቱን በደንብ ታውቁት ይሆናል። ብቻችሁን ሽርሽር ስትወጡ ወይም ከመፅሃፍ ስትላቀቁ ወይ ከሰው ጋር መነጋገር ስታቆሙ ይህ ሁሉ ነገር እንዴት አሰልችቷችሁ እንደነበር ትገነዘባላችሁ፡፡ ይህን ስሜት በደንብ ታውቁታላችሁ፣ ነገር ግን ለምን እንደሰለቻችሁ አታውቁም፤ ምን ብላችሁ ጠይቃችሁም አታውቁም:: ያን ስልቹነት በጥቂቱ ብትመረምሩት መንስኤው ብቸኝነት እንደሆነ ትገነዘባላችሁ፡፡ አብረን መሆን የምንፈልገው፣ መዝናናት የምንፈልገው፣ የሚረብሹንን መምህራን ወይም ምርጥ ልብ ወለዶች የምንሻው ከብቸኝነታችን ለማምለጥ በማሰብ ነው፡፡ ውስጣዊ ብቸኝነት ሲሰማን የህይወት ተመልካች እንሆናለን ፤ ይህን ብቸኝነታችንን ተገንዝበን አልፈነው ስንሄድ ብቻ ተሳታፊዎች መሆን እንችላለን፡፡

ብዙ ሰዎች እንዴት በብቸኝነት መኖር እንደሚችሉ ስለማያውቁ ትዳር ይይዙና ሌላ አይነት ማህበራዊ ግንኙነት ይመሰርታሉ፡፡ ይህ ሲባል ግን አንድ ሰው ብቻውን መኖር አለበት አይደለም። መወደድ ስለፈለጋችሁ ብቻ የምታገቡ ከሆነ ወይም ሰልችቷችሁ ስራችሁን ራሳችሁን እንደ መርሻ ከተጠቀማችሁበት መላ ህይወታችሁ ረብሻን ፈላጊ እንደሆነ ትገነዘባላችሁ፡፡ ከዚህ ልዩ የብቸኝነት ፍርሃት በላይ የሚሆኑ ጥቂቶች ብቻ ናቸው፡፡ ነገር ግን ከዚህ ፍርሃት በላይ ሲኮን እውነተኛው ሀብት ይገኛልና ሁሉም ሰው ፍርሃቱን መብለጥ አለበት፡፡

በብቸኝነትና ብቻን በመሆን መካከል ከፍተኛ ልዩነት አለ፡፡ አንዳንድ ወጣት ተማሪዎች ብቸኝነት ምን እንደሆነ አያውቁ ይሆናል፤ በዕድሜ የገፉት ግን ይህን ጠንቅቀው ያውቃሉ። ብቸንነት ጨርሶ  የመቆረጥ፣ ያለምንም ምክንያት በድንገት የመፍራት ስሜት ነው። አእምሮ የሚጠጋው ነገር ሲያጣ፤ የባዶነቱን ስሜት የሚያስወግድለት ነገር ሲያጣ ይህ ፍርሃት ይሰማዋል። ይህ ብቸኝነት ነው፡፡ ብቻን መሆን - ግን ፍፁም የተለየ ነገር ነው፤ በብቸኝነት ውስጥ አልፋችሁ ስትገነዘቡት የሚመጣ የነፃነት ሁኔታ ነው። በዚያ የብቻ መሆን ሁኔታ ውስጥ ስትሆኑ በስነ - ልቡና ረገድ የማንም ጥገኛ አትሆኑም፡፡ ምክንያቱም ደስታን፣ ምቾትን መፈለጋችሁ ያቆማል፡፡ ይህን ጊዜ ብቻ አዕምሮ ሙሉ በሙሉ ብቻውን ይሆናል፤ ፈጣሪ ይሆናል፡፡

የብቸኝነትን፣ የባዶነትን ልዩ ስሜት የመጋፈጡን፣ ያለ መፍራቱን፣ ስሜቱ ሲመጣ ሞባይል ያለመጠቀሙን፤ በስራ ያለመጠመዱን ወይ ወደሲኒማ ቤት ያለመሮጡን፤ ከዚህ ይልቅ ስሜቱን የመመልከቱን፣ የመገንዘቡን ነገር መፍጠር ያለበት ትምህርት ነው:: ስጋትን የማያውቅ ወይም ያላወቀ ሰው የለም፡፡ ይህንን ስሜት በወሲብ፣ በእግዚአብሔር፣ በስራ፣ በመጠጥ፣ ግጥሞች በመፃፍ ወይም በልባችን የተማርናቸውን ጥቂት ቃላት በመደጋገም ወዘተ ለማምለጥ ስለምንሞክር ፈፅሞ አንገነዘበውም።

ስለዚህም የብቸኝነት ህመም ሲመጣባችሁ ትታችሁት ከመሮጥ ይልቅ ተጋፈጡት፡፡ ትታችሁት ከሮጣችሁ ፈፅሞ አትገነዘቡትም፤ ሁልጊዜ በየጥጋጥጉ ቆሞ ይጠብቃችኋል። ስሜቱን ተገንዝባችሁ አልፋችሁት ብትሄዱ ግን ማምለጡ፣ መዝናናቱ አስፈላጊ እንዳልሆነ - ትረዳላችሁ፤ አዕምሯችሁ የማይበላሽ፣ የማይነጥፍ ብልፅግናን ይጎናፀፋል፡፡ 

ይህ ሁሉ የትምህርት አካል ነው፡፡ በትምህርት ቤት ፈተና ለማለፍ ብቻ የተወሰኑ ትምህርቶችን የምትማሩ ከሆነ ትምህርት ራሱ ፣ ከብቸኝነት የማምለጫ መንገድ ይሆናል፡፡ ትንሽ ብታስቡበት ይገባችኋል። ከአስተማሪዎቻችሁ ጋር ብታወሩ እንዴት ብቸኞች እንደሆኑ፣ እንዴት ብቸኞች እንደሆናችሁ ትረዳላችሁ፡፡

በውስጣቸው ከራሳቸው ጋር ብቻቸውን የሆኑ፣ አዕምሮና ልባቸው ከብቸኝነት ስቃይ የፀዳ ሰዎች እውነተኞች ናቸው- ምክንያቱም እውነታውን ከራሳቸው ይረዳሉ፣ ጊዜ የማይወስነውን መቀበል ይችላሉ፡፡

@Zephilosophy
@Zephilosophy
1.9K viewsedited  19:41
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-22 22:48:52 ጊዜህን በርካሽ ዋጋ አትሽጥ!!

"ሴኔካ አካላዊ ንብረቶቻችንን መጠበቅ ላይ ጥሩ የሆንነውን ያህል፣ አእምሯዊ ድንበሮቻችን ማስመር ላይ ግን ግድ የለሽ መሆናችንን . ያስታውሰናል። ማንም እንዳሻው ድንበራችንን አልፎ ሲገባ አንቃወመውም: ንብረት ተመልሶ ሊገኝ ይችላል፤ እንዲያውም ገና ብዙ የምድር ሃብቶች በሰው አልተነኩም። ጊዜ ግን? ጊዜ ፈጽሞ ሊተካ የማይችል ሀብታችን ነው፤ ተጨማሪ መግዛት አንችልም፡፡ ማድረግ የምንችለው በተቻለ መጠን ለመቆጣጠር ጥረት ማድረግ ብቻ ነው፡፡"

"በሕይወታችን ውስጥ ሌሎች ጣልቃ እንዲገቡ በቀላሉ እንፈቅዳለን፤ የከፋው ነገር ደግሞ በአብዛኛው ጊዜያችንን ሊያጠፉት ለሚችሉት ሰዎች መንገድ የምናመቻች መሆናችን ነው። ማንም ሰው ለአላፊ አግዳሚው ገንዘቡን አይሰጥም፤ ግን እያንዳንዳችን ለምን ያህል ሰዎች ሕይወታችንን ሰጥተናል!ለንብረትና ለገንዘብ እጃችን አይፈታም፣ ሁላችንም እጅግ ስስታሞች መሆን ለሚገባን ለሚባክን ጊዜ ግን የምናስበው እጅግ ትንሽ ነው።”
- ሴኔካ

"የሕይወታችንን ቀናት ልክ እንደ ገንዘባችን አንመለከተም? በትክክል ለምን ያህል ቀናት በሕይወት እንደምንቆይ ስለማናውቅ፣ አንድ ቀን የምንሞት የመሆኑን ሀቅ በቻልነው ሁሉ ላለማሰብ ስለምንሞክር፣ ጊዜያችንን በነጻነት ለማባከን ፍቃድ የተሰጠን ይመስለናል። እዚህ ላይ እኔ በምትኩ የማገኘው ምንድነው?” ብለን እምብዛም ሳንጠይቅ በዚያችው ባለችን ጊዜ ላይ ሰዎችና ክስተቶች ጊዜያችንን እንዲሰርቁን እንፈቅድላቸዋለን፡፡"


"እንዴት እንደምትጠቀምበት ካወቅክ፣
ሕይወት ረጅም ነው ነገሩ፣ ለመኖር ያለን ጊዜ አጭር ስለመሆኑ ሳይሆን ብዙውን ያባከንነው ስለመሆናችን ነው። በደንብ ከተጠቀምንበት ሕይወት በበቂ ሁኔታ ረጅም ነው ብዙ ታላላቅ ነገሮችን ለመስራት በበቂ ሁኔታ ተለክቶ የተሰጠ ነው። በድሎትና ችላ በማለት ውስጥ ካባከንነው፣ መልካም ፍጻሜ ለማግኘት ካልሰራን፣ በመጨረሻ ማለፉን እንኳን ከመረዳታትን በፊት አልፎ እናገኘዋለን። ስለዚህ የተቀበልነው ሕይወት አጭር አይደለም፤ አጭር ያደረግነው እኛ
ነን።”
-ሴኔካ

ስለዚህ ዛሬ ራስህን ስትጣደፍ ወይም “በቂ ጊዜ የለኝም፡፡” የሚሉትን ቃላት ስትናገር ብትሰማው፣ ቆም በልና ጥቂት ሰከንዶች ውሰድ፡፡ ይህ እውነት ነው? ወይስ ብዙ አላስፈላጊ ነገሮች በመስራት ተጠምደህ ነው? በእርግጥ ውጤታማ ነህ፣ ወይስ በሕይወትህ ውስጥ ብዙ የባከነ ነገር እንዳለ ትገምታለህ? በህይወታችን አብዛኛውን ጊዜ  የምናባክነው በማይጠቅሙን ሀሳቦች እና በማይረቡ ነገሮች ላይ ነው። እያንዳንዱን ደቂቃ የምንጠቀም ቢሆን ምን ያህል ጊዜ ሊተርፈን እንደሚችል አስቡ!!


"እንዲህም እላለሁ እንዲት ቀንም ቢሆን አልሰጥም - ማንም ቢሆን አንድ ቀኔን ሊመልስልኝ አይችልምና!!


ምንጭ -የእለት ፍልስፍና

@Zephilosophy
@Zephilosophy
5.0K viewsedited  19:48
ክፈት / አስተያየት ይስጡ