2022-09-26 23:08:28
የአለም ሙስሊም ሊቃውንቶች ህብረት መስራች ዶክተር ዩሱፍ አልቀርዳዊ
በእውቀት ሜዳ ላይ ታላቅ ፈረሰኛ ነው። በበርካታ ዘርፎች ላይ የጥበብ ጅረቱ ሲፈስ የጥልቅ ዕውቀቱ ፏፏቴ ድምፅና ውበት የብዙዎችን ልብ ገዝቷል። በቀላሉ የማይበጠስና የማይቀደድ በስሱ ተቋጥሮ የማይላላ ወፍራም አሻራው ደምቆ ይታያል። ግዙፍ ነው ሚዛን የሚደፋ ተንቀሳቃሸ ላይብረሪ። ዩሱፍ አብደላህ ይሰኛሉ። በእውቅ ስማቸው ዶክተር ዩሱፍ አልቀርዳዊ።
ሸይኹ እንደ አውሮፓውያን የዘመን ቀመር መስከረም 9 ቀን 1926 በአፍሪካ ጠርዝ ሰሜን ምስራቅ በምትገኘው የግብፅ ምድር በጋርቢያ ጠቅላይ ግዛት ሰፍጥ ቱራብ በተሰኘች መንደር ተወለደ። ወላጅ አባቱ በደማቅ የአደብ ፏፏቴ በስነምግባር የላቀ ሰው ነበር። ግና ህይወት በጎ ጎኗን እያጨበጨበችና እየተፍለቀለቀች አልነበረም የተቀበለችው። ገና በለጋነት ዕድሜው ጡጦ እንኳ ከአፉ ሳይጥል በሁለት ዓመቱ የልጅነት ጨዋታውን ሳይጠግብ አባቱን ከአጠገቡ አጣ። ወላጅ አባቱ ዳግም ላይመለስ ሕይወቱ አለፈ። የሞትን ፅዋ ተጎነጨና የቲም የሚል ስያሜን ተቸረ። ግና የመንፈስ የቲምነት ፈፅሞ አልተስተዋለበትም። ከልጅነቱ ጀምሮ ቀልብን የሚይዙ ኮስታራ ጉዳዮች የገጠሙት ሰው ነውና ወደፊትም ኮስታራ ወኔ ሊኖረው እንደሚችል መጠርጠር አይከብድም። ተወዳጁ ነብይ ረሱል(ሰለሏሁ ዓለይሂ ወሰለም) ትዝ አሉኝ የቲም አልነበሩ? ከርሳቸው ጀምሮ በብዛት በታሪክ ማህደር ውስጥ የጥበብን ፋኖስ ያበሩት ጀግኖች አይታሞች አልነበሩምን?!
የዚህ ታዳጊ ልጅ እድገት በአጎቱ ስር ሆነ። የልጁ አሳዳጊ የሆኑት አጎቱ በተርቢያ ኮትኩተው ያሳድጉት ጀመር። የአዕምሮው ልምላሜ ጥራትና እውነተኛው የጥበብ መናገሻ ባለቤት መሆኑ ከወዲሁ ሳያስታውቅ አልቀረም። ነገሮችን ከውስጠ ሚስጥራቸው ማስተንተን ይወዳል። በአዎንታዊ አቅጣጫ መመርመር ያስደስተዋል። የነገሮችን መልክ ገላልጦ ለመስረግ መሯሯጥ ይማርከዋል። "ትምህርቶችን ሲሸመድድ እንደ ህፃናት አልነበረም። በተደጋጋሚ ከንግግሩ እንደተሰማው ሽምደዳው በማስተንተን የታጀበና በማስተዋል የተደገፈ ነበር። በቃ በጠቢባን ጎዳና ላይ!" ይላሉ አንዱ ኡስታዛቸው።
ልጁ ከተወለደ አስር አመት ሳይሆነው ቁርአንን በቃል መሸምደድና አሳምሮ መቅራት ችሏል። በተጅዊድና ባማረ ቅላፄ የአላህን ቃል ያነበንበው ይዟል። በ11 ዓመቱ የጠማውን የኢስላማዊ ጥበብ ትምህርት ለመውሰድ ቋምጦ በመስጂድና በመድረሳ ሀለቃዎች ላይ መድመቅ ጀምሯል።
የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በአል-አዝሃር ዩኒቨርሲቲ ሲከታተል ቆይቶ እንደ አውሮፓውያን የዘመን ቀመር በ1958 በአረበኛ ቋንቋ እና በስነ-ጽሑፍ በከፍተኛ ውጤት ዲፕሎማ አገኘ። በ 1960 ከቁርአንና ሱና ሳይንስ ጥናት ማስተርሱን በሃይማኖት መሰረታዊ ጉዳዮች ፋኩሊቲም ዲፕሎማ አግኝቷል። የዶክትሬት ዲግሪ ከአንደኛ ደረጃ ሽልማት ጋር በ1973 ዓመት ተጎናፅፏል። ወጣቱ በእውቀት ባህር ኃይል የተገፋ ይመስል ሀገሩ ባሉ ሊቃውንት እውቀትን ሊወስድ ይገሰግስ ጀመር። የቀድሞ ቁስሉ በጥበብ ፍቅር ተነድፎ እፍ የተባለ ይመስል ከሱ ውጪ የሚዘምርለት ጉዳይ የለም። በቃ… ዒልም ብቻ!
በተለያዩ ዘርፎች ላይ የተፃፉ በርካታ መፅሃፍትን ቢሃፍዝም ህይወቱን ለሚያፈቅረው ነገር አሳልፎ ሰጥቷል፣ ድንቅ ተስፋዎችም አብረውት ተሰልፈዋልና የተራራው ውጣውረድ፣ የአቧራው አሰልቺነት ሳይበግረው ተንከራተ። እነዚያ ታላላቅ የስብዕና ባለቤት የሆኑት የአላህ አገልጋዮች ከከፈሉት መስዋትነት አንፃር ይህ ለወጣቱ ምንም ነው። ጭው ባለ ሜዳ ላይ በሙቀት ሲግል የቀደምቶችን የገድል ህይወት እያስታወሰ ይበረታል። ከየስፍራው የሸማመተውን ጥበብ ሰብስቦ ለሊቅነት የመብቃት ራዕይ ከውስጡ ተወለደ።። ጥቅጥቅ ባሉ የእውቀት መንገዶች ነጉዶ ሲያሰላስል የኖረ ተመራማሪ በመሆኑና በነጋ ጠባ ያለ መታከት የሚንከራተት ጥበብ ፈላጊ በመሆኑ የተነሳ ግብፅ ካፈራቻቸው ተራራ ሊቃውንት ተርታ በመሰለፍ የላቀ ክብርን ተጎናፀፈ።
ከአሁን በኋላ የኢስላም ሊቅ ሆኗልና በአንቱታ እየጠራሁ ታሪኩን ላስኮምኩማችሁ።
ዓላማቸው ማጥናትና ማስተማር ነው። መፅሀፍ መክተብ ፣ በአምልኮ መበርታትና ለሌሎች አገልግሎት የሚሆኑ ስራዎችን በመስራት ማሳለፍ። ከብዙ ትግሎች ጀርባም መሰለፍ። አዎ በእርግጥም ለጊዜያቸው በጣም ስሱ ናቸው። እሳቸው ዘንድ አንዲት ደቂቃ ብቻ ሳይሆን አንዲት ሴኮንድም ትልቅ ቦታ አላት። "የአንዲትን ሴኮንድ ዋጋ ለመረዳት ከመኪና አደጋ ለትንሽ የተረፈን ሰው ጠይቅ" የሚል መርህ አላቸው። በቃ እሳቸው የምግብ ማዐድ ላይ ሆነው ፣ ጉዞ ላይ ሆነው እንኳ የሚያነቡት መፅሃፍ የሚያጠኑት አንኳር ነጥብ ሳይኖር አይታዩም።
በስነምግባር ምጥቀት የፍጡራኑ አርአያ ናቸው። ቸርነታቸው፣ ጀግንነታቸው፣ ታማኝነታቸው፣ ፍትሃዊነታቸው፣ ቁጥብነታቸው፣ ቻይነታቸው፣ ቃል አክባሪነታቸው … ወዘተ ብዙዎችን ያስደመመና ያስናቀ ነበር። የገዘፈ ክብር እንዲዘንብላቸው የማይሹና ከፍ ከፍ ማለትን የማይፈልጉ ፣መተናነስ መለያ ባህሪያቸውም ነበር።
አንዳንድ አመለካከቶቻቸው እና ፈትዋዎቻቸው በአንዳንድ ምሁራኖች ዘንድ ተቀባይነትን አላገኙም። ምክንያቱም ከቁርአንና ሀዲስ ማስረጃ ይልቅ ረዕዩን ያስቀድማልና ነው። ግና ደጋፊዎቹ እንደሚናገሩት በሸሪዓ ዓላማዎች ላይ የኡሱሉል ፊቅሂ ሕጎችን መሠረት በማድረግ ጥልቅ የፊቅሂ ግንዛቤን በማግኘቱ ረገድ ተሳክቶለታል ይላሉ። ከ170 በላይ መፅሃፍትን ከትበዋል። አነሆ አንድ ክፍለ ዘመንን ሊኖሩ አራት አመት ሲቀራቸው ይህንን አለም ተሰናበቱ። መልካም ስራቸውን አላህ ይቀበላቸው። ስህተታቸውን ይቅር ብሎ ቀብራቸውን የጀነት ጨፌ ያድርግላቸው።
በርካታ ከሸሪዓ ጋር የሚጋጩ ንግግሮችና ፅሑፎች እንዳሏቸው ባምንም፣ ብዙ ኡለማኦች ለእያንዳንዱ ንግግር ከበቂ በላይ ምላሽ ስለሰጡበት ስህተታቸውን መዘከሩ አግባብም አደብም ባለመሆኑ በመልካም አውስቶ ማለፍንና አላህ እንዲምራቸው መጠየቅን ከአደብ ቆጥሬ አላሁመግፊር ለሁ ወርሀምሁ ብዬ አላህን እጠይቀዋለሁ።
33 views🅡🅔🅨🅐🅝 ●, 20:08