2023-01-11 06:24:36
Daniel:
✞ እንኩዋን ለቅዱሳን "ሕጻናተ ቤተ ልሔም" እና "አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞
+*" ሕጻናተ ቤተ ልሔም "*+
=>በሮሙ ቄሣር በአውግስጦስ ዘመን ሰው ሁሉ ይቆጠር ዘንድ አዋጅ ወጥቷልና እመ ብርሃን ማርያም ከቅዱሳኑ ዘመዶቿ ዮሴፍና ሰሎሜ ጋር ወደ አባቷ ዳዊት ከተማ ወደ ቤተ ልሔም ሔደች::
+በዚያም ሳሉ የምትወልድበት ጊዜ ቢደርስ በፍጹም ድንግልና እንደ ጸነሰችው ሁሉ በፍጹም ድንግልና ወለደችው:: (ኢሳ. 7:14, ሕዝ. 44:1) ተፈትሖም አላገኛትም:: ልማደ አንስትም አልጐበኛትም:: ምጥም አልነበረባትም::
+በጊዜውም በምሥራቅ የፋርስ: የባቢሎንና የሳባ ነገሥት አስቀድሞ ከበለዓም: በሁዋላም ከዠረደሸት በተረዱት መሠረት ኮከቡን በማየታቸው ታጥቀው ተነሱ::
+ከምሥራቅ አፍሪቃና ከእስያም በተመሳሳይ ኮከቡን በማየታቸው 12 ነገሥታት በየግላቸው 10 10 ሺህ ሠራዊትን እየያዙ ድንግልንና ንጉሥ ልጇን ፍለጋ ወጡ::
+12ቱ ነገሥታት ከነ ሠራዊታቸው ሲሔዱ ስንቃቸው በማለቁ 9 ነገሥታት ተስፋ ቆርጠው ተመለሱ:: 3ቱ ግን በፍጹም ጥብዓት ከ30ሺ ሠራዊት ጋር በኮከብ እየተመሩ ኢየሩሳሌም ደረሱ::
+እነዚህም መሊኩ የኢትዮዽያ (የሳባ ንጉሥ ተወራጅ): በዲዳስፋና መኑሲያ (ማንቱሲማር) ደግሞ የፋርስና የባቢሎን ነገሥታት ናቸው:: ወደ ኢየሩሳሌም ሲደርሱም ሔሮድስና ሠራዊቱ ታወኩ::
+እነርሱ ግን የቤተ ልሔምን ዜና ከጠየቁ በሁዋላ በጐል ድንግል ማርያምን: ክርስቶስን: ዮሴፍና ሰሎሜን አገኙ:: ለ2 ዓመታት እነርሱን ፍለጋ ደክመዋል: ተንከራተዋልና ደስታቸው ወሰን አጣ::
+በእመቤታችንና በልጇ ፊት በደስታ ዘለሉ:: "አንፈርዓጹ ሰብአ ሰገል" እንዲል:: ወርቁን: እጣኑንና ከርቤውንም ገብረው በግንባራቸው በፊቱ ሰገዱ:: 3 ጊዜ እየወጡ እየገቡ ቢመለከቱት በኪነ ጥበቡ አንዴ እንደ ሕጻን: በ2ኛው እንደ ወጣት: በ3ኛው እንደ አረጋዊ ሆኖ ታይቷቸው ፈጽመው አድንቀዋል::
+ወደ ሃገራቸው ሲመለሱም "ወአስነቀቶሙ ሕብስተ ሰገም" እንዲል የገብስ ዳቦ ጋግራ ድንግል ሰጠቻቸው:: እነርሱም ይህንን እየተመገቡ የ2 ዓመቱን መንገድ በ40 ቀን ሲጨርሱት ዳቦው ግን ያ ሁሉ ሺህ ሰው ተመግቦት አላለቀም:: ተአምራትንም ሠርቷል::
+ሰብአ ሰገል ቅዱስ መልአክ እንደ ነገራቸው በሔሮድስ ዘንድ ሳይሆን በሌላ ጐዳና ተጉዘው ሃገራቸውን መግባታቸውን ንጉሡ ሰማ:: እንደ ዘበቱበት ሲያውቅም የሚያደርገው ጠፍቶበት ወደ ቤቱ ገባ::
+በሕሊናው የሚመላለሰውም አንድ ነገር ብቻ ነበር:: የአይሁድ ንጉሥ የተባለውን (እርሱስ የሰማይና የምድር ሁሉ ንጉሥ ነው) እንዴት ሊያጠፋው እንደሚችል ያስብ ነበር:: በዚያች ሰዓትም ሰይጣን በሰው ተመስሎ ወደ እርሱ ቀረበ::
+ሕጻኑን እንዴት ሊገድለው እንደሚችል ነግሮት: በዓለም ታይቶ የማይታወቀውን ጭካኔ አስተማረው:: ርጉም ሔሮድስም ሠራዊቱን ጠርቶ "አዋጅ ንገሩልኝ" አላቸው::
+እነርሱም "በቤተ ልሔምና በአውራጃዋ: በይሁዳም የምትገኙ እናቶች:- አውግስጦስ ቄሣር ሕጻናትን በማርና በወተት አሳድገህ ለሹመት አብቃልኝ: ለእናቶቻቸውም ወርቅና ብር ስጥልኝ ስላለ 2 ዓመትና ከዚያ በታች የሆናቸውን ሕጻናት ሁሉ አምጡ" እያሉ አዋጁን ነገሩ::
+የቤተ ልሔምና የአካባቢዋ እናቶችም ያላቸው አንድም: ሁለትም እየያዙ: የሌላቸው ደግሞ እየተዋሱ ወደ ሔሮድስ ዘንድ ይዘዋቸው መጡ:: ያን ጊዜ አውሬው ሔሮድስ እናቶችን በአንድ ቦታ እንዲታጐሩ አድርጐ ሕጻናቱን በወታደሮቹ አሳፍሶ ወደ ተራራ አወጣቸው::
+በሥፍራውም ተወዳዳሪ በሌለው ጭካኔ 1,200 ወታደሮቹን አሰልፎ ሕጻናቱን አሳረዳቸው:: ሰይፍ የበላቸው የቤተ ልሔም ሕጻናት ቁጥርም 144,000 ሆነ::
+የሕጻናቱ ደም ከተራራው እንደ ጐርፍ ወረደ:: የእናቶች የጡት ወተትም በመሬት ላይ ይፈስ ነበርና ተቀላቀለ:: የቤተ ልሔም እናቶች አንጀታቸው በእጥፉ ተቆረጠ:: ታላቅ ሰቆቃም አካቢውን ሞላው:: ዋይታም ሆነ::
+ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ እንዳለው ነቢዩ ኤርምያስ የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ:: "ራሔል ስለ ልጆቿ አለቀሰች:: የሉምና መጽናናት አልቻለችም" (ማቴ. 2:18, ኤር. 31:15)
+ሰይጣን ግን አላማው እንዳልተሳካና ድንግልና አምላክ ልጇ መሸሻቸውን ሲያውቅ ይህንኑ ለሔሮድስ ሹክ አለው:: ስለዚህም ንግሥተ አርያም ድንግል ማርያምና ወልደ አምላክ ልጇ በስደት ለ3 ዓመት ከ6 ወር ተንገላቱ::
+እንደ ገናም ክፉ ሰዎች መጥተው ለሔሮድስ አሉት:- "አንተ የምትሻው በዘካርያስ ቤት አለና ግደለው::"
ሔሮድስም ወታደሮቹን ልኮ: ሕጻኑን ቅዱስ ዮሐንስን ቢያጣው ደጉን ነቢይ: አረጋዊ ዘካርያስን በቤተ መቅደስ መካከል ገድሎታል::
+በጊዜው የሚፈርድ እግዚአብሔርም ስለ ሕጻናቱ ደም ተበቅሎ ሔሮድስን አጠፋው:: ወደ እመቀ እመቃትም አወረደው:: 144 ሺው ንጹሐን ሕጻናት ግን ስልጣነ ሰማይ ተሰጣቸው:: ከእነርሱ በቀር ማንም በማያውቀው ምሥጢርና ዜማ ፈጣሪያቸውን ይሠልሱትና ይቀድሱት ዘንድም አደላቸው:: (ራዕ. 14:1)
+አባ ሕርያቆስ በሐዳፌ ነፍስ ድርሰቱ "ያስምዓነ ቃለ መሰናቁት ዘሕጻናት-የሕጻናትን የመሰንቆ ድምጽ ያሰማን" እንዳለ:: (ቅዳሴ ማርያም)
+እነዚህ 144 ሺህ ንጹሐን ሕጻናት ዛሬ በሰማይ ለምዕመናን ምሕረትን: ለጨካኞች ፍርድን ይለምናሉ:: በፍርድ ቀንም በጌታ ፊት በክብር ቅንዋቶቹን ይዘው ይመጣሉ::
<< ክብራቸው ታላቅ ነውና ለቅዱሳን ሕጻናት ምስጋና ይሁን !! >>
+*" አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ "*+
=>በሃገራችን እጅግ ዝነኛ ከሆኑ ቅዱሳን አንዱ አባ ሊባኖስ ናቸው:: እርሳቸው እንደ ተስዓቱ (ዘጠኙ) ቅዱሳንና አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሁሉ ከውጪ ሃገር የመጡ ናቸው::
+የነበሩበት ዘመንም 5ኛው መቶ ክ/ዘመን መጨረሻና 6ኛው መቶ ክ/ዘመን ውስጥ ነው:: ጻድቁ አባ ሊባኖስን "አባ መጣዕ" እያሉ መጥራት የተለመደ ነው:: "መጣዕ" ማለት ኤርትራ ውስጥ የሚገኝና ጻድቁ በተጋድሏቸው የቀደሱት ቦታ ነው:: ጥንተ ታሪካቸውስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-
+አባ ሊባኖስ ትውልዳቸው ከሮም ታላላቅ ሰዎች ነው:: አባታቸው አብርሃም: እናታቸው ደግሞ ንግሥት ይባላሉ:: በብሥራተ መልአክ ተጸንሰው ስለ ተወለዱ ስማቸውም በዚያው "ሊባኖስ" ተብሏል::
+"ሊባኖስ" እመ ብርሃን የተወለደችበት ቅዱስ ሥፍራ ሲሆን በጥሬ ትርጉሙ "ደጋ" ማለት ነው:: ምሥጢራዊ ትርጉሙ ግን ለጻድቅነት ያገለግላል:: አባ ሊባኖስ በሃገራቸው ሮም ከወላጆቻቸው ጋር አድገው ለአካለ መጠን ሲደርሱ ከወደ ቁስጥንጥንያ ሸጋ ብላቴና አጭተው አጋቧቸው::
+ወጣቱ አባ ሊባኖስ ግን ማታ "ወደ ጫጉላ አልገባም" ብለው እንቢ አሉ:: ለዚያች ሌሊት ብቻ ከአባታቸው ጋር እንዲያድሩ ተፈቀደላቸው:: መጻሕፍትን የተማሩ ነበሩና በሌሊት ምን እንደሚያደርጉ ሲያወጡ: ሲያወርዱ ቅዱስ መልአክ ከሰማይ ወርዶ 3 ጊዜ "ሊባኖስ" ብሎ ጠራቸው::
+"እነሆኝ ጌታየ!" ቢሉት ከአባታቸው ጐን ነጥሎ እያጫወተ ሳይታወቃቸው ከሮም ግብጽ (ገዳመ ዳውናስ) አደረሳቸው::
+በጊዜው ታላቁ ኮከብ ቅዱስ ዻኩሚስ ነበር:: አባ ሊባኖስን አስተምሮ አመነኮሳቸው: በዓትም ለየላቸው:: በዚያ ለተወሰነ ጊዜ እንደቆዩም ቅዱሱ መልአክ መጥቶ "ለዘለዓለም መጠሪያህ በዚያ ነውና ወደ ኢትዮዽያ ሒድ" አላቸው::
909 views03:24