2023-01-30 08:00:25
Daniel:
✞ ✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ ፡፡ አሜን ፡፡ ✞ ✞
ጥር 22 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
+ + አባ እንጦንስ + +
=>በቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ "ታላቁ / ዓቢይ / THE GREAT" የሚል ስም የሚሰጣቸው አባቶች የተለዩ
ናቸው::
አንድም እጅግ ብዙ ትሩፋቶችን የሠሩ ናቸው:: በሌላ
በኩል ደግሞ በተመሳሳይ ስም ከሚጠሩ ሌሎች ቅዱሳን
እንለይበታለን::
+ገዳማዊ ሕይወት ጥንቱ ብሉይ ኪዳን ነው::
በቀዳሚነትም በደብር ቅዱስ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ደቂቀ
ሴት እንደ ጀመሩት
ይታመናል:: ሕይወቱ በጐላ: በተረዳ መንገድ የታየው ግን
በታላቁ ጻድቅ ሄኖክ: ከዚያም በቅዱሱ ካህን መልከ
ጼዴቅ
አማካኝነት ነው::
+ቀጥሎም እነ ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ: እነ ኤልሳዕ ደቀ
መዝሙሩ ኑረውበታል:: በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ሙሉ
ሕይወቱን በገዳም
(በበርሃ) ያሳለፈው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ
ቅድሚያውን ይይዛል::
+ለስም አጠራሩ ስግደት ይሁንና መድኃኒታችን ክርስቶስ
በገዳመ ቆረንቶስ ለ40 ቀናት በትሕርምት ኑሮ ገዳማዊ
ሕይወትን
ቀድሷል: አስተምሯል:: በዘመነ ስብከቱም ያድርባት
የነበረችው የደብረ ዘይቷ በዓቱ (ኤሌዎን ዋሻ) በራሷ
ለዚህ ሕይወት
ትልቅ ማሳያ ናት::
+ከጌታ ዕርገት በኋላም ክርስቲያኖቹ የዓለም ሁካታ
ሲሰለቻቸው: አንድም በንጹሕና በተሸከፈ ልቡና
ለፈጣሪያቸው መገዛትን
ሲሹ ከከተማ ወጣ እያሉ ይኖሩ እንደ ነበር የታሪክ
መዛግብት ያሳያሉ:: አኗኗራቸውም በቡድንም: በነጠላም
ሊሆን ይችላል::
+ዋናው ነገር ግን በጾምና በጸሎት መትጋታቸው ነው::
ይሕም ሲያያዝ እስከ 3ኛው መቶ ክ/ዘመን ደረሰ:: በዚህ
ዘመን
ግን አባ ዻውሊ የሚባል አንድ ንጹሕ ክርስቲያን ይሕንን
ሕይወት ወደ ሌላ ደረጃ ከፍ አደረገው::
ለ80 ዓመታት ሰው ሳያይ ተጋድሎ 'የባሕታውያን አባት'
ተባለ:: ደንብ ያለው ተባሕትዎም ጀመረ::
+ይህ ከሆነ ከ20 ዓመታት በኋላ ደግሞ አባ እንጦንስ
የሚባሉ ደግ ክርስቲያን ይህንን ገዳማዊ ሕይወት በሌላ
መንገድ
አጣፈጡት:: በቅዱስ ሚካኤል አመንኳሽነት ገዳማዊ
ሕይወት በምንኩስና ተቃኘ:: ስለዚህም አባ እንጦንስ
የመነኮሳት አባት ተባሉ::
+እርሳቸውም ሕይወቱን ለማስፋፋት ከተለያዩ አሕጉር ደቀ
መዛሙርትን እየተቀበሉ አመንኩሰዋል:: ቅዱሳን የአባ
እንጦንስ
ልጆችም ወደየ ሃገራቸው ተመልሰው: ሕይወቱን በተግባር
አሳይተው ገዳማዊነትን አስፋፍተዋል::
+"+ አባ እንጦንስ +"+
+አባ እንጦንስ የመነኮሳት ሁሉ አባታቸው: ለገዳማውያን
ሁሉም ሞገሳቸው ናቸው:: እንዲያውም ብዙ ጊዜ "ኮከበ
ገዳም:
ማኅቶተ ገድል (የበርሃው ኮከብ: የተጋድሎ መብራት)"
ተብለውም ይጠራሉ::
+ቤተ ክርስቲያን ለጀማሪዎች ትልቅ ትኩረት ትሰጣለች::
ለምሳሌ:- አባ ዻውሊን (የካቲት 2 የሚከበሩ)
ለብሕትውና
መሠረትን ስለ ጣሉ "አበ ባሕታውያን" ብላ ታከብራለች::
አባ እንጦንስን ደግሞ "አበ መነኮሳት (የመነኮሳት አባት):
ቀዳሚሆሙ ለመነኮሳት (ለመነኮሳት ቀዳሚና ጀማሪ)
ስትል ትጠራቸዋለች::
+አባ እንጦንስ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ለሚነሱ ቅዱሳን
መነኮሳት ሁሉ መንገድን ይጠርጉ ዘንድ ብዙ መከራን
በትዕግስትና
በአኮቴት ተቀብለዋል:: ላለፉት 1,700 ዓመታት እንደ
ሻማ እየቀለጡ ያበሩ አበው ቅዱሳን ሁሉ የአባ እንጦንስ
ልጆች ናቸው::
+ከምጥ የከፋ የዲያብሎስ ፈተናን ተቀብለው ከመንፈሳዊ
አብራካቸው ቅዱሳኑን ወልደዋል:: የመነኮሳት አለቃ
የሆኑትን
ታላቁን መቃርዮስን ጨምሮ በርካቶችን አመንኩሰው
ለቅድስና አብቅተዋል::
+አባ እንጦንስ ግብጻዊ ሲሆኑ የተወለዱት አቅማን
በምትባል ቦታ አካባቢ ነው:: ጊዜውም በ252 ዓ/ም
ነው:: የተባረኩ
ወላጆች ለቅዱሱ እንጦንስና አስከትለው ለወለዷት ሴት
ልጃቸው አስቀድመው ፍቅረ ክርስቶስን: አስከትለውም
ሃብት
ንብረታቸውን አውርሰው ዐርፈዋል::
+በዚህ ጊዜ የአባ እንጦንስ እድሜ አፍላ ወጣትነት ላይ
ነበር:: በልጅነት ጊዜአቸውም አባ እንጦንስን ሲስቁ:
ሲጫወቱ:
አልያም ሲቀልዱ አየሁ የሚል ሰው አልነበረም:: ፍጹም
ቁም ነገረኛና ታዛዥ: በዚያ ላይም አስተዋይ ነበሩና ሙሉ
ጊዜአቸውንም ከቅዱስ ቃሉ በመመገብ: በትምሕርትና
በማስቀደስ ያሳልፉ ነበር::
+ዘወትርም ዜና ሐዋርያትን እያነበቡ በመንፈሳዊ ቅናት
ይቃጠሉ ነበር:: በጊዜው የምናኔ ሕይወት ጐልቶ ባለ
መገለጡ አባ
እንጦንስ የሚያደርጉት ይጨንቃቸው ነበር:: ሲጸልዩም
"አበው ሐዋርያት ይሕንን ክፉ ዓለም ንቃችሁ ጌታችሁን
የተከተላችሁበት ጥበብ እንደ ምን ያለ ነው!" እያሉ
ይደነቁ ነበር:: መሻታቸውን ያወቀ ጌታም ምሥጢርን
ገለጠላቸው::
+አንድ ቀን በቅዳሴ ላይ ወንጌል ሲነበብ ካህኑ ስለ
ምናኔ የሚጠቅሰውን ክፍል አነበበ:: ለአንድ ባለ ጠጋ
ሕግጋትን
ከነገረው በኋላ "ፍጹም ልትሆን ከወደድክስ ያለህን ሁሉ
ሸጠህ ተከተለኝ" (ማር. 10:17) የሚለውን ጥቅስ
ሲሰሙ
ተገርመው "ጌታ ሆይ! ይህንን የተናገርኸው ለእኔ ነው"
ሲሉ አሰቡ:: በቀጥታም ሃብታቸውን ለአካባቢው ሰው
አካፍለው:
እህታቸውን ከደናግል ማኅበር ደምረው እርሳቸው ወደ ዱር
ሔዱ::
+ከዚህች ቀን ጀምረው አባ እንጦንስ ከ80 እስከ መቶ
ለሚገመቱ ዓመታት ከአጋንንት ጋር በጦርነት ነበር
የኖሩት::
በንጹሕ አምልኮታቸውና በቅድስናቸው የቀና ጠላት
ሰይጣን በብዙ ጐዳና ፈተናቸው:: አቅም ቢያጥረው
አራዊትን መስሎ
ታገላቸው::
+በዚህ አልሳካ ቢለው የእሳት ሰንሰለትን አምጥቶ
ገረፋቸው:: በሞትና በሕይወት መካከል ጥሏቸው ሔደ::
ወድቀው
ያገነኟቸው ሰዎች ለዘመዶቻቸው ሰጥተዋቸው አገገሙ::
ልክ ሲነቁ ግን ፈጥነው ወደ በርሃ ተመለሱ::
+ሰይጣን በርሃው የቅዱሳን ማደሪያ እንዳይሆን ሰግቷልና
ጨክኖ ታገላቸው:: ግን አልቻላቸውምና ተረታ:: አምላከ
ኃያላን
ክርስቶስ ከቅዱሱ ጋር ነበርና:: ከዚህ በኋላ ግን ጸጋው
በዝቶላቸው ድውያንን የሚፈውሱና ሰይጣን
የማይቀርባቸው ሰው
ሆኑ::
+በረዥም ዘመነ ቅድስናቸውም:-
1.ብዙ አርድእትን ከመላው ዓለም ሰብስበው:
አስተምረው: ምናኔ ከግብጽ ማዶ በመላው ዓለም
አስፋፉ::
2.በደመና እየተጫኑ ብዙ አሕጉራትንም እየዞሩ ሰበኩ::
በዚህም አሕዛብን ወደ እምነት: ኃጥአንን ወደ ንስሃ
መለሱ::
3.ጊዜው ዘመነ ሰማዕታት ነበርና ወደ አደባባይ ሒደው
ከሃዲዎችን ገሠጹ:: ማንም ደፍሮ ግን አልገደላቸውም::
+እነዚህንና ሌሎች ተግባራትን እየሠሩ በቅዱስ ሚካኤል
እጅ መነኮሱ:: እርሳቸውም ብዙዎችን አመነኮሱ::
አርጅተው እንኳ
ከተጋድሎ ያላረፉት አባታችን የጣመ ነገር ቀምሰው:
ገላቸውን ታጥበው አያውቁም:: በ372 ዓ/ም በዚህች ቀን
ሲያርፉም
ዕድሜአቸው 120 ደርሶ ነበር::
+የአባ እንጦንስን በዓል ለማክበር የምትሹ ቤተ
ክርስቲያናቸው ጎንደር ከተማ ከቀሃ ኢየሱስ በላይ
ይገኛል::
<< ለአባታችን እንጦንዮስ / እንጦንስ / እንጦኒ ክብር
ይገባል:: >>
+" ቅዱስ ዑራኤል "+
+በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት ከ7ቱ ሊቃነ
መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ዑራኤል:-
1.2K views05:00