2023-04-04 21:32:01
" እኛ እንዲህ ዓይነት ዘረፋ ይኖራል ብለንም አስበን አናውቅም " - የዘረፋው መርማሪ
ጠቅላላ ዘረፋውን ለመፈጸም የወሰደው 2 ሰዓት ከ13 ደቂቃ ነው።
ዘረፋው በተመሳሳይ ሰዓት፣ በ28 አገራት ውስጥ ነው የተፈፀመው።
ነገሩን በአጭሩ ለማስቀመጥ ተራ ግለሰቦች ወደ ባንክ ኤቲኤም ማሽን ሄደው ገንዘብ ያወጡበት ዘረፋ ነው።
ይህ እንዴት ሆነ ? የሚለውን እንመልከት።
በሕንድ የተወሰኑ ሰዎች ለአስተኔ ገጸባሕሪ (extra role) ፊልም ቀረጻ ተመለመሉ። ደስም አላቸው።
የተሰጣቸው ሚና ከኤቲኤም ማሽን ብር ማውጣት ነው።
ሕንድ ሀገር ማሃራሽትራ የሚገኙ ምልምል ተዋናዮች ድርጊቱን ሲፈጽሙ ለፊልም ቀረጻ መስሏቸዋል።
የታላቁ የገንዘብ ርቆት አካል እንደተደረጉ በፍጹም አያውቁም።
ይህ የሆነው በሐምሌ 2018 ሰንበት ነበር።
ኮስሞስ ይባላል የተዘረፈው ባንክ።
ጭር ባለው የሰንበት ዕለት ድንገት ዋናው የባንኩ መሥሪያ ቤት ያሉ ሠራተኞች መልዕክት ደረሳቸው። መልዕክቱ የሚመጣው ከአሜሪካ የቪዛ ካርድ ኩባንያ ነበር።
ቪዛ ኩባንያ ለኮስሞስ ባንክ ሰዎች በቀጣይ ደቂቃዎች በርካታ የገንዘብ ጥያቄዎች ሊቀርቡላችሁ ይችላል ሲሉ አስጠነቀቁ። ያልተለመዱ ነገሮች በኤቲኤም አካባቢ እየታዩ እንደሆነ አብራሩ።
ግን የኮስሞስ ባንክ ሰዎች ምንድነው የምታወሩት በሚል ቸል አሉት ማስጠንቀቂያውን ነገሩ ሊገባቸው አልቻለም። ምክንያቱም እነርሱ ሲስተም ላይ የሚታይ ምንም የተለየ ነገር የለም።
ከግማሽ ሰዓት በኋላ ቪዛ ኩባንያ በድጋሚ ወደ ኮስሞስ ደወለ።
" እኔ ጋ የሚታዩ ምልክቶች ጤናማ አይመስሉም፤ ለማንኛውም ሁሉምን ኤቲኤም ማሽኖቻችሁን ለጊዜው ከጥቅም ውጭ አድርጉ " አላቸው።
ይህ ለኮስሞስ ባንክ ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል ውሳኔ ቢሆንም ምክሩን ተቀብለው ኤቲኤም ማሽኖቻቸውን ዘጉ።
እንዲያም ሆኖ ዘግይተዋል። ኮስሞስ ባንክ በዚያች ሁለት ሰዓት ብቻ 14 ሚሊዮን ዶላር ተዘርፈው ነበር።
ይህን ዘረፋ ማን አቀነባበረው ?
ይህ ዘረፋ በ28 አገሮች ውስጥ በሚገኙ ኤቲኤም ማሽኖች ላይ በተመሳሳይ ሰዓት የተፈጸመ ነው።
- ሩሲያ፣
- አሜሪካ፣
- ካናዳ፣
- ዩናይትድ ኪንግደም፣
- ዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ይገኙበታል።
ሂደቱ በሰሜን ኮሪያ ጠላፊዎች መመራቱ እንደተደረሰበት ተነግሯል።
የዝርፊያው አቀናባሪዎች ላይ ከመደረሱ በፊት የባንኩ ሰዎች ለምን በርካታ ሰዎች #በተመሳሳይ ሰዓት ወደ ኤቲኤም ማሽን ሄደው ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ እንደሚወስዱ ግራ ገብቷቸው ነበር።
የዘረፋው መርማሪ፣ “እኛ እንዲህ ዓይነት ዘረፋ ይኖራል ብለንም አስበን አናውቅም” ይላሉ።
የደኅንነት ካሜራ (ሲሲቲቪ) ምስሎችን በመጠቀም የሕንድ መርማሪዎች ለጊዜው 18 ሰዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋል ቻሉ። እነዚህ ሰዎች ተራ ሰዎች ናቸው። ሾፌሮች፣ የቡና ቤት አስተናጋጆች፣ ጫማ ጠራጊዎች ይገኙበታል።
እነርሱ ለፊልም ቀረጻ መመልመላቸውን እንጂ ማን እየተጠቀመባቸውን እንደነሆ አያውቁም ነበር።
በመጨረሻ ከዚህ ጥንቅቅ ካለ ዘረፋ ጀርባ ያለው ‘አልአዛር’ የተሰኘው የሰሜን ኮሪያ ጠላፊዎች ቡድን እንደሆነ ተደረሰበት።
እንዴት ግን ቡድኑ በ28 አገራት ዘራፊ ሊያሰማራ ቻለ ?
ዘራፊና አዘራፊን አገናኝ ደላላ ፦
" አልአዛር " በሚል የሚጠራው የዘራፊዎች ቡድን የሰሜን ኮሪያ የወታደራዊ ደኅንነት መሥሪያ ቤት የሚመራው ነው ይባላል።
" አልአዛር " የሚለውን ስም ያገኘውም ከመጽሐፍ ቅዱስ ሞቶ ከተነሳው አልአዛር ነው።
የእነርሱ የኮምፒውተር ቫይረሶች አንዴ ከገቡ ሁሉን ነገር ይገድላሉ። ኮምፒውተር ሲስተሙን መልሰው መቀስቀስ የሚችሉት እነርሱ ብቻ ናቸው። ከእዚሁ ተግባራቸው ጋር ተያይዞ ነው አልአዛር የሚለው ስያሜ የተሰጣቸው።
ከዚህ ቀደም፦
- ሆሊውድን፣
- ሶኒ ፒክቸርስን እና ሌሎችንም ግዙፍ መሥሪያ ቤቶች መረጃ ዘርፈዋል።
ከባንግላዴሽ ባንክ አንድ ቢሊዮን ዶላር ለመዝረፍ ሞክረዋል።
ሰሜን ኮሪያ ይህ " አልአዛር " የተሰኘው ቡድን በአገሬ ስለመኖሩ አላውቅም ስትል ታስተባብላለች።
ቡድኑ (አልአዛር) ኮስሞስ ባንክ ላይ ለፈጸመው ዘረፋ የተጠቀመው " ጃክፖት " የሚባለውን ስልት ነው። ይህ ስም የተሰጠው ልክ እንደ መቆመሪያ ማሽን ኤቲኤም ገንዘብ እንዲተፋ ስለሚያደርግ ነው።
" አልአዛር " ቡድን ይህን ስልት በተግባር ከማዋሉ በፊት የተመሳሰለ ኢሜይል ወደ ባንኩ ሰዎች በመላክ እንዲከፍቱት ካደረገ በኋላ ወደ ባንኩ ሲስተም ሰርጎ መግባት ችሏል።
ከዚያም የባንኩን የቁጥጥር ሥርዓትን ካሉበት ሆነው ማዘዘ ቻሉ።
ይህ መቆጣጠሪያ ባንኩ የገንዘብ ወጪ ጥያቄ ሲቀርብለት ማሽኑ ገንዘብ እንዲተፋ የሚያዝ ሥርዓት ነው።
ማለትም ከየትኛውም የዓለም ክፍል ከሚገኝ ኤቲኤም የገንዘብ ትዕዛዝ ቢመጣ ሰርሳሪዎቹ ማሽኑ ገንዘቡን እንዲለቀው ማድረግ ያስችላቸዋል።
የማይችሉት አንድ ማሽን ምን ያህል ገንዘብ መልቀቅ እንዳለበት መወሰን ነበር። ብዙ ገንዘብ ለማውጣት ደግሞ የግድ ብዙ ካርድ ማተም ነበረባቸው።
የሚቀራቸው ተመሳሳይ #የኤቲኤም_ካርድ_ህትመት ነው። ይህን የሚሠራ ሌላ ድርጅት ተገኘ።
አስገራሚው እሱ አይደለም፤ ሰሜን ኮሪያዊያን እንዴት ከ28 አገር በተመሳሳይ ጊዜ ገንዘብ የሚያወጡላቸው ሰዎችን ማዘጋጀት ቻሉ ? ምክንያቱም ቪዛ ለማግኘት ራሱ ብዙ ችግር የሚያዩ ናቸው።
ይህን ሥራ ለሌላ ለሚተባበራቸው ድርጅት ኃላፊነት መስጠት ነበረባቸው።
በበይነ መረብ በተዘረጋው የጠላፊዎች ግንኙነት አንድ ሰው ይህን ሥራ እንደሚሠራ ገለጸ።
ይህ ቢግቦስ በሚል ስም የሚጠራው መረጃ ቦርቧሪ ግለሰብ ኤቲኤም ካርዶችን ማምረት እና ሰዎችንም ማዘጋጀት እንደሚችል ገለጸ።
በካናዳና አሜሪካ ተቀጣሪ ሊሆኑ የሚችሉ እንዲሁም ከኤቲኤም ማሽን ገንዘብ ማውጣት የሚቸሉ ግለሰቦችን እንደሚመለምል አስታወቀ።
ይህ በትክክል አልአዛር ቡድን የሚፈልገው አገልግሎት ነበር። ቢግቦስ እና አልአዛር አብረው ጥምረት ፈጠሩ።
ቢግቦስ ለ14 ዓመታት በስርቆት የተሰማራ ማንነቱ ሳይታወቅ የቆየ ግለሰብ ነበር። የሆነ ወቅት ላይ ማንነቱ ተደርሶበት አሜሪካ ውስጥ በመኖርያ ቤቱ ሳለ ተይዞ አሁን ዘብጥያ ወርዷል። የ35 ዓመት ካናዳዊ ነው።
እርሱን መያዝ ቢቻልም የባንኩ 14 ሚሊዮን ዶላር ግን እስከወዲያኛው ቀልጦ ቀርቷል። እነዚህ የሰሜን ኮሪያ ሰርሳሪዎች በፍጹም ዝቀተኛ ገንዘብ ላይ ጊዜያቸውን አያጠፉም። እንዲያውም አሁን አሁን ላይ ትኩረታቸውን ወደ ክሪፕቶከረንሲ አዞረው ወደ 3.2 ቢሊዮን ዶላር ዘርፈዋል።
የአሜሪካ ባለሥልጣናት አልአዛር የተባለውን የዓለም ግዙፍ የባንክ ዘራፊ ቡድን ብሎ ይጠራዋል ለዚያውም ያለ አንዳች የጦር መሣሪያ።
Credit : BBC AMHARIC, Tikvah
#Share
@ethio_techs @ethio_techs
1.9K viewsPOLY, 18:32