2022-08-30 05:45:42
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስቅዱስ ስም ነሐሴ ሃያ አራት በዚህች ቀን የክርስቶስ ምስክሩና ሐዋርያው የሆነ ተጋዳይ ቅዱስ ቶማስ የመርዓስ ኤጲስቆጶስ አረፈ።
የዚህንም አባት ትሩፋቱንና ገድሉን ሰው ተናግሮ ሊፈጽመው አይችልም እርሱ አስቀድሞ በጾም በጸሎት በሰጊድ ቀንና ሌሊትም በመትጋት ለድኆችና ለምስኪኖች በመራራት ተጠምዶ የሚኖር ነው። ከዚህም በኋላ መርዓስ ለሚባል አገር ኤጲስቆጶስ ይሆን ዘንድ የክብር ባለቤት ጌታችን መረጠው መንጋውንም እንደ ሐዋርያት ጠበቀ። ከሀዲ ዲዮቅልጥያኖስም በነገሠ ጊዜ ክርስቲያኖችን ያሠቃያቸው ዘንድ ከመኳንንቶቹ አንዱ ወደዚያች አገር ደረሰ እርሱም ቅዱስ ቶማስን ወደ እርሱ ያቀርቡት ዘንድ ጭፍሮቹን ላከ እነርሱም እየደበደቡ በምድር ላይ እየጎተቱ ወሰዱት ደሙም እንደውሃ ፈሰሰ። ከዚህም በኋላ መኰንኑ ቅዱስ ቶማስን ለአማልክት ስገድ አለው ቅዱሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት "ከእግዚአብሔር ልጅ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ለረከሱ ጣዖታት አልሰግድም ለረከሱ ጣዖታት የሚሰግድ ሁሉ የተረገመ ነውና" አለው።
መኰንኑም ተቆጥቶ እጅግ የበዛና ዕፁብ ድንቅ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው የነዳጅ ድፍድፍን አፍልተው በላዩ በአፉና በአፍንጫው ውስጥ ጨመሩ እንዲህም እያደረጉበት እስከ ብዙ ዘመናት ኖረ የእሊህ ከሀድያን ልባቸው እንደ ድንጊያ የጸና ስለሆነ ቅዱስ ቶማስ ቶሎ እንዲሞት አልፈለጉም። ሌሎች ብዙዎች ሰዎችን ያሰፈሩአቸው ዘንድ የክብር ባለቤት ክርስቶስንም ይክዱት ዘንድ የሥቃዩን ዘመን አስረዘሙ እንጂ። እርሱ የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችንና በአምላካችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል የጸና ነውና፤ ማሠቃየቱ አድክሟቸው ከሀድያን በተቸነፉ ጊዜ ስለ ስሕተታቸውም ይዘልፋቸው ስለነበር ስለዚህ በጨለማ ቦታ ጣሉት በዚያም ሃያ ሁለት ዓመት ኖረ። ከሀድያንም በየዓመቱ ወደ እርሱ ገብተው ከሕዋሳቱ አንዱን ይቆርጣሉ። በዚያም ቦታ አፍንጫውን፥ ከንፈሮቹን፥ ጆሮዎቹን፥ እጆቹንና እግሮቹን ቆረጡ መንጋዎቹም ያረፈ መስሏቸው በየዓመቱ መታሰቢያውን ሲያደርጉ ኖሩ። ነገር ግን እንዲት ክርስቲያናዊት ሴት በጣሉት ጊዜ ስለአየችው ቦታውን ታውቅ ነበር እርሷ በሌሊት ወደ እርሱ ተሠውራ በመሔድ ትመግበዋለች። ጻድቅ ቈስጠንጢኖስም እስከ ነገሠና የቀናች የክርስቶስን ሃይማኖት ክብር እስከ ገለጠ ድረስ እንዲህ ሲሠቃይ ኖረ።
ይህም ንጉሥ ክርስቶስን በመታመን የታሠሩ እሥረኞችን ሁሉ በሀገሮች ሁሉ በወህኒ ቤት ያሉትን ይፈቷቸው ዘንድ አዘዘ። ይችም ሴት ሄዳ ስለ ቅዱስ ቶማስ ከእርሱ የሆነውን ሃያ ሁለት ዓመት ተጥሎ እንደኖረ ለካህናቱ ነገረቻቸው በውስጡ ወደሚኖርበትም ቦታ መራቻ ቸው ። እነርሱም አንሥተው ተሸከሙት እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ ቤተክርስቲያን አደረሱት በቤተ መቅደሱም ፊት ለፊት በወንበሩ ላይ አስቀመጡት ምእመናንም ሁሉ ወደርሱ እየመጡ ከእርሱ ይባረኩና የተቈረጡ ሕዋሳቱን ይሳለሙ ነበር። ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም የከበሩ የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ኤጲስቆጶሳትን የአንድነት ጉባኤን በኒቅያ አገር በሰበሰበ ጊዜ ይህ የከበረ ቶማስ ከእሳቸው አንዱ ነው። ንጉሡም ወደ እነርሱ ገብቶ ሰላምታ ሰጣቸውና ከእርሳቸውም ቡራኬ ተቀበለ። የዚህ የቅዱስ ቶማስን ተጋድሎውን በነገሩት ጊዜ ወደርሱ ቀርቦ ሰገደለት ሕዋሳቱም ከተቈረጡበት ላይ ተሳለመው አዝኖና እጅግም አድንቆ ሕዋሳቱን ዳሠሠው ፊቱንና ዐይኖቹን አሻሸው። ከሀዲ አርዮስንም ተከራክረው ከረቱ በኋላ አውግዘው ለይተው ከወገኖቹ ጋር ከቤተ ክርስቲያን አሳደዱት። ከዚህም በኋላ መንፈስ ቅዱስ እንደአስተማራቸውና እንደመራቸው የሃይማኖትን ትምህርት በአንደበታቸው ተናገሩ ሕግና ሥርዓትን ሥጋዊና መንፈሳዊ ፍርድንም ሠሩ። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ቶማስ ወደ መንበረ ሢመቱ ሔደ ካህናቱንና መንጋዎቹን ሁሉ ሰብስቦ አነበበላቸው እርሱንም እንዲአስተውሉት እንዲጠብቁትም በመጠበቅም እንዲጸኑ አዘዛቸው። ጥቂት ዘመናትም ከኖረ በኋላ በሰላም በፍቅር አረፈ የሹመቱም ዘመን አርባ ዓመት ነው በዚህም እግዚአብሔርን አገለገለው።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛ ንም በዚህ ተጋዳይ አባት ጸሎት ይማ ረን።በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ዳግመኛም በዚህች ቀን ታላቅ የከበረ ሐዲስ ሐዋርያ የትሩፋትም መምህር የሆነ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ዐረፈ።
ዳግመኛም በዚህች ቀን ኢትዮጵያዊት የሆነች ተጋዳይ የከበረች ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው ዳግመኛም የአብርሃም የይስሐቅ የያዕቆብም መታሰቢያቸው ነው።
የኒህ ቅዱሳን በረከታቸው ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።
አሜን።
"ጽዮንን የሚወዳት አይደክምም"
ቅዱስ ያሬድ
511 viewsውሉደ ያሬድ ሰንበት ትምህርት ቤት, 02:45