2023-01-11 19:05:25
ልከውኛል ወይስ ልኮኛል?
በአላህ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ እጅግ በጣም አዛኝ በሆነው፡፡
4፥171 *”እናንተ የመጽሐፉ ሰዎች ሆይ! በሃይማኖታችሁ ወሰንን አትለፉ፡፡ በአላህም ላይ እውነትን እንጅ አትናገሩ”*፡፡ .. *”«ሦስት ናቸው» አትበሉም”*፡፡ ተከልከሉ፤ ለእናንተ የተሻለ ይኾናልና፡፡ *”አላህ አንድ አምላክ ብቻ ነው”*፡፡ يَٰٓأَهْلَ ٱلْكِتَٰبِ لَا تَغْلُوا۟ فِى دِينِكُمْ وَلَا تَقُولُوا۟ عَلَى ٱللَّهِ إِلَّا ٱلْحَقَّ ۚ إِنَّمَا ٱلْمَسِيحُ عِيسَى ٱبْنُ مَرْيَمَ رَسُولُ ٱللَّهِ وَكَلِمَتُهُۥٓ أَلْقَىٰهَآ إِلَىٰ مَرْيَمَ وَرُوحٌۭ مِّنْهُ ۖ فَـَٔامِنُوا۟ بِٱللَّهِ وَرُسُلِهِۦ ۖ وَلَا تَقُولُوا۟ ثَلَٰثَةٌ ۚ ٱنتَهُوا۟ خَيْرًۭا لَّكُمْ ۚ إِنَّمَا ٱللَّهُ إِلَٰهٌۭ وَٰحِدٌۭ ۖ سُبْحَٰنَهُۥٓ أَن يَكُونَ لَهُۥ وَلَدٌۭ ۘ لَّهُۥ مَا فِى ٱلسَّمَٰوَٰتِ وَمَا فِى ٱلْأَرْضِ ۗ وَكَفَىٰ بِٱللَّهِ وَكِيلًۭا
የሥላሴ አማንያን ከባይብል የሥላሴ እሳቤ ለማግኘት የማይቆፍሩት ጉድጓድ፣ የማይፈነቅሉት ድንጋይ፣ የማይደረምሱት መሬት የለም። በተለይ የሥላሴ ሽታው እንኳን ከማይሸተው ከብሉይ ኪዳን ፍንጭ ለማግኘት ሲዳዱ ማየት ፈገግ ያሰኛል። የብሉይ ኪዳን ቀዳማይ ተዳራሲያን አይሁዳውያን እንጂ ክርስቲያኖች አይደሉም። ክርስቲያኖች ደኃራይ ተዳራሲያን እንደመሆናችሁ መጠን አይሁዳውያን ከሙሴ ጀምሮ ሥላሴ የሚባል አምላክ ሰብከው እንደማያውቁ ከባለቤቶቹ ቀረብ ብሎ መጠየቅ ነው። እስቲ ለዛሬ ሥላሴን ያሳያል ብለው ድምዳሜ ላይ አደረሰን ከሚሏቸው ጥቅሶች አንዱ እንይ፦
ኢሳይያስ 48፥16 ወደ እኔ ቅረቡ ይህንም ስሙ፤ እኔ ከጥንት ጀምሬ በስውር አልተናገርሁም፤ ከሆነበት ዘመን ጀምሮ እኔ በዚያ ነበርሁ፥ አሁንም *"አዶናይ ያህዌህ በመንፈሱ ልኮኛል"*። NET Bible
ዕብራይስጥ ማሶሬቲክ፦
אֲדֹנָי יְהוִה שְׁלָחַנִי--וְרוּחו
ግሪክ ሰፕቱጀንት፦
καὶ νῦν Κύριος ἀπέστειλέ με καὶ τὸ πνεῦμα αὐτοῦ.
የዕብራይስጡ ማሶሬቲክ እና ግሪክ ሰፕቱጀንት(LXX)፦ "አዶናይ ያህዌህ በመንፈሱ ልኮኛል" ብለው አስቀምጠውት ሳለ ሥላሴአውያን፦ "አዶናይ ያህዌህ እና መንፈሱ ልከውኛል" በማለት ሥላሴ ለመስራት ሞክረዋል።
"ሠላሐኒ" שְׁלָחַ֖נִי ማለት "ልኮኛል" ነው እንጂ "ልከውኛል" ማለት አይደለም። "ሠላሐ" שְׁלָחַ֖ ማለት "ላከ" ማለት ሲሆን ነጠላ ግስ ነው፥ ይህ ግስ በተመሳሳይ ነቢያት "ላከኝ" ላሉበት ግስ የተጠቀሙት ይህንን ግስ ነው፦
ዘፍጥረት 45፥5 አሁንም ወደዚህ ስለ ሸጣችሁኝ አትዘኑ፥ አትቈርቈሩም፤ እግዚአብሔር ሕይወትን ለማዳን ከእናንተ በፊት *"ልኮኛልና"* שְׁלָחַ֖נִי ።
2 ነገሥት 2፥2 ኤልያስም ኤልሳዕን፦ ያህዌህ ወደ ቤቴል *"ልኮኛልና"* שְׁלָחַ֖נִי በዚህ ቆይ፡ አለው።
ኤርምያስ 26፥12 ኤርምያስም ለአለቆችና ለሕዝቡ ሁሉ እንዲህ ብሎ ተናገረ፦ በሰማችሁት ቃል ሁሉ በዚህች ቤትና በዚህች ከተማ ላይ ትንቢት እናገር ዘንድ ያህዌህ *"ልኮኛልና"* שְׁלָחַ֖נִי ።
ብሉይ ላይ "ሠላሐኒ" שְׁלָחַ֖נִי የሚለው ቃል 26 ቦታ አለ፥ ሁሉም ጋር "ልኮኛል" ለማለት እንጂ "ልከውኛል" ለማለት በፍጹም አልተጠቀሙበት። ኢሳይያስ ላይ ግን የሥላሴ አማንያን ትርጉም ላይ ሆን ብለው የሥላሴን እሳቤ ለማዳበር የጨመሯት ነው። የላከ ለሚለው ነጠላ ቃል ብዜት "ላኩ" ነው፥ "ላኩ" ደግሞ "ሣላሁ" שָׁלְח֖וּ ነው፦
ኤርምያስ 14፥3 ታላላቆችም ብላቴኖቻቸውን ወደ ውኃ *"ላኩ"* שָׁלְח֖וּ ።
ኢሳይያስ "ልከውኛል" ለማለት ቢፈልግ ኖሮ "ሣላሁኒ" שָׁלְח֖וּנִי ይል ነበር፥ ቅሉ ግን አላለም። የያህዌህ መንፈሱ ከአፉ እና ከአፍንጫው የሚወጣ እስትንፋ ነው፦
ዘጸአት 15፥8 *”በአፍንጫህ እስትንፋስ”* ውኆች ተከመሩ፥ ፈሳሾችም እንደ ክምር ቆሙ፤ ሞገዱም በባሕር ውስጥ ረጋ፡፡
መዝሙር 33፥6 በእግዚአብሔር ቃል ሰማዮች ጸኑ፥ ሠራዊታቸውም ሁሉ *”በአፉ እስትንፋስ”*።
የያህዌህ እስትንፋስ ከያህዌህ በተለይ መልኩ እንደ ያህዌህ እራሱ የቻለ ማንነት"person" ከሆነ እርሱ ማን ነው? ያህዌህስ ከራሱ አፍ እና አፍንጫ ተሸንሽኖ የሚወጣ ሌላ ማንነት ካለው ያህዌህ አንድ ነው ከሚለው ትምህርት ጋር ይጣረሳል። ሲቀጥል አፍንጭ እና አፍ ሁለት ስለሆኑ ሁለት እስትንፋሶች ከወጡ በኃላ ተገጣጥመው ነው ወይስ ተለያይተው ነው ማንነት የሚሆኑት?
ሢሰልስ ኢሳይያስን የያህዌህ እስትንፋስ አላከውም፥ ግን ላከው ቢባል የሚያስደንቅ አይደለም። ምክንያቱም ከያህዌህ አፍ የምትወጣ ጥበብ ትልካለች፦
ምሳሌ 9፥1 *"ጥበብ ቤትዋን ሠራች"*፥ ሰባቱንም ምሰሶችዋን አቆመች።
ምሳሌ 9 3፤ *"ባሪያዎችዋን ልካ"* በከተማይቱ ከፍተኛ ስፍራ ላይ ጠራች።
ሉቃስ 11፥49 ስለዚህ ደግሞ *የእግዚአብሔር ጥበብ* እንዲህ አለች፦ ወደ እነርሱ ነቢያትንና ሐዋርያትን *እልካለሁ*፥ ከእነርሱም ይገድላሉ ያሳድዱማል፥
ያህዌህ መልእክቱን ለነቢያት የሚያስተላልፈው በመንፈሱ ነው፦
ዘካርያስ7፥12 የሠራዊትም ጌታ ያህዌህ *"በቀደሙት ነቢያት እጅ በመንፈሱ የላከውን ሕጉን እና ቃሉን"* እንዳይሰሙ ልባቸውን እንደ አልማዝ አጠነከሩ።
ላኪ ያህዌህ በመንፈሱ ከሆነ የተላከው ማን ነው? የተላከው ኢሳይያስ ነው። ዐውዱ ላይ፦ "ወደ እኔ ቅረቡ ይህንም ስሙ፤ እኔ ከጥንት ጀምሬ በስውር አልተናገርሁም፤ ከሆነበት ዘመን ጀምሮ እኔ በዚያ ነበርሁ" የሚለው ያህዌህ ነው። ከዚያ ኢሳይያስ፦ "አዶናይ ያህዌህ በመንፈሱ ልኮኛል" ይላል። ይህ የተለመደ አነጋገር በኢሳይያስ መጽሐፍ እንይ፦
ኢሳይያስ 50፥3-4 *"ሰማያትን ጥቍረት አለብሳቸዋለሁ፥ መጋረጃቸውንም ማቅ አደርጋለሁ። የደከመውን በቃል እንዴት እንደምደግፍ አውቅ ዘንድ አዶናይ ያህዌህ የተማሩትን ምላስ ሰጥቶኛል፥ ማለዳ ማለዳ ያነቃኛል፥ እንደ ተማሪዎችም ትሰማ ዘንድ ጆሮዬን ያነቃቃል"*።
"ሰማያትን ጥቍረት አለብሳቸዋለሁ፥ መጋረጃቸውንም ማቅ አደርጋለሁ" የሚለው ያህዌህ ሆኖ ሳለ እዛው ዐውድ ላይ፦ "የደከመውን በቃል እንዴት እንደምደግፍ አውቅ ዘንድ አዶናይ ያህዌህ የተማሩትን ምላስ ሰጥቶኛል፥ ማለዳ ማለዳ ያነቃኛል፥ እንደ ተማሪዎችም ትሰማ ዘንድ ጆሮዬን ያነቃቃል" የሚለው ኢሳይያስ ነው። መቼም፦ "አንዱ ያህዌህ ለሌላው ያህዌህ የተማረ ምላስ ሰጥቷል፣ ማለዳ ማለዳ ያነቃዋል፣ ጆሮውን ያነቃቃዋል" የሚል ቂል ያለ አይመስለኝም። ስለዚህ ከላይ ያለውን ጥቅስ በዚህ ስሌት ተረዱት። የሚያጅበው እኮ ኣ “አዶናይ” אֲדֹנָ֥י ማለት "ጌታዬ" ማለት ከሆነ ኢሳይያስ 48፥16 እና 50፥4 ላይ "ጌታዬ" የሚለው ኢሳይያስ እንጂ ሌላ ማንም አይደለም። ሲቀጥል “አዶኒም” אֲדֹנִ֣ים የብዙ ቁጥር ሆኖ ሲመጣ "ጌቶች" ማለት ከሆነ ሥላሴን ያሳያል ካላችሁ እንግዲያውስ መንፈሱ እና የተላከው ከሥላሴ ውጪ ነው። ቅሉ ግን "ጌታዬ" ያህዌህ ልኮኛል የሚለው ኢሳይያስ ሲሆን ላኪው ደግሞ ያህዌህ በመንፈሱ ነው።
ከወንድም ወሒድ ዑመር
317 views16:05