2021-02-14 17:17:02
የስራ ስምሪት አሰራርን ታሳቢ ያደረገ ዘመናዊ የስራ ፈላጊዎችና የስራ ሁኔታ ምዝገባ ስርዓት ሊዘረጋ መሆኑን የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ።
የክልል ቢሮዎችም ይህን ታሳቢ አድርገው እንዲሰሩ ጠይቋል።
ዝቅተኛ የደሞዝ መጠንን ለመወሰን የሚያስችል መመሪያ እየተዘጋጀ መሆኑንና የክልል ቢሮዎች በውጭ አገርም ሆነ በአገር ውስጥ እየሰሩ ያሉትን ሰራተኞች መብት ለማስጠበቅ ሊተጉ እንደሚገባም ተገልጿል።
ለሁለት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሴክተር የ2013 በጀት ዓመት የስድስት ወር እቅድ አፈፃፀም የጋራ መድረክ ትናንት ተጠናቋል።
በመድረኩ የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ እንዳሉት ሚኒስቴሩ የስራ ስምሪትንና የስራ ገበያ መረጃን ዘመናዊ ለማድረግ እየሰራ ነው።
ለዚህም ይረዳ ዘንድ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል።
የስራ ገበያ መረጃ በአገሪቱ ያለውን የስራ ሁኔታና የስራ ፈላጊዎችን መረጃ ማደራጀት መሆኑን ገልፀው፤ በአሁን ወቅት የስራ ፈላጊዎች መረጃ በወረቀት እየተመዘገበ እንደሆነ ተናግረዋል።
ይህንን ተግባር ዲጂታል ለማድረግ ሚኒስቴሩ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ስራውን ለማገዝ የክልል ቢሮዎች የስራ ፈላጊዎችን መረጃ በአግባቡ መያዝ እንዳለባቸው አስረድተዋል።
ለውጭ አገር ዜጎች የስራ ፈቃድ ከመስጠት ባሻገር በተፈቀደላቸው አግባብ ብቻ እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ለማጣራት እየተሰራ ነውም ብለዋል።
በሂደቱ ያለአግባብ ሲሰሩ የተገኙ መኖራቸውን ጠቁመው ክልሎችም ፈቃድ መስጠት ብቻ ሳይሆን የቁጥጥር ስራን አጠናክረው እንዲቀጥሉ አሳስበዋል።
ዝቅተኛ የደሞዝ መጠንን ለመወሰን የሚያስችል መመሪያ እየተዘጋጀ መሆኑንና የክልል ቢሮዎች በውጭ አገር የሚሰሩትንም ሆነ በአገር ውስጥ እየሰሩ ያሉትን ሰራተኞችን መብት ለማስጠበቅ ሊተጉ ይገባል ብለዋል።
የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ አደረጃጀት በሁሉም ክልል ወጥ እንዲሆን ለማድረግ ክልሎች መስራት እንዳለባቸውና ሚኒስቴሩም እገዛ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።
በጋራ ምክክር መድረኩ ከሴክተር እቅድ በተጨማሪ የሚኒስቴሩና የክልል ቢሮዎች የ2013 በጀት ዓመት የመጀመሪያ መንፈቅ ዓመት እቅድ አፈፃፀም ቀርቧል።
በመድረኩም ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የባለድርሻ አካላትና የክልል ሰራተኛና ማህበራዊ ቢሮ ኃላፊዎችና ተወካዮች መገኘታቸውን ከኢዜአ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
FBC
5.2K viewsአብርኆት 2021, 14:17