2022-08-28 06:21:44
ተላላፊ በሽታ
«እርስ በርስ በቅንነት ከመዋደድ የበለጠ ምንም ነገር ነፍስን ከፍ ሊያደርጋትና ብዙ ደስታን ሊሰጥ የሚችል ነገር የለም።»
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)
ዓለም ሁለት ነገሮችን አጣምሮ የያዘ እምነትን ትፈልጋለች፡፡ በአስደንጋጭ ነገሮች የማይናወጥ መለኮታዊ እውነት እና ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ የሆነ የሕይወት ለውጥ ለማምጣት ሁልጊዜ የሚሠራ ኃይል ናቸው። ማንም ቢሆን የሚፈልገው ይህንኑ ይመስለኛል። እውነት የእምነት መሠረት ሲሆን፤ ያመነውን ተግባራዊ በሆኑ መንገዶች የምንኖርበት ኃይል ደግሞ ፍቅር ነው፡፡ እንድንወድ የማያስችል ሃይማኖት ገዳይ አስገዳይ ነው፡፡ ከፍቅር የተለየ ክርስትና ሰማያዊ እውቅና አይኖረውም፡፡ አምላካችን ታላቅ፣ ወሰን የለሽ፣ ሁሉን አዋቂ እና ሁሉን የሚችል የጸጋ አምላክ ነው፡፡ በእርግጥም እግዚአብሔር ተግባራዊ በሆኑ መንገዶች እንድንወድ ኃይል ይሰጠናል። ለስም አጠራሩ ክብር ይግባው!
የፍቅር ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ፡-
«እኛ ወንድሞችን የምንወድ ስለ ሆንን ከሞት ወደ ሕይወት እንደ ተሻገርን እናውቃለን፤ ወንድሙን የማይወድ በሞት ይኖራል።» ይለናል፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ፡-
«ፍቅር ከሌለው ሁሉም ነገር ርኩስ ነው። አንድ ሰው ድንግልናውን ቢጠብቅ፣ ቢፆም ወይም በትጋት ቢጸልይ ወይም ለድሆች ቢመጸውት . . . አብያተ ክርስቲያናትን ቢያሠራ ወይም ሌላ መልካም ነገር ቢያደርግ ይህ ሁሉ ያለ ፍቅር በእግዚአብሔር ዘንድ አይቆጠርም። ምክንያቱም በእግዚአብሔር የማይፈለግ ነውና። ስለዚህ ያለ ፍቅር ምንም ነገር አታድርጉ፡፡» ይላል፡፡
ተወዳጆች፤ ፍቅር ዳግመኛ የመወለዳችን ማለትም ክርስቲያን የመሆናችን ማስረጃ ነው፡፡ «እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፥ ደቀ መዛሙርቴ እንደ ሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ።» (ዮሐ. 13፥35) ተብሎ እንደ ተጻፈ፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መከተላችን በተግባራዊ ሁኔታ የሚገለጠው ፍቅር ሲኖረን ነው፡፡ ፍቅር ግን ከሌለን . . . .
ቅዱስ ባስልዮስ፡-
«ባልንጀራን መውደድ ጠባዩ ምንድን ነው? የራስዎን ጥቅም ሳይሆን የሚወዱትን ሰው መንፈሳዊ እና አካላዊ ደኅንነት መፈለግ ነው። ባልንጀራውን የሚወድ ፍቅሩን ለእግዚአብሔር ይገልጣል፡፡» ይላል፡፡
መጽሐፍ ቅዱስ ቅድስናን እና ለሌሎች የሚኖረንን ፍቅር በፍርድ ቀን ከመዳን እና ካለ መዳን ጋር ያያይዘዋል /ዕብ. 12፥14፤ ገላ. 5፥21፤ 1 ቆሮ. 6፥10/፡፡ ፍቅር የእምነት እውነታ ማረጋገጫ ነው፡፡ በእግዚአብሔር የተስፋ ቃሎች ላይ ያለን እምነት፤ ሰዎችን በመውደድ/ ባለ መውደዳችን ይፈተናል፡፡ ከክርስቶስ ጋር አንድ የሚያደርገን እና ኃይሉን የምንቀበልበት መንገድ እውነተኛ ፍቅር ነው። በምናየው ሰው በኩል የማይታየውን እግዚአብሔር የምናገኘው ሌሎችን በመውደድ ነው፡፡
ቅዱስ አግናጤዎስ፡-
«በዕድሜ፣ በጾታ፣ በደረጃ ልዩነት ሳትፈጥሩ፤ ለባልንጀሮቻችሁ ቅዱስ ፍቅር አሳዩ፡፡»
ተወዳጆች ሆይ ፤ ራሳችንን እንመርምር፡፡ እግዚአብሔር በሌሎች ምን ያህል ተወዳችኋል? ብሎ አይጠይቀንም፡፡ ነገር ግን ምን ያህል ለሌሎች ፍቅር ሰጥታችኋል? ብሎ ይጠይቀናል፡፡ ከሌሎች ምን ያህል እንደ ተቀበልን ሳይሆን እንዴት ለሌሎች በረከት እንደሆንን ይጠይቀናል፡፡ አምላካችን ስለ ሌሎች ስህተት አይጠይቀንም፤ ነገር ግን እነሱን ከስህተት ለመመለስ ስላደረግነው ጥረት ይጠይቀናል፡፡ ምን ያህል እንደ ተጠላን ሳይሆን ምን ያህል እንደ ወደድን፤ ምን ያህል እንደ ተገፋን ሳይሆን ምን ያህል እንዳቀረብን፤ ምን ያህል እንደ ተበደልን ሳይሆን ምን ያህል ይቅር እንዳልን፤ ምን ያህል እንደ ተፈተንን ሳይሆን ምን ያህል እንደ ታገሥን . . . . ይጠይቀናል፡፡ በእውነት ራሳችንን የት እንዳለን እንመልከት፡፡
እኛን እንዲሁም ሌሎችን ሊበክሉና ሊጎዱ የሚችሉ ተላላፊ በሽታዎች ሁለት አይነት ናቸው፡፡ አንዱ አይነት ሰውን ከውስጥ ሊጎዳ የሚችል ሲሆን፤ ነገር ግን ሌሎችን አይጎዳም፡፡ ሌላው አይነት ግን እኛን በመጉዳት ብቻ አይቆምም፤ ሌሎችንም ይበክላል። በአገራችን ሰው ብዙ ትኩረት ያልሰጠው ማስክና ሳኒታይዘር፤ ክትባትና ኦክስጅን የማያሽለው፤ መራራቅና አለመጨባበጥ የሚያባብሰው «ጥላቻ» የሚባል ተላላፊ በሽታ ተስፋፍቷል፡፡
እንደ ጥላቻና በቀል የመሳሰሉ ተላላፊ በሽታዎች ይኖሩብን ይሆን? ከእኛ አልፈው በሌሎች ጆሮ ውስጥ የምናፈሳቸው የተሳሳቱ አሳቦች ይኖሩን ይሆን? በራሳችን ድክመቶች ተይዘን፤ ነገር ግን ሸክማችንን በሌሎች ላይ እየጫንን ይሆን? በመውደቅ ተጠላልፈን፤ ነገር ግን ለሌሎች ማሰናከያ ሆነን ይሆን? ጥላቻችን ብዙዎችን እየበከለ፤ እየገደለ ይሆንን??
@Nolawiiher
@Nolawiiher
«ፍቅርን ተከታተሉ፥» /1 ቆሮ. 14፥1/!!
1.3K views Estifanos, 03:21