2023-04-02 18:30:37
ኒቆዲሞስሰው ሥልጣን ቢኖረው ዕውቀት ሊጎድለው እንዲሁም ሀብት ላይኖረው ይችላል፡፡ ዕውቀት ቢኖረው ደግሞ ሀብትና ሥልጣን ማካበት ያዳግተዋል፡፡ ሀብት ቢኖረውም እንኳን ዕውቀት ይጎድለዋል፤ ሥልጣንም አይኖረውም፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ሦስቱንም አንድ ላይ አስተባብሮ የያዘ የአይሁድ አለቃ ነበር፡፡
ከፈሪሳዊያን ወገን የሆነው ኒቆዲሞስ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ስብከቱ ያስተማረውን ወንጌልን ለመማር ከአይሁድ ሁሉ ቀድሞ በሌሊት ወደ ጌታችን ይሄድ ነበር፡፡ ፈሪሳውያን ማመን በተሳናቸው በዚያን ጊዜ ጆሮውን ለቃለ እግዚአብሔር፣ ልቡን ለእምነት የከፈተ ሰው ነው፡፡
እናውቃለን በማለት የሚመካኙ በርካታ ሰዎች ከመልካም ነገር ሲከለከሉ እርሱ ግን “ዐዋቂ ሳለ ራሱን ዝቅ አድርጎ፣ እምነት በማጣት የነጠፈችውን የፈሪሳውያንን ኅብረት ጥሎ፣ ሐዋርያትን መስሎ ጌታውን አግኝቶታል፡፡” ቀርቦም እንዲህ አለው፤ ‹‹መምህር ሆይ፥ ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን፤ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ይህን ተአምር ሊያደርግ የሚችል የለምና፡፡›› ጌታችን ኢየሱስም መልሶ ‹‹እውነት እውነት እልሀለሁ፤ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም›› አለው፡፡
ነገር ግን ኒቆዲሞስ ምሥጢሩ ስላልተገለጠለት ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?›› በማለት ጌታን መልሶ ጠየቀው፡፡ ጌታችንም እንዲህ ብሎ መለሰለት፤ ‹‹እውነት እውነት እልሀለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስ የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡››
አሁንም ግን ኒቆዲሞስ ምሥጢሩ አልተገለጠለትም ነበርና ‹‹ይህ ሊሆን እንዴት ይቻላል?›› በማለትም ጌታን ጠየቀው፡፡ ጌታችንም ‹‹አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ፤ ነገር ግን እንዴት ይህን አታውቅም? በምድር ያለውን ስንነግራችሁ ካላመናችሁኝ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፤ እርሱም በሰማይ የሚኖረው ነው፡፡ ሙሴ በምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀል ዘንድ አለው፡፡ ያመነበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ እንዲኖር እንጂ እንዲጠፋ አይደለም…›› በማለት አስረድቶታል፡፡ (ዮሐ.፫፥፪-፲፭)
የዓለም መድኃኒት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት በዚያች ሰዓት፣ ሐዋርያት በተበተኑባትና አይሁድ በሠለጠኑባት ጊዜ እንኳን ከጌታችን ሳይል በድፍረት ከእግረ መስቀሉ የተገኘ እንዲሁም ቅዱስ ሥጋውን በድርብ በፍታ ገንዞ የቀበረ ሰው ኒቆዲሞስ ነው፤ ስለዚህም ሰባተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት በእርሱ ስም ተሰይሟል፡፡
ለኒቆዲሞስ ምሥጢሩን ገልጾ ያዳነውና ያከበረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኛም ምሥጢሩን ይገልጽልን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፤ አሜን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
4.7K views15:30