2022-10-30 22:25:18
"እንዘ ተሐቅፊዮ"
ቅዳሜ ጥቅምት 26 ከቀኑ 10 ሰዓት ጀምሮ በምሥራቀ ፀሐይ ቀበና መድኀኔ ዓለም አይቀርም።
"እንዘ ተሐቅፊዮ" የእመቤታችን ታላቁ ጉባኤ የሥዕለ ቅድስት ድንግል ማርያም ምስለ ፍቁር ወልዳ አገባብ
ቅዳሜ ጥቅምት 26 ከ10 ሰዓት ጀምሮ ረጅም ምንጣፍ ይነጠፋል፣ ዘመነ ጽጌ ነውና 10 ሺሕ አበባ ይጎዘጎዝበታል፡፡ ሊቁ አባ ጽጌ ድንግል በማሕሌተ ጽጌ መጽሐፉ "እንዘ ትነጽፍ ዘርቤታተ ወትነሰንስ መጽርየ። ለክብረ ሥዕልኪ ድንግል ትሰግድ ነፍስየ" (ምንጣፍን እያነጠፈች ሽቱንም እየረጨች ድንግል ሆይ ሰውነቴ ትሰግዳለች) እንዳለ።
ሠረገላተ አሚናዳብ የተባለች የእመቤታችን ሥዕል በፈረስ በሚሄድ ሠረገላ ላይ ሥዕለ ማርያምን በአባቶች ካህናት ተይዛ ትገባለች፡፡
ከሠረገላዋ ጀርባ በ7ቱ የመቅረዝ መብራቶች አምሳል 7 ጡሩንባ የሚነፉ ይቆማሉ፡፡
ከነርሱ ቀጥለው ንጽሕናዋን በጻፉ ማስተማሩ ቀደምት ሊቃውንት አምሳል ሊቃውንት "እንዘ ተሐቅፊዮ" እየዘመሩ ይከተሏታል፡፡
እመቤታችን በእናትና አባቷ ቤት በነበረችበት 3 ዓመት ልክ 3 የካቴድራሉ ካህናት በፊቷ በቀኝና በግራዋ ማዕጠንት ይዘው ያጅቧታል፡፡
ቤተ መቅደስ በነበረችበት 12 ዓመት ልክ 6 ችቦ በቀኝ 6 ችቦ በግራ የሚይዙ ይመደባሉ፡፡
ቅዱስ ገብርኤል በውሃ ዳር፣ በቤተ ዮሴፍ፣ በቤተ መቅደስ 3 ጊዜ ባበሠራት አምሳል 3 ዲያቆናት ከሠረገላው ፊት 3 የመጾር መስቀል ከፍ አድርገው ይዘው ይመራሉ፡፡
ከዲያቆናቱ ፊት በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና ንጽሕት ናትና 3 ነጋሪት የሚጎስሙ ይኖራሉ፡፡
ትውልደ ሴም፣ ትውልደ ካም፣ ትውልደ ያፌት ከፍ ባለ ድምፅ እስከ ፍጻሜ ዓለም ቅድስናዋን የሚመሰክሩ ናቸውና ከነጋሪቶቹ በኋላ 3ት መለከት የሚነፉ አሉ፡፡
ከቀንደ መለከቱ ፊት ዘካርያስ ለእመቤታችን በሚያቀርብላት አበባ አምሳል 3 ነጫጭ የሀገር ባሕል ልብስ የለበሱ ሕፃናት ሴቶች በንጹሕ ዕቃ የተያዘ አበባ እየበተኑላት ይሄዳሉ፡፡
ከሕፃናቱ ፊት በትውልድ ዘይተርፍ አምሳል የካቴድራሉ ሰ/ት/ቤት ዝማሬን እያቀረቡ ይመራሉ፡፡ ከእነርሱ ፊት ረጃጅም ቅዱሳት ሥዕላትን በመያዝ ከፊት ከፊት ይመራሉ፡፡
ዐውደ ምሕረቱ ላይ እንደደረሰች ከሠረገላው ላይ በክብር ወርዳ 1 ጊዜ ቤተ ክርስቲያኑን ዑደት ታደርጋለች፡፡
በዐውደ ምሕረቱ ላይ በከበረ ባመረ በቀንቆጠቆጠ መቀመጫ ላይ በክብር ትቀመጣለች፡፡
ምስለ ፍቁር ወልዳ ከበር ዐውደ ምሕረቱ ድረስ እስክትደርስ ድረስ ዝማሬ በዘማርያን በደመቀ መልኩ እየተሰጠ ይቆያል፡፡
1150 የእመቤታችን አምሳላት የሚኾኑ የአበቦች ምስጢር ይመሰጠራል።
የእመቤታችን ወዳጆቿ ብቻ ከጉባኤው አይቀሩም።
["ኦ ርኅርኅተ ሕሊና ዘሕገ ልማዳ ምሕረት ለኩሉ ፍጥረት፤ ንሳለማ ንዑ ለሥዕለ ማርያም ቡርክት"]
(ለፍጥረት ኹሉ የሕጓ ልማድ መራራት የኾነች ሕሊናዋ የምትራራ የቡርክት ማርያምን ሥዕል እንሳለማት ዘንድ ኑ) (መልክአ ሥዕል)
በነጋታው ጥቅምት 27 ታቦተ መድኀኔ ዓለም ወጥቶ በታላቅ ድምቀት በዓሉን አክብረን ታላቅ በረከት እናገኛለን
የቤተ ክርስቲያኑ አድራሻ ከ4 ኪሎ ወደ ቀበና አደባባይ ሲመጡ ማደያው ጋር ከመድረሶት በፊት።
5.4K views19:25