2023-04-13 06:40:27
[ሕጽበተ እግር በሊቃውንት]
በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ (በድጋሚ የተፓሰተ)
በዕለተ ዐርብ የዓለምን ኀጢአት በደሙ የሚያጥበው ከጎኑ በሚፈሰው ውሃ ዓለምን የሚቀድሰው ጌታችን አስቀድሞ በዕለተ ኀሙስ የደቀ መዛሙርቱን እግር በውሃ በማጠብ ትሕትናን የገለጸበት አስደናቂ ምስጢር የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በመገረም እንዲኽ ብለዋል፡-
ያዕቆብ ዘሥሩግ እንዲኽ አለ፡-
“በመንክር ትሕትና ወረደ እግዚአብሔር ቃል…” (እግዚአብሔር ቃል በሚያስደንቅ ትሕትና ሰው ኾነ፤ የማይታዩ ረቂቃን መላእክት አደነቁ በልዑል ዙፋኑ ለደቀ መዛርቱ ሲያገለግል ባዩት ጊዜ አገልጋዮች መላእክት ደነገጡ፤ ትሕትና ወደ አለበት ፍቅር የአሕዛብን እግረ ልቡና ያቀና ዘንድ ግሩም እሳት በትሕትና መገለጡን ባዩ ጊዜ ብርሃናት ደነገጡ፤ አገልጋይ ይኾን ዘንድ እዚኽ ዓለም ከመጣ ከወልድ የተነሣ የአባቱ አገልጋዮች መላእክት እጅግ አደነቁ።
በመለኮቱ ግን ማገልገል የለበትም፤ በወገቡ የታጠቀውን ማድረቂያ አይተው መላእክት አደነቁ፤ ስሙ ከፀሓይና ከጨረቃ በፊት የነበረ ርሱ አገልጋይ ኾነ፤ ሕያው ጌታን ሱራፌል ያመሰግኑታል፤ ቦታውን ግን አያውቁም፤ ሱራፌልን የፈጠረ ርሱ በራት ጊዜ ወገቡን ዘርፍ ባለው ዝናር ታጠቀ፤ እንዳያቃጥል በመፍራት የማይታይ እሳት ለሐዋርያት አገልጋይ ኾኖ አብነት ይኾናቸው ዘንድ የትሕትና ሥራን የሚሠራበትን ውሃ በኩስኩስት ቀዳ የደቀ መዛሙርቱን አለቃ ጴጥሮስንም እግሩን ሊያጥበው ጠራው) (ሃይ. አበው ዘያዕቆብ ዘሥሩግ ክፍል 9)
የቁስጥንጥንያው ፓትሪያርክ የነበረው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ይኽነን አለ፡-
“ልዑለ ባሕርይ የሚኾን ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳ የደቀ መዛሙርቱን እግር ካጠበ፣ ከዚህ በላይ ደግሞ የይሁዳን እግር፥ የሌባውን እግር፥ ከክፋቱ መፈወስ የማይችለውን ሰው ካጠበ፥ ከማዕዱ እንዲካፈል ካደረገ እኛማ እንዴታ? እኛማ እንዴት ይህን ከማድረግ እንከለከላለን? የሠራተኞቻችንን እግር ብናጥብ ምንድነው ክፋቱ? የአሠሪና የሠራተኛ ልዩነት የቃላት ልዩነት ብቻ አይደለምን? እኛስ ሁላችን ዕሩቅ ብእሲዎች ነን፡፡ እርሱ ግን የባሕርይ አምላክ ነው፤ ኾኖም የባሮቹን እግር ዝቅ ብሎ ከማጠብ ምንም አልተጠየፈም፡፡
ለዚህም ነው ‘እኔ ጌታችሁና መምህራችሁ ስኾን እግራችሁን ካጠብኳችሁ፥ እናንተም የወንድማችሁን እግር ልታጥቡ ይገባችኋል’ ያለን፡፡ … ጌታችን እንዲህ ራሱ አድርጐ ካሳየን በኋላ እኛ አናደርግም ብንል በዚያች ቀን የምንመልሰው መልስ ምን ይኾን? … ይህን ከማድረግ ተከልክለን በትዕቢት የምንያዘውስ እኛ ምንድነን? እንደምን ያለ ስንፍናስ ቢይዘን ነው? ሰው ሆይ! በኪሩቤል ላይ የሚቀመጠው እርሱ ዝቅ ብሎ የይሁዳን እግር ካጠበ፥ አፈርና ትቢያ የምትኾን አንተ ራስክን ከፍ ከፍ ታደርጋለህን? ለዚህ ትዕቢትህስ እንደምን ያለ ፍዳ ይጠብቅህ ይኾን? ወዳጄ ሆይ! ከፍ ከፍ ማለትን ትወዳለህን? እንኪያስ ና! እንዴት ከፍ ከፍ እንደምትልም አሳይሃለሁ፡፡ እንደ ጌታህና እንደ መምህርህ እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ራስህን ዝቅ አድርግ፤ የዚያን ጊዜም ከፍ ከፍ ትላለህ” /St. John Chrysostom, Homily LXXI/፡፡
ሊቁ ቅዱስ ያሬድም ይኽነን አለ፡-
“ሐዋርያቲሁ ከበበ
እግረ አርዳኢሁ ሐጸበ
ኮኖሙ አበ ወእመ
ወመሀሮሙ ጥበበ”
(ሐዋርያቱን ሰበሰበ፤ የደቀ መዛሙርቱንም እግር አጠበ፤ እንደ አባትና እናት ኾናቸው የትሕትና ጥበብን አስተማራቸው)፡፡
አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በመጽሐፈ ምስጢር ይኽነን አለ፡-
“ዘያቀንቶሙ ለአድባር በኀይሉ ቀነተ ለንጸ ለተልእኮ…” (ተራሮችን በኀይሉ የሚያስታጥቃቸው ለማገልገል ማበሻ ጨርቅ ታጠቀ፤ የባሕርን ውሃ እንደ አቁማዳ የሚሰበስበው በወንዞች መዝገቦች የሚሾማቸው ርሱ ከወዳጁ ከአልዓዛር ቤት የውሃ ማድጋ አንሥቶ እግሮችን ለማጠብ ያገለግልባት ዘንድ ወደ ኩስኩስት አፈሰሰ፤ እጆቻቸውንና እግሮቻቸውን እንዲታጠቡ የናስ ኩስኩስት ሠርቶ በኦሪቷ ድንኳን ደጃፍ እንዲያኖራት ሙሴን ያዘዘው ውሃውን በኩስኩስት ሞልቶ የደቀ መዛሙርቱን እግር ሊያጥብ ጀመረ)
318ቱ ሊቃውንት በሕንጻ መነኮሳት እንዲኽ አሉን፡-
“ኢትትሐከይ ኀጺበ እግረ አኃው ሶበ መጽኡ ኀቤከ...”
(ወንድሞች ወደ አንተ በመጡ ጊዜ እግራቸውን ማጠብን ቸል አትበል፥ ይህችን ሥራ ቸል የሚልዋትን ስለዚህ ትእዛዝ ሥላሴ በፍዳ ይመረምሯቸዋልና፤ ምንም ኤጲስ ቆጶሳትም እንኳ ቢኾኑ እግዚአብሔር አስቀድሞ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጥቦ እንዲሁ ያደርጉ ዘንድ አዝዟቸዋልና” ብለው አስተምረዋል) (ሃይ.አበ. ዘሠለስቱ ምዕት 20፡29)፡፡
ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ቅዱሳን ሐዋርያትን እግራቸውን ብታጥባቸው በዚኽ በታጠበና በተባረከ ባማረ እግራቸው ዓለምን ዙረው ወንጌልን እንዳስተማሩ የእኛንም እግሮቻችን እንደነሡ የሕይወት ውሃ የሚሰጥባት፤ የዓለምን ኀጢአት ያጠበ ቅዱስ ደምኽ ወደሚቀዳባት፤ ቅዱስ ሥጋኽ ለመድኀኒት ወደሚፈተትባት ወደ ቤትኽ ዘወትር የሚገሠግሡ አድርጋቸው፡፡
ከመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ
የቴሌግራም ቻናል https://t.me/Rodas9
7.4K views03:40