2023-03-02 19:19:43
መልእክት
ስለ ስፖርት ፌዴሬሽኖች በመንግስት የተቀመጠው አቅጣጫ ና ያለውን ሂደት በተመለከተ የቼዝ ቤተሰብ ማወቅና መረዳት ስለሚገባው ቼዝ ፌዴሬሽንን ትኩረት በማድረግ ከዚህ በታች አጠር ያለውን መረጃ ለማድረስ ወደድን።
ስፖርት እያንዳንዱ ሰው ሊደግፈው ፤ ሊያስፋፋው፥ ሊጠቀምበት እንደሚገባ የታወቀ ነው። ለዚህም ነው ስፖርት ከፖለቲካ ውጭ ሆኖ ራሱን ችሎ በህዝብ የሚመራው። የሚያድገውም የሚስፋፋውም የተሻለው አማራጭ ይህ ስለሆነ።
በእስከ አሁኑ ሂደት አብዛኛው ፌዴሬሽኖች በመንግስት ውስጥ ሆነው ግን በህዝብ በተመረጡ እየተመሩ ስራቸውን እያከናወኑ ነበር። ይህ ሂደት ለስፖርት እድገት ብዙም ጠቃሚ ሆኖ ስላልተገኘ መንግስት ሁሉም ፌዴሬሽኖች ራሳቸው ችለው እንዲወጡ አቅጣጫ በማስቀመጥ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ መረዳት ተችለዋል።
የመንግስት አቅጣጫ የሚከተለው ይመስላል
ፌዴሬሽኖች የራሳቸው ሰራተኛ (ባለሙያ) በመቅጠር ራሳቸው ችለው እንዲወጡ አስፈላጊውን ድጋፍ ያደረጋል
መንግስት በጀት ይሰጣል እንዲሁም በልዩ ሁኔታ ያግዛል
ፌዴሬሽኖች እስከሚደራጁ ቢሮም ሆነ ሌሎች ድጋፎች ያደርጋል
ይህ የመንግስት ሂደት ለስፖርት ማህበረሰብ ያልተጠበቀና እጅግ አስደሳች ዜና ነው።
ይህን የመንግስት መልካም መንገድ በመከተል ብዙ ፌዴሬሽኖች ወድያውኑ ራሳችን ችለን እንወጣለን ብለው በመወሰን ለስፖርቱ የሚበጀውን ሂደት በመምረጥ ወደ እንቅስቃሴ ገብተዋል።
የቼዝ ፌዴሬሽን ይህን ወርቃማው እድል በመጠቀም ራሱን ችሎ በመውጣት ስፖርቱን ይታደጋል ታሪክም ይሰራል የሚል የብዙዎች ተስፋና እምነት የነበረ ቢሆንም ባልተጠበቀ ሁኔታ ላለመውጣት መወሰኑን መረዳት ተችለዋል። የተሰጠው ምክንያትም በሂደት አቅም እስከምንፈጥር በመንግስት ላይ መቆየት ይሻላል የሚል ነው።
በእርግጥ መንግስት አስገድዶ አሁን መውጣት አለባቹ ባይልም ውሳኔው ግን ከመንግስት ፖሊሲና አቅጣጫ የማይሄድ ከመሆኑ በተጨማሪ ስፖርቱን በእጅጉ የሚጎዳ አብዛኛው የቼዝ ቤተሰብ ያሳዘነ ውሳኔ ነው።
ሌላው አጠያያቂ የሆነው አቅም እስከምንፈጥር እንቆይ የሚለው ነው።
እኛም እንጠይቃለን
ለቼዝ ፌዴሬሽን ብቻውን መንግስት 3 ሰራተኛ በመመደብ በጀት በመስጠት ቢሮ በመስጠት ስፖርቱ በሚፈለገው ደረጃ አላደገም ከተባለ አሁን 3ቱም ሰራተኛ በተነሱበት ለሁሉም ፌዴሬሽኖች አንድ ላይ በመሰብሰብ ስፖርት ለሁሉም በሚል አደረጃጀት አንድ ፅ/ሀላፊ በአስተባባሪነት በተመደበበት እንዴት ብሎ ነው ቼዝ ፌዴሬሽን አቅም የሚፈጥረው?
የአሁኑ ሂደት ከበፊቱ በምን ሁኔታ ነው አቅም ለመፍጠር የሚያግዘው?
የመንግስት ፖሊስና አቅጣጫ ባለመከተል የሚፈጠር አቅምስ ምን ይሆን?
ዝቅ ብሎ በመውረድ አቅም መፍጠር የሚቻል ከሆነ ከፍ ብሎ ራስን ችሎ አቅም የማይፈጠርበት ሁኔታ ችግሩ ምንድ ነው?
እስከ አሁን ያልተኬደበት መንገድ የቼዝ ስፖርት ራሱን ማስቻል ነው። አንድ ሀገር አቀፍ ፌዴሬሽን ራሱን ችሎ ሲቆም የሚኖረው ጠቀሜታ እጅግ በጣም ብዙ ቢሆንም በጥቂቱ ለማንሳት ያህል
በነፃነት መስራትና መንቀሳቀስ ያስችላል
የነበረውን የመንግስት አስቸጋሪ ቢሮክራሲ ያስቀራል
ቼዝ ስፖርት እንደ ኬንያ በእጅጉ እንዲስፋፋ ያግዛል
ብዙ ባለሙያዎችን አካትቶ ለመስራት አመቺ ነው
ስፖርቱ ከፖለቲካ ንክኪ ወጥቶ በትክክል የህዝብ ይሆናል
የቼዝ ቤተሰቡ በቀጥታ ይሳተፍበታል
ከጥገኝነት ይላቀቃል
ከጥገኝነት ስትላቀቅ ያለህ አማራጭ ጠንክሮ መስራት ስለሆነ ሁሉም ሰው በተለይ ፌዴሬሽን ውስጥ የሚገባ ሰው ጠንክሮ በመስራት ስፖርቱን እንዲያድግ ይረዳል።
የራስነት ስሜት ይጨምራል
የስፖርቱ ወዳጆች እንዲሁም ሌሎች ስፖርቱን እንዲያግዙ ተነሳሽነት ይፈጥራል
ይበልጥ ግልፅ ለማድረግ ከዚህ በፊት መንግስት ለቼዝ ፌዴሬሽን 3 ሰው በመመደብ ይሰራ የነበረው ስራ ሁሉም ሰራተኞች ተነስተዋል። በአንፃሩ ሁሉም ፌዴሬሽኖች ስፖርት ለሁሉም በሚለው አደረጃጀት 1 ሀላፊ (በውስጡ ከ10 ያነሱ ባለሙያዎች ይዞ) ለሁሉም ፌዴሬሽኖች ( ከመንግስት ላልወጡ እንደ ቼዝ ላሉ ፌዴሬሽኖች) የመደበ ሲሆን ይህ ደግሞ ስፖርቱ በባሰ የሚያቀጭጭ ከመሆኑ በተጨማሪ መንግስት ራሳቸው ችለው ለማይወጡ ፌዴሬሽኖች ትኩረት እንደማይሰጥ በግልፅ ያሳያል። ምክንያቱ ሁሉም ፌዴሬሽኖች በአንድ አደረጃጀት በማጨቅ 1 ሀላፊ ለሁሉም ፌዴሬሽኖች በመመደብ የስፖርት እድገት ይመጣል ብሎ ማሰብ ሞኝነት ነው ።
ሌላ እንደ ፈለግክ የማትሰራበት የቢሮክራሲ ማነቆ እንዳለ ሆኖ አዲስ የቢሮ ሀላፊ ያውም ለቼዝ ለብቻው ያልተመደበ ሰው ጋር ተቀናጅቶ ለመስራት አዳጋች ከመሆኑ በተጨማሪ የጭቅጭቅ ቦታ እንዳይሆንም ያሰጋል።
ከአለምአቀፍ የቼዝ መርህና ሂደትም የሚቃረን ነው። የቼዝ ስፖርት የራሱ የፅህፈት ቤት ሰራተኛ(General secretary) ተመድቦለት በራሱ መርህና ፍልስፍና መመራት ያለበት ስፖርት ነው። ከሌሎች ስፖርት ጋር ታጭቆ ያውም ከነበረው በታች ወርዶ የቼዝ ስፖርት እድገትና መስፋፋት መመኘት የማይታሰብ ነገር ነው ።
ታድያ የቼዝ ፌዴሬሽን ስራ አስፈፃሚው ይህን ወርቃማው እድል በመጠቀም ለምን ቼዝን አልታደገም? እንዴት ከነበረበት የተሻለ ሂደት ዝቅ ማለትን መረጠ? መንግስት በጀትም ቢሮም ድጋፍ እሰጣለሁ እያለ ለግዜው ቢያንስ አንድ ሰራተኛ በመመደብ ራሱን ችሎ መውጣት ለምን አቃተው?
በእውነት ለመናገር ስራ አስፈፃሚው መንግስት ካስቀመጠው አቅጣጫ በተቃራኒ ለምን መቆየትን መረጠ የሚለው ራሳቸው የሚመልሱት ሆኖ በየተኛው መልኩ ሲታይ ግን ውሳንያቸው ለቼዝ ስፖርት የማይጠቅም የተሳሳተ አካሄድ መሆኑ ግን አጠያያቂ አይደለም።
አሁንም ግዜው አልረፈደም። የምንወደውን ቼዝ ስፖርት ራሱን ችሎ ከፍ ከፍ ብሎ ማየትን እንፈልጋለን። ይህ እውን ለማድረግ ደግሞ ወርቃማው ግዜ አሁን ነው። ይህን እድል መጠቀም ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ የቼዝ ማህበረሰቡ ከፍተኛ ተሳትፎ ወሳኝ ነው።
የቼዝ ስፖርት እንኳን ራሱን መቻል ለሌሎች መትረፍ የሚገባው እጅግ ጠቃሚና ተወዳጅ ስፖርት ነው።
አንድ ቤተሰብ ነን
234 views16:19