2022-06-25 06:05:31
በለቅሶ የተዋጠው መንደር...
ወሩ ወርሓ ሰኔ ቀኑ የወሩ 17ኛ ቀን ነው ድንገት ከአንድ መንደር ተገኘሁ መንደሩ የመነኮሳት መንደር ነው...ብዙ መነኮሳት አንድ አረጋዊ መነኮስ ከበው ያለቅሳሉ እሱም በጣም እያለቀሰ ነው የነገሩን ሥርና ጫፍ ለማወቅ የሚሻ ጉጉቴ እግሮቼን ከስፍራው ቸከላቸውና ቆሜ ቀረሁ፡፡
❖ ❖ ❖
አለባበሱ እንደነገሩ የሆነ የሰውን ዐይን የማይስብ ድሪቶ ለባሽ ምስኪን ሰው በባዶ እግሩ እየተራመደ ወደሚያለቅሱት መነኮሳት ተጠጋ፤ ያ እያለቀሰ የነበረ አረጋዊ መነኮስ ይህንን ምስኪን መሳይ ሰው ሽቅብ ተመለከተውና ይቀርበው ዘንድ ምልክት ሰጠው ያወቀውም ይመስላል፡፡
❖ ❖ ❖
ምስኪኑና ባለ ባዶ እግሩ ሰው በቀስታ ወደ አረጋዊው መነኮስ ጎንበስ ብሎ "አባቴ ሆይ ምን ሆነህ ነው የምታለቅ ሰው? መነኮሳቱስ ስለምን ያለቅሳሉ?" ሲል ጠየቀው፡፡
እኔ ሁለት ነገር አልለይ ብለውኛል አንደኛው የዚህ የምስኪኑና የባለ ባዶ እግሩ ሰው ማንነት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የአረጋዊው መነኮስ የለቅሶ ጉዳይ ናቸው፡፡ ቀስ እያልኩ ጉዳዩን ለማጣራት መጠጋት ጀመርኩ፡፡
❖ ❖ ❖
አረጋዊው ሰው ከበው የሚያለቅሱለትን መነኮሳት በዐይን ጥቅሻ ትተውት እንዲሄዱ አዘዛቸውና መነኮሳቱ በቅጽበት ተበተኑ፡፡
ጠጋ ብዬ ሳይ የአረጋዊው መነኮስ ማንነት አሁን መጣልኝ የማውቀው የአንድ ትልቅ ገዳም አስተዳዳሪ ናቸው የከበቧቸው መነኮሳትም የገዳሙ መናንያን ሲሆኑ የሚያለቅሱትም አስተዳዳሪያቸው ህመም ጠንቶባቸው በሞት ጣር ላይ በመሆናቸው ምክንያት ነበር፡፡
❖ ❖ ❖
አረጋዊው መነኮሳቱ መሄዳቸውን ዐይቶ ለዚያ ምስኪን ባለ ባዶ እግር ድሪቶ ለባሽ እንዲህ አለው...
"ወንድሜ ሆይ እኔ ከዚህ አስቀድሞ ማንም ሰው ያልሰራትን ኃጢአት ሠርቻለሁ፤ አባቴ ሆይ ብቻ በጸሎትህ አትርሳኝ..." እያለ እንባውን ዘረገፈው
በአዩኝ አላዩኝ እግሮቼ እየተንቀጠቀጡም ቢሆን ጠጋ ብዬ ማዳመጥ ጀመርኩ
❖ ❖ ❖
አረጋዊው መነኮስ ኑዛዜውን ቀጠለ እንዲህም አለ...
"እኔ በምኖርበት ሥፍራ ቅስና መሾም ፈልጌ አባቶች ባልሾሙኝ ጊዜ ወደ እሩቅና የማልታወቅበት ስፍራ ሔጄ ቅስና ተሹሜያለሁ ክህነት አለኝ ብዪ በድፍረት ቅዳሴ ቀደስኩ...፤የጠላሁትንም ብዙ ሰው በመርዝ ገደልኩ፤ ከእናቴ ጋር ዐሥር ጊዜ በተራክቦ ተኛሁ ከእኔ መፀነሰች ጊዜ መርዝ አጠጥቼያት ሕፃኑን ሳይወለድ በሆዷ ውስጥ እያለ ገደልኩት፤ ኃጢአቴ ብዙ ነው ተነግሮም አያልቅም፤ ከበጎ ሥራም ምንም ምን የሠራሁት የለም፤ አባቴ ሆይ ከዚህ ከኃላፊው ዓለም መውጫዬ ደርሷልና በጸሎትህ አትርሳኝ..." ብሎ እጅግ በበዛ ጣርና ጋር እየተሰቃየ ከብዙ ቆይታ በኀላ ነፍሱ ከሥጋው ተለየች፡፡
ለካስ የመነኮሳቱ ለቅሶ ይኸው ጣርና ጋር ኖሯል አልኩ በልቤ...
❖ ❖ ❖
ያ ምስኪን ባለ ባዶ እግር የአረጋዊውን ሙት በድን መሬት ላይ ትቶ ዐይኖቹን ሽቅብ አነሳ ነፍሱ እየተከታተላት መሰለኝ ወዲያው መራራ ለቅሶን እያለቀሰ በባዶ እግሩ እየተቻኮለ ገሠገሠ...ሔደ ከዐይኔም ተሰወረ...
❖ ❖ ❖
በኀላ እንደሰማሁት ያ ምስኪን ባለ ባዶ እግር ባሕታዊ ለትጹን ይባላል ይህ ጻድቅ በወንጌል "ስለ ወዳጆቹ ነፍሱን አሳልፎ የሚሰጥ ያለ ከሆነ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም" የሚለውን የቅዱስ ወንጌል ቃል አብነት አድርጎ የአረጋዊው ነፍስ ትማር በጾም በጸሎት በስግደትና በልዩ ልዩ ተጋድሎ ጠምዶ አምስት ጊዜ ለመሞት ደርሶ እየተጋደለ እግዚአብሔርን ለመነው ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ "ተው ለዚህ ሰው አትለምንለት ራስህንም አትግደል እግዚአብሔር እውነተኛ ፈፈራጅ ስለሆነ የእሱ ኃጢአት ሥርየት የለውም" አለው፡፡
❖ ❖ ❖
ይህንን የሰማው ጻድቁ ለትጹን "እሱን የማትምረው ከሆነማ እኔን ከሕይወት መጽሐፍ ደምስሰኝ በማለት" ይሞት ዘንድ ራሱን ወደ ባሕር ወረወረና ሞተ፡፡
ወዲያው ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይድረሰውና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ ቅዱስ ሚካኤልን አዘዘውና አባ ለትጹንን አስነስቶ በፊቱ አቆመው እንዲህም አለው "ለትጹን ወዳጄ ሆይ ለዚህ ምሕረት ለማይገባው ሰው ስለምን ራስህን ታስጨንቃለህ ህይወትህንስ በከንቱ ታጣለህ?" ሲል ጠየቀው፡፡
አባ ለትጹንም መለሰ እንዲህ ሲል
"መሓሪና ይቅር ባይ ጌታዬና መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የዚህን ኃጢአተኛ ሰው ነፍስ ማርልኝ የማትምረው ከሆነ ግን የእኔንም ነፍስ ጨምረህ ከእሱ ጋራ ወደ ስቃይ ሥፍራ ጣላት" አለው፡፡
❖ ❖ ❖
ጌታችንም የአባ ለትጽኑንን ደግነት አድንቆ የዚያን ኃጢአተኛ ሰው ነፍስ ያመጣት ዘንድ ቅዱስ ሚካኤልን አዘዘው፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም አመጣት ጌታችንም ያቺን ነፍስ ተቀብሎ በከበሩ እጆቹ ዳሰሳት እንዳልተፈጠረችም አደረጋት "ይህቺ ነፍስ አፈር ትሁን እንጂ ለስቃይም ለሕይወትም አትሁን" አለ፡፡ እንዳለውም ከ እም ኀበ አልቦ ኀበ ቦ ወደ እም ኀበ ቦ ኀበ አልቦ (ካለ መኖር ወደ መኖር እንዳመጣት ሁሉ ከመኖር ወደ አለመኖር መለሳት) አባ ለትጹንም የፈጣሪውን ፈጽሞ አመሰገነው፡፡
ይህ አባ ለትጹን ከብሕንሳ አገር የነበረ በጎልማሳነቱ በአባ ኤስድሮስ የመነኮሰ፤ ሰባት ሰባት ቀን እየጾመ መጋደል የጀመረ፤ መታሰቢያውን ለሚያደርግና ስሙን ለሚጠራ ከመድኃኔ ዓለም የምህረት ቃል ኪዳን የተቀበለ ታላቅ ጻድቅ ነው፡፡ በረከቱ በሁላችን ላይ አድሮ ይኑር፡፡
አርኬ
ሰላም ለአባ ለትጹን እስከ ፍጻሜ ዘክህለ፡፡ ከመ ያውጽእ እምደይን ብእሴ ህጉለ፡፡ ለለ መዋዕል ሰዱስ እንዘ ይበልዕ ቁጽለ፡፡ እም ብዝኀ ተጋደለ ገድለ፡፡ በአምሳለ ዖፍ ኮነ ሥጋሁ ቀሊለ፡፡
የሰኔ ፲፯ ቀን ስንክሳር
❖ ❖ ❖
ማስታወሻ
የዛሬ ዓመት አንብባው የጻድቁ ፍቅር ስቧት በዚህ ቀን ዳቦ ጋግራና ሻማ አብርታ እኔና ባለቤቴን ከትንሹ ወንድሟ ጋር ለጸሎት አቁማ ላዘከረችን የበኩር ልጄ ተማሪ ጽዮን (ፍቅርተ ቂርቆስ) ክብር ተጻፈ፡፡
ሰኔ ፲፰ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም.
አራት ኪሎ
አዲስ አበባ
42 viewsYabsra, 03:05