+ የሰጠኸኝ ሴት + እግዚአብሔር አዳምን "አትብላ ካልሁህ ዛፍ በላህን?" ብሎ ጠየቀው:: አዳምም :- ከእኔ ጋር እንድትሆን የሠጠኸኝ ሴት ከዛፉ ሠጠችኝና በላሁ አለ:: የሰጠኸኝ ሴት! በጣም ይገርማል:: ሚስቴ አላለም:: አዳምና ሔዋን የተገናኙ ቀን አዳም ያለውን አስታውሱ "ይህች አጥንት ከአጥንቴ ይህች ሥጋ ከሥጋዬ" ብሎአት ነበር:: ምንም እንክዋን አዳም ወላጆች ባይኖሩትም ሰው እናትና አባቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይተባበራል ብሎም ነበር:: ራቁታቸውን ቢሆኑም አይተፋፈሩም ነበር:: አሁን በራቁቱ ብቻ ሳይሆን በሔዋንም አፈረባት:: እናትና አባቱን ይተዋል እንዳላለ ሔዋንን ራስዋን ተዋት:: ከሚስቱ ጋር መተባበር ቀርቶ ክስ ጀመረ:: አካሌ አጥንቴ ሥጋዬ ማለቱ ቀረና የሠጠኸኝ ሴት አለ:: የጫጉላው ጊዜ አለፈና ከሚስትነትዋ ሴትነትዋ ብቻ ታየው:: በጋብቻ ብቻ አይደለም እግዚአብሔር የሠጠንን ነገር ሁሉ ቀድመን የራሳችን እናደርጋለን ነገሮች ሲበላሹ ግን ባለቤትነቱን ወደ እርሱ እንመልሰዋለን:: የሠጠኸኝ ሥራ የሠጠኸኝ ወላጆች የሠጠኸኝ ሰፈር የሠጠኸኝ ሀገር የሠጠኸኝ መሪ የሠጠኸኝ ጉዋደኞች የሠጠኸኝ ደካማ ሥጋ የሠጠኸኝ ዓይን ትናንት ሲሠጠን ዘምረን የተቀበልነውን ሥጦታ ዛሬ ለምሬት እንጠቅሰዋለን:: የሠጠኸኝ የሠጠኸኝ .... ሠጠኝና በላሁ ብለን ቀርጥፈን ለበላነው ዕፀ በለስ ፈጣሪን እንከስሰዋለን:: ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ ግንቦት 17 2012 አዲስ አበባ ኢትዮጵያ 61 viewsYabsra, 10:58