2022-08-18 08:12:58
ደብረ-ታቦር /ቡሄ/
ቡሄ ፣ ጅራፍ ማስጮ ፣ ችቦ ማብራትና ሙልሙል ዳቦ ሐይማኖታዊ ምስጢራቸው ምንድነ
በቤተክርስቲያናችን ስርዓት ነሐሴ ውስጥ እጅግ በርካታ በዓላት ይከበራሉ፡ከእነዚህ ውስጥ ደግሞ በጾመ ማርያም/
ፍልሰታ/ መገባደጃ ላይ የምናከብረው ከጌታችንንና ከአምላካችን ከመድሐኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኝ አበይት በዓላት መካከል አንዱ የሆነው የደብረ_ታቦር }በዓል ትልቁና ዋነኛው ነው፡፡
ደብረ-ታቦር ጌታችን ያዕቆብ ዮሐንስንና ጴጥሮስን ይዞ ወደ ታቦር ተራራ ካወጣቸው በኃላ በዛ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበትና ሙሴና ኤልያስን ጠርቶ የህያዋንና የሙታን
አምላክነቱን ያሳየበት ዕለት ነው ።ታዲያ ይህን እለትበሀገራችንና ቤተ-ክርስቲያናችን በቀላሉ አክብራው የምታልፍ በዓል አይደለም፡፡ ይልቁንም የተለያዩ ሥርዓቶችን በመፈፀም አስባው አክብራው ታልፋለች፡፡ ስለዚህም ዛሬ የበዓሉ ዋዜማ ላይ እንገኛለንና እንደ እግዚአብሔር አምላካችን መልካም ፈቃድ በበዓሉ ላይ ትርጉማቸውን
አውቀንም ሆነ ሳናውቅ ለበርካታ ጊዜያት የምንፈፅማቸውን ትውፊታዊ የሃይማኖት ሥርዓቶች ምስጢራቸው ምን እንደሆነ
እናያለን፡፡ ከስሙ ለመጀመር ያህል የደብረ-ታቦር በዓል በሀገራችን ቡሄ እየተባለ ነው የሚጠራው ቡሄ ምን ማለት ነው?
ቡሄ
,
ቡሄ ማለት ብራ፣ ብርሃን፣ ደማቅ ማለት ነው፡፡ ከስሙ ትርጉም እንደምንረዳው ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት በዓል
ስለሆነ ብራ፣ ብርሃን ደማቅ የሚል ፍቺ ያለው ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡
አንድም ቡሄ ማለት በዓሉ የሚውልበት ወቅት የክረምት ጨለማ አልፎ የብርሃን ወቅት የሚመጣበት ሰማይም ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት
የሚለወጥበት የመሸጋገሪያ ወቀት ስለሆነ ብራ ተብሏል፡፡
"ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት እንዲሉ"
አንድም ቡሄ…..ቡኮ "/ሊጥ" ማለት ነው፡፡ በዚህ በዓል ቡኮ ተቦክቶ ዳቦ/ሙልሙል/ ተጋግሮ የሚታደልበት በዓል ስለሆነ
ይህ ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡
እስኪ የሙልሙል ዳቦን ነገር ካነሳን እርሱስ ሃይማኖታዊ ትርጉም ይኖረው እንደሆነ የታሪኩንም አመጣጥ በዛው እንመልከት
ሙልሙል ዳቦ
,
ሙልሙል ዳቦ አመጣጡ ጌታችን ብርሃናዊ መለኮቱን በገለጠበት በዚህ ዕለት በደብረ-ታቦር አካባቢ የነበሩ ህፃናት እረኞች ቀኑ የመሸ ስላልመሰላቸው /ጌታችን በብርሃን
አካባቢውን ሞልቶት ስለነበረ/ በዛው ሆነው ከብትና በጎቻቸውን እየጠበቁ ሲቆዩባቸው የሰዓቱን መግፋት የተመለከቱ ወላጆች
በችቦ ብርሃን ተጠቅመው ለልጆቻቸው የሚቀመስ ሙልሙል ዳቦ ይዘው ወዳሉበት መምጣታቸውን ያሳያልና ታሪኩን እየዘከርን
በዓሉን እናከብራለን፡፡
አንድም እንደ ሐዋርያት የምስራች ሊነግሩን ወንጌል ሊሰብኩልን ነው። ታዳጊዎች በየደጃፋችን መጥተው "ቢሄ በሉ" ሲሉን ይበሉት ዘንድ ሙልሙል ይሰጣቸዋል። ይህም መጽሐፋዊ ነው ጌታችን ደቀ
መዛሙርቱን በደረሳችሁበት ሁሉ ሰላምታን ስጡ /ማቴ 10፣12/ብሏልና ሕፃናቱም የሐዋርያት ምሳሌ ስለሆኑ የጌታን በዓል ሊያበስሩ ሲመጡ ዳቦ መስጠት ልማዳዊ ብቻ ሳይሆን መጽሐፋዊ ነው ማለት ነው። መዝሙራቸው ደግሞ ሐዋርያት የምስራች ወንጌል ይዘው የመምጣታቸው ምሳሌ ነው፡፡ ሐዋሪያት በገቡበት ሀገር ሁሉ
አስተምረው አጥምቀው የፀጋ ልጅነትን አሰጥተው እንደሚቆዩ ሁሉ ልጆቹም ዘምረው አመስግነው መርቀው ውለዱ ክበዱ የመንግስተ ሰማያት ወራሾች ያድርጋችሁ ብለው አመስገነው ይሄዳሉና ህፃናቱ በሐዋሪያት ይመሰላሉ፡፡ ሌላው ሕፃናትና እረኞችን ስናነሳ ጅራፋቸውንም
ማንሳታችን አይቀሬ ነው፡፡ በሀገራችንም ከበዓሉ ቀን መድረስ አንስቶ ለበርካታ ቀናት በተለያዩ አካባቢዎች ጅራፍ ይጮሃል ይሄም በዚህ ታላቅ በዓል ሌላው ምሳሌያዊ ምስጢር ነው።
የጅራፍ ማጮህ ምሳሌነት
,
በደብረ ታቦር በዓል በትውፊታዊ መልኩ የሚታየው ምስጢር በእየሩሳሌም ስለሚሆነው የጌታችን የሞቱ ምሳሌ ነው፡፡ በዚህ በዓል ጅራፍ መገመዱ እና ማጮሁ ሁለት አይነት ምሳሌ አለው፡፡የመጀመሪያው ጌታችን በዕለተ አርብ የደረሰበትን ግርፋትና
ሕማም እናስብበታለን፣ ሁለተኛው ደግሞ ድምፁን ስንሰማ የባህሪ አባቱን የአብን የምስክርነት ቃልና በግርማው ሲገለጥ
የተሰማውን ነጎድጓድ ያስታውሰናል፡፡ የጅራፍን ትውፊታዊ ውርስ መጽሐፋዊ ትምህርቱንና ምስጢሩን ከትውልድ ጠብቆ
ለማስተላለፍ ከመኖሪያ ቤት ርቆና በሜዳ በተራራማ አካባቢ ብናረገው ጠቃሚ ነው፡፡ አሁን አሁን ግን ጅራፍን በርችት መቀየሩ
የሚያመጣውም የምስጢር ተፋልሶ መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡
የደብረ ታቦር በዓል በዚህ አይነት ምሳሌያት እየተከበረ ሰንብቶ መጠናቀቂያ የሚሆነው በሌላ ምሳሌያዊ ምስጢር ችቦ በማብራት ነው።
ችቦ ማብራት
,
በዚህ በዓል ምዕመናን በቤተ ክርስቲያንና በየቤታቸው ችቦ ለኩሰው የማብራታቸው ምስጢር ስለሁለት ነገር ነው። የመጀመሪያው ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር ተራራ ላይ የገለጠውን ብርሃናዊ መለኮት ለማሳየት የሚያመለክት ሲሆን ያንን በዘመናችን ለመግለጥ የበዓሉ ዋዜማ ማታ ችቦ አብርተን አምላካችንን እናመሰግናለን፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በተራራው ላይ የነበሩትን እረኞች ፍለጋ የወጡ ቤተሰቦቻቸው መሽቶ ስለነበር ይታያቸው ዘንድ እሳት ለኩሰው መብራት የመያዛቸውን ታሪክ ለመዘከር ነው።
በአጠቃላይ እንግዲህ በዓለ ደብረ ታቦር ከእነዚህ ምስጢር ካላቸው ትምህርቶችና ትርጓሜያት ጋር ይከበራል። እንግዲህ ይህ ታላቅ በዓል ከነሥርዓቱ ከትውልድ ወደ ትውልድ በቅብብል እንደመጣልን እኛም ሃይማኖታዊ ትውፊቱን ሳይለቅ ማስተላለፍ
ይጠበቅብናል፡፡ የዚህ ነገር ባለ ድርሻ አካላት ደግሞ ወጣቶችና ወላጆች ናቸው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በቡሄ ጨዋታ የሚሰሙ ግጦሞች ስድብ ፌዝና ሳቅ ያዘሉ ሆነው ይታያሉ። ተጫዋቾቹም ከሰጡን እንመርቃለን ካልሰጡን እንራገማለን አይነት መልዕክት
ያስተላልፋሉ።የሚብሰው አሳባቢ ነገሩ ደግሞ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን ወደ ገንዘብ ማግኛ መቀየሩ ነው፡፡ ስለሆነም ይህን
ነገር በተለይ የነገ የሀገር ተረካቢና የቤተክርስቲያን ተተኪ የሆንን ወጣቶች ማስተካከል ይኖርብል፡፡ወላጆችም ሕፃናት በየደጃፋችን ላይ በዓሉን ሊያበስሩ ሲመጡ አስደንግጦ ከማባረር በሚገባው መልኩ አስተምረን መርቀን ማስተናገድ ይጠበቅብናል ባህሉም እንዳይተው የበኩላችንን አደረግን ማለት ነው።
ዘተዋህዶ
@tewhodox
@tewhodox
ለወዳጅ ለዘመድ ለጓደኛ ያጋሩ
686 views05:12