2022-09-01 08:30:00
ኀሙስ ነሐሴ ፳፮ ፳፻፲፬ ዓ.ም
━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━━
#መኖር_ኋላ_ቀረ_ሞት_እየዘመነ
#በአፍሪካ_መሬት_ላይ
#ክስተት_ያሉት_ሁሉ_ክፍተት_እየሆነ
በመርከብ አናት ላይ
የሚኖር ባንዲራ ፥ መኖሩ እንዲወሳ
ንፋስን ያስሳል
እርሱ እንዲውለበለብ ፥ መርከብ እየረሳ።
ውኃ ላይ እያሉ...
ለመውለብለብ ብቻ
ንፋስን መለመን ፥ ንፋስን ማባበል
መጣራት ምዕበል !
ውኃ ላይ ያለ ነፍስ
አይጠይቅም ንፋስ ፥ ለመታየት ብሎ
መታየት ይመጣል ፥ ከመኖር ቀጥሎ።
ይልቅ...
ዓላማህ እንዲታይ ፥ በዓለም ተረጋግቶ
የእኔና የአንተን ጀልባ
ማጋጠም እንያዝ ፥ መጋጠሙን ትቶ።
ያኔ...
ጻማ ቢሆን ቀኑ
አብረን እስከሆንን ፥ ንፋስ ቢንቀለቀል
የአመንከውን ሰንደቅ
እንኳን ጀልባዬ ላይ ፥ ጀርባዬም ላይ ስቀል።
በገጠምነው መርከብ ፥ ቢታገል ማዕበል
አንጋደደን እንጂ ፥ ገደለን አንበል።
ዳሩ እኔና አንተ
የባህር ላይ ሞቱን ፥ አንድ ላይ ተላልፈን
ምነው በየብሱ ላይ ፥ መቅዘፊያው ተርፈን ?
የመከራ ጊዜ ፥ እንዳላዋደደን
ከውኃው ላይ ቆመን
እመሬት ስንደርስ ፥ ምን አንገዳገደን ?
እንመካከር ዘንድ ፥ መከራ ምንሻ
እንከባበር ዘንድ ፥ ችግር እጅ መንሻ
ሆኖብን ነገሩ ፥ ሁሌ ማያግባባን
ከአሳ ጥርስ አምልጠን ፥ ቢላ ጥርስ የገባን።
እንተራረድ ዘንድ ፥ እጃችን ቀለለው
የገዳይን ትርክት ፥ ዕውቀት እያጀለው
ተዋከብን !
ተዳከምን !
አያውቁት አወቅና...
አይስሉት ሰላና...
ምራቅ መዋጫ እንኳን ፥ ጊዜ የት አለና ?
ኧረ ቀስ...
ኧረ ቀስ...
ኧረ ቀስ...
ኧረ ቀስ...
ኋላ ለመቅበዝበዝ ፥ እግዜርን መቀስቀስ።
ኧረ ሰከን! ፥ ሰከን!
በባከነ ሰዓት ፥ ደግሞ ለመባከን ?
ኧረ ማሰብ! ፥ መንቃት!
አሜን ሳያልቅብን ፥ የአባቶች ምርቃት።
ቅዱስ ፥ ቅድስና
ፍፁም ፥ ፍፅምና
ከቶ የለምና !
ደግሞ አይኖርምና።
እንደው እንኳን ቢያንስ...
ባንቀደስ እንኳን ፥ ባንቀድስ እንኳን
ባንባረክ እንኳን ፥ ባንባርክ እንኳን
ባናላቅስ እንኳን ፥ ባናለቅስም እንኳን
ምን ያሳልቀናል ፥ በእናቶች ድንኳን ?
ኧረ ቀስ...
ኧረ ቀስ...
ኧረ ቀስ ፥ ገመናው አይውጣ
እንችለው ይመስል ፥ እግዜርን እናውጣ ?
የጭካኔ ልኩ ፥ በአጥብቆ ቢጠማን
እንደስማዚያ ፥ ማልን ለእርግማን
የመጥፋት የመግፋት ፥ ለምዶብን ታሪኩ
ደምግባት ጠፍቶብን
ደም ግብዓት ሆነ ፥ የመሠልጠን መልኩ
እንጂ ታውቀው የለ
በቂ ስለት እንጂ ፥ በቂ ሰበብ የለ።
እንጂ ታውቀው የለ
ምን ቢለን ቃሉ
ዓለም ትጠፋለች ፥ ትጠፋለች ዓለም
በትዕቢት ነው እንጂ ፥ በትንቢት አይደለም።
ትንቢት የሚያስቀይር ፥ ትህትና ስላጣን
ሀገራችን ሁሉ
እንዳይጥም አድርጎ ፥ ነገራችን ቀጣን።
መኖር ኋላ ቀረ ፥ ሞት እየዘመነ
በአፍሪካ ሰማይ ሥር...
ክስተት ያሉት ሁሉ ፥ ክፍተት እየሆነ !
ክስተት እና ክፍተት
መለየት ካቃተው ፥ ሕዝብ ይሉት ፍጡር
ራሱን ይመርመር
ቢያንስ ለሁለቱም ፥ እንዳይሆን ደንገጡር።
እንደሰው ሳንስቅ
ዕንባችን የማይቆም ፥ ሞቱን የሚያፈጥነው
መርከብ እየረሱ
ንፋስ ሚለምኑ ፥ ሰንደቆች መብዛት ነው።
ኧረ ቀስ !
┈┈┈┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
ኤልያስ ሽታኹን
╰══•••┈ ┈ ┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
ለመቀላቀል @poemandquote
አስተያየት @poemandquotebot
┏─━─━─━─━≪♡≫━─━─━─━─┓
❘ ❝ ሰው፡ከሆኑ፡በቂያችን፡ነው። ❞ ᴀ ❘
┗─━─━─━─━≪♡≫━─━─━─━─┛
427 viewsመከበር, 05:30