2023-02-03 22:55:41
" የታላቂቱ ከተማ ጾም"
የታላቂቱ ከተማ የነነዌ ኃጢያት ከመብዛቷ የተነሳ እግዚአብሔር ፊት ደረሰች ።ት.ዮና ፩÷፪ ነቢዮ ዮናስ ሄዶ በዛች በታላቂቁ ከተማ በነነዌ እንዲሰብክ #እግዚአብሔር ላከው የዋህው ዮናስም #እግዚአብሔር መሐሪ ነው በኃላ ሄጄ ካልተመለሳችሁ ከሰማይ እሳት ወርዳ ትበላችዋለች ብዬ ከሰበኩ በኃላ ቢምራቸው እኔ ሐሰተኛ ነቢይ እባላለው ብሎ ወደ ነነዌ መሄድ ትቶ ወደ ተርሴስ በመርከብ ተሳፍሮ ኮበለለ።
አዳም እጸ በለስን ከበላ በኃላ ከእግዚአብሔር ፊት ለመደበቅ ሞክሮ ነበር እግዚአብሔር አምላክም እንደ አባት ነውና እንዳይሳቀቅበት አንድም በኃላ ዘመን አላዋቂ የሰው ሥጋን ተዋህጄ አድንሃለው ሲለው ባላዋቂ ልማድ ከፊቱ የተሰወረበት ይመስል " አዳም አዳም ሆይ ወዴት አለህ " ሲል በፍቅር ጠይቆት ነበር።
አበው " #እግዚአብሔር አምላክ ሞኝ ነጋዴን ይመስላል መንግስተ ሰማያትን የምታክል ውድ ነገር በጥርኝ ውኃ ልስጣችሁ ብሏልና" ይላሉ ማቴ ፲ ÷ ፴ ፱ የዋህው ዮናስ ይህን ብሒለ አበው ሳይሰማ የቀረ አይመስልም እግዚአብሔር እንደ ሞኝ ቆጥሮ አካሄዱንም እንደማያውቅበት አስቦ ከፊቱ ኮበለለ ።
የዳዊትን መዝሙር ያልሰማህ ይህ አይሁዳዊ ሰው ምነኛ የዋህ ነው።
"ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ?
ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ?
ወደ ሰማይ ብወጣ፥ አንተ በዚያ ነህ፤
ወደ ሲኦልም ብወርድ፥ በዚያ አለህ።
እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ፥ እስከ ባሕር መጨረሻም ብበርር፥ በዚያ እጅህ ትመራኛለች፥ ቀኝህም ትይዘኛለች።በውኑ ጨለማ ትሸፍነኛለች ብል፥ ሌሊት በዙሪያዬ ብርሃን ትሆናለች፤ ጨለማ በአንተ ዘንድ አይጨልምምና " #መዝ ፻ ፴ ፰(፻ ፴ ፱) ÷ ፯-፲ ፩
እግዚአብሔር ግን የተሳፈረበትን ታንኳ በማዕበልና በሞገድ አስጨነቃት ይህም ሁሉ በእርሱ ምክንያት እንደሆነ ለመረከበኞቹ ነግሮ እርሱን ወደ ባሕር ቢጥሎት በጸጥታ መጓዝ እንደሚችሉ ገለጠላቸው ። ባንተ በእግዚአብሔር ሰው ላይማ ይህን አናደርግም ባይሆን ዕጣ እናውጣ ተባባሉ ዕጣውም ሲወጣ ለሦስት ጊዜ ያክል በዮናስ ላይ ደረሰበት ወደ ባሕሩም ጨመሩት ወዲያውም ታላቅ ዓሳ አንበሪ ከእግዚአብሔር ታዞ ዮናስን ዋጠው መንገዱንም ከተርሴት ወደ ነነዌ ሀገር ቀየረው ነነዌም ሲደርስ ከደረቅ የብስ ላይ አውጥቶ ተፋው “ከሰው ይልቅ #የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና፥ ” ፩ኛ ቆሮ ፩፥፳ ፭
ዮናስም የእግዚአብሔር ሥራ እያደነቀ ወደ ነነዌ ከተማ ገብቶ ንስሐን ፣ጾምን፣ ጸሎትን ሰበከላቸው ካልተመለሱ ግን የእሳት ዲን እንደሚበላቸውም አስጠነቀቃቸው ነነዌም ሰማች ወደ ልቧም ተመለሰች ንጉሱም ህጻናትና የሚጠቡ ልጆች ሳይቀሩ የእናታቸውን ጦት እንዳይጠቡ እንሰሳትም ቢሆኑ እስከ ሦስት ቀን ድረስ አፋቸው ታስሮ ከምግብ ተከልክለው እንዲቆዮ የጾም አዋጅ አወጀ። ከሦስት ጾም ቀናት በኃላ እግዚአብሔር ለነነዌ ምሕረትና ይቅርታ አደረገላት።
በዚህም ከሰማይ ይመጣባቸው የነበረ የእሳት ዲን ቀረላቸው ነቢዮ ዮናስም ይህው እግዚአብሔር ማራቸው እሳቱም ቀረላቸው። ስለዚህ እኔ የታለ እሳቱ ?ውሸታም እባላለው ብሎ ሰጋ እግዚአብሔር አምላክ ግን ቅዱሳኑ ዝቅ ብለው እሱ ይከብር ዘንድ ሰው አይደለምና ዮናስም አልዋሸም ባትመለሱ ይበላችሁ ዘንድ ያለው እሳት ይህቺ ነበረች ሲል ለምልክት እሳት ከሰማይ አውርዶ የነነዌን ከተማ እረጃጅም ዛፎች ጫፎቻቸውን አቃጥላ ተመልሳ እንድትሄድ አድርጓል ።
ባትመለሱ ኖሮ ወርዳ ትበላችሁ ነበር ሲል ነው። ዛሬ ዳግማዊቷ ነነዌ ኢትዮጵያ እሳቱ ወርዶ እየለበለባት ነው። ዘረኝነቱ እሳት ነው፣ የሥልጣን ሽኩቻው እሳት ነው፣ እምነት የለሽነቱ እሳት ነው... ግን ዛሬም አልተመለሰችም ዮናሶቿም ስደት፣ ሽሽትን መርጠው ከሩቁም ሆነው የወደፊቷን ይተነቢዮላት ዘንድ ወደዋል። መቆስቆስ ቀላል ነው መማገድ ግን መንደድን በኃላም አመድ መሆንን ያስከፍላል።
ተክለ ኤል ኃ/ማርያም
አ.አ ኢትዮጵያ
የካቲት፲፬/፳ ፲፫ዓ.ም
205 viewsተርቢኖስ ሰብስቤ , 19:55