2022-08-23 15:56:43
‘ሁከት ይወገድልኝ’ – የሰበር ችሎት የህግ ትርጉምየአንድ ንብረት ባለይዞታ የሆነ ሰው ይዞታውን ለመንጠቅ ወይም በይዞታው ላይ ሁከት ለመፍጠር የሚፈፀምን ማንኛውንም ድርጊት እንዲቆም ወይም ንብረቱ እንዲመለስለት የሚያቀርበው የይዞታ ክስ
በፍ/ሕ/ቁ. 1149/1/ መሰረት የሁከት ይወገድልኝ ክስ መቅረብ የሚችለው አቤቱታ አቅራቢው ለክርክሩ መነሻ በሆነው ነገር በቀጥታ ወይም በጠባቂ ይዞታ ሲኖረው ነው፡፡ እንዲሁም የይዞታ ክስ የሚቀርበው ለክርክሩ መነሻ የሆነውን ንብረት በወቅቱ ለመያዝ ምንም ዓይነት መብት በሌለው ሰው ላይ ስለመሆኑም የድንጋጌው መንፈስ ያስረዳል፡፡ የሁከት ይወገድልኝ አቤቱታ አቅራቢ በማስረጃ ማረጋገጥ ያለበት ንብረቱ በይዞታው ስር የነበረና የሁከት ድርጊት ፈፃሚው የኃይል ተግባር በመጠቀም ወይም በሚስጢር ንብረቱን የወሰደበት መሆኑን ነው፡፡ ሁከት ተፈጥሯል የሚባለው ባለይዞታ የሆነው ሰው በይዞታው ስር በሚገኘው ንብረት እንዳይገለገልበት ሌላ ሰው ጣልቃ ገብቶበት መሰናክል ሲፈጥርበት ወይም ረብሻ ሲፈጥርበት ነው፡፡
ሰ/መ/ቁ. 80241 ቅጽ 15፣[1] ፍ/ህ/ቁ. 1149(1)
የሁከት ይወገድልኝ ክስ ለማቅረብ ከሳሹ ማስረዳት ያለበት ባለቤትነት ወይም የባለቤትነት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት እንዳለው ሳይሆን ክስ ያቀረበበት ንብረት ህጋዊ ባለይዞታ መሆኑ በሌላ አነጋገር ሁከት የተፈጠረበትን ነገር በእጁ አድርጎ በእውነት ሲያዝበት እንደነበር ነው፡፡
ሰ/መ/ቁ. 38228 ቅጽ 9[2]
ሁከት እንዲወገድ በቀረበ ክስ ተከሳሽ የሚያነሳው የባለቤትነት ክርክር እራሱን የቻለ ባለቤትነት የመፋለም ክስ /petitory action/ በሚመለከተው ላይ አቅርቦ ከሚታይ በስተቀር ሁከት ተፈጥሯል ወይስ አልተፈጠረም ተብሎ ለሚያዘው ጭብጥ ተገቢነት የለውም፡፡
ሰ/መ/ቁ. 27506 ቅጽ 6[3]
የሁከት ይወገድልኝ ክስ ሲቀርብ በፍርድ ቤት በጭብጥነት ተይዞ መፈታት የሚገባው ጉዳይ ሁከት አለ ወይንስ የለም? የሚለው ነው፡፡
የውሉ ተገቢውን የአጻጻፍ ሥርዓት ተከትሎ አለመደረግ ይዞታው በተጨበረበረ መንገድ ስለመያዙ ወይንም በማናቸውም ሕገወጥ ሁኔታ ስለመያዙና ሁከት እንዲወገድለት ክስ ያቀረበው ከሳሽ በይዞታው በእውነት ሊያዝበት እንደማይችል አያረጋግጥም፡፡ በዚህ ረገድ ውሉ ጉድለት አለበት ከተባለ በፍ/ብ/ሕ/ቁ/1808(2) ላይ እንደተመለከተው ውሉ ፈራሽ ነው እንዲባል የክስ ምክንያት ከሚሆን በስተቀር ሁከት ይወገድልኝ ተብሎ በቀረበ ክስ ላይ ሊስተናገድ የሚችል አይሆንም፡፡
ሰ/መ/ቁ 36645 ቅጽ 9[4]
በአብላጭ ድምፅ የተሰጠ
[1] አመልካች ጽናት የሆቴል ቱሪዝም ስራዎች ኃ.የተ. የግል ማህበር እና ተጠሪ አቶ ዳመነ ነጋ /5 ሰዎች/ የካቲት 12 ቀን 2005 ዓ.ም.
[2] አመልካች ሐጂ መሀመድ አወል ረጃ እና ተጠሪ እነ አቶ ዲኖ በሺር /2 ሰዎች/ ታህሣሥ 7 ቀን 2001 ዓ.ም.
[3] አመልካች እነ ሣሙኤል ውብሸት እና ተጠሪ ብዙነህ በላይነህ ሐምሌ 19 ቀን 1999 ዓ.ም.
[4] አመልካች ረዳት ሳጂን አያኖ አንጀል እና ተጠሪ እነ ወ/ሮ ዓለሚቱ ህዳር 11 ቀን 2001
1.1K views12:56