ኸዋሪጅና ሺዓ
ትርጉም : በሙሐመድ ሰዒድ
“ኸዋሪጅ” ማለት ቃሉ ዐረብኛ ሲሆን በጥሬ ትርጉሙ ከሙስሊሙ ማኅበረሰብ ረግጦ መውጣትና ማፈንገጥ ማለት ነው፡፡ ይህ ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቅም ላይ የዋለዉም በኸሊፋ ዐሊይ ኢብኑ አቢ ጧሊብ (ረ.ዐ.) ዘመን ሲሆን፤ ቃሉም ሙስሊም መሪን (ዐሊን) ባለመታዘዝ አምፀውና አፈንግጠው የወጡ ቡድኖችን ለማመልከት ነው ነበር ጥቅም ላይ የዋለው፡፡ በመሠረቱ በእስልምና አስተምህሮ መሠረት በወንጀልና አላህን (ሱ.ወ.) በማመፅ እስካላዘዘ ድረስ ሙስሊም መሪን መታዘዝ ግዴታ ነው፡፡ ታዲያ ኸዋሪጆች ይህንኑ አስተምህሮ ቢያውቁም ለራሣቸው ትክክለኛነት የተለያዩ ምክንያቶችን በመደርደር ከሙስሊም መሪ ትዕዛዝ፣ ከመመሪያዉና በርሱ ሥር ከመተዳደር አፈነገጡ፡፡ ትልቁ ምክንያታቸዉም በዳይ እና ጠማማ የሆነ መሪን የመታዘዝ ግዴታ የለብንም የሚል ነው፡፡ በዳይ እና ጠማማነትንም የሚያስቀምጡት በራሣቸው መስፈርትና ግምገማ ነው፡፡ ዐሊ ኢብኑ አቢ ጧሊብን (ረ.ዐ.) ያህል ታላቅ እና ገና ምድር ላይ እያሉና ሳይሞቱ በጀነት የተመሠከረላቸውን የነቢዩ (ሰ.ዐ.ወ.) ባልደረባ በጥመት መወንጀል በራሱ ትልቅ ግርምትን የሚጭር ነው፡፡ የኸሊፋው ዐሊ ክብር በቀላሉ ከዚህ እስከዚህ ተብሎ የሚገለጽ አይደለም፡፡ ታላቅ ሶሐቢ ናቸውና፡፡
ዛሬም ድረስ ያሉ ኸዋሪጆች እና የተክፊር አመለካከት ያላቸዉ ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች በዚሁ ባህሪያቸው ይታወቃሉ፡፡ እኛ ብቻ ነን አዋቂ፣ እኛ ብቻ ነን ትክክል የሚል ስሜት የተጠናወታቸው ናቸው፡፡ ትልቅ ትንሽ፤ አዋቂ መሃይም ሳይሉ ሰዎችን በጭፍንና በበደል ይፈርጃሉ፡፡ ለብዙዎች ክብር ላላቸው ስብእናዎችም ክብርና ዕውቅና ይነፍጋሉ፡፡ ደረጃ ያላቸው ዑለሞችን ጭምር ከደረጃቸው ያወርዳሉ፡፡
“ኸዋሪጅ” የሚለው ቃል ያኔ በዐሊ ኢብኑ አቢ ጧሊብ (ረ.ዐ.) ዘመን ለዚያን ጊዜ ቡድኖች የተሠጠ ስያሜ ይሁን እንጂ ከዚያ ወዲህም ቢሆን ከዋናው የሙስሊም ስብስብ አፈንግጠው ለወጡት ቡድኖች ሁሉ ሊዉል ይችላል ይላሉ በርካታ ሙስሊም ሊቃዉንት፡፡
https://t.me/NejashiPP