2022-06-23 15:08:16
#ዕፀ_ገነት (#የገነት_ዛፍ) - #የአምላክ_እናት
በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ
━━━━━━✦༒ ༒✦━━━━━━
✥ ጦማሩን ሌሎች እንዲያነቡትም Forward, React, Pin & Comment በማድረግ ለወዳጆችዎ ያካፍሉት።
☞ @gishenmaryam
☞ የሕይወት ፍሬ ክርስቶስን በድንግልና የወለደች ቅድስት ድንግል ማርያም በገነት ውስጥ ባሉት ዕፀዋት ኹሉ እንደምትመሰል በርካቶች ሊቃውንት በየድርሳናቸው ገልጸዋል፡፡ እነዚኽም በገነት ያሉ አዝርዕት፣ አትክልት፣ ዕፀዋት በዚኽ ዓለም ካሉት የተለዩ ናቸው፤ ቅጠላቸው ሰፋፊ ነው ዐሥራ ኹለት ክንድ ይኾናል፤ መዐዛቸው የመንፈቅ መንገድ ኼዶ ይሸታል፤ ፍሬያቸው የጋን መክደኛ ያኽላል፤ ጣዕማቸው ነፍስን ከሥጋ ይለያል፤ አላምጠው እስኪውጧቸው ድረስ ፍሬ ይተካሉ፤ ጥራታቸው እንደ መስታዮት ፊትን ያሳያል (ሕዝ ፵፯፥፲፪-፲፫፤ ራእይ ፳፪፥፪-፫)፡፡
☞ ሊቁ ኤጲፋንዮስ የሥነ ፍጥረትን ነገር በሚያሳውቀው መጽሐፉ የዕፅወ ገነትን ነገር ሲያስረዳ፡- “ወቈጽለ ዕፀዊሃኒ ለገነተ ንኡሳን በበ፲ቱ ወ፪ቱ እመት ወጽጹላን እሙንቱ ከመ ከዋክብት…” (በዚኽችም በገነት በውስጧ ያሉት አዝርዕት፣ አትክልት፣ ዕፀዋት ታናናሹ ቅጠላቸው ዐሥራ ኹለት ዐሥራ ኹለት ክንድ ይኾናል፤ ይኸውም እንደ ከዋክብት ያበራሉ፤ ፍሬያቸው እንደተመዘነ ብር ክብ ነው፤ ጣዕማቸው ከአፍ መዐዛቸው ከአፍንጫ ሳይለይ ሰባት ቀናት ይቆያል) በማለት ገልጧል፡፡
☞ ለነዚኽ ኹሉ ሊቃውንት መሠረት የኾናቸው ይኽ ታላቅ ምስጢር የተገለጠለት የአዳም ሰባተኛ ትውልድ የኾነው ሔኖክ ያየው እውነት ነው፡፡ ይኽ ሔኖክ ከሰው ተለይቶ ስድስት ዓመት በእግረ ገነት ወድቆ በሰባተኛው ተሰውሯል (ዘፍ ፭፥፳፬፤ ሔኖ ፬፥፩)፡፡ ይኽ አባት የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስለኾኑት ስለገነት ዛፎች ያየውን የተገለጠለትን ሲገልጥ “ወርኢኩ ፯ተ አድባረ ክቡራነ ወኲሉ ፩ዱ እምነ ፩ዱ ወየዐውድዎ ዕፀወ መዐዛ…” (የከበሩ ሰባት ተራራዎችን አየኊ፤ ኹሉም አንዱ ከአንዱ ልዩ ልዩ የኾኑ ዕንጨቶች ከበዋቸዋል፤ ከውስጣቸውም መቼም ቢኾን እንደ ርሱ አድርጐ የሸተተኝ ሌላ ዕፅ የሌለ ከሽቱ ኹሉ የበለጠ የሽቱ ዕንጨት አለ፤ ዛፉም ቅጠሉም አበባውም ለዘላለም አይጠወልግም፤ ፍሬውም ያማረ ነው፤ ያውም እንደ ዘንባባ ፍሬ ያለ ነው፤ ያን ጊዜ ይኽ ዕንጨት መልካም ነው፤ ቅጠሉም አበባውም ለዘላለም አይጠወልግም፤ ፍሬውም ያማረ ነው፤ ያውም እንደ ዘንባባ ፍሬ ያለ ነው፤ ያን ጊዜ ይኽ ዕንጨት መልካም ነው፤ ቅጠሉም ያማረ ነው፤ ፍሬውም ፊት ለፊት ለማየት እጅግ ያማረ ነው አልኊ) ሔኖ ፯፥፩-፲፩ በማለት በገነት ስላያቸው አዝርዕት፣ አትክልት፣ ዕፀዋት ምስጢር ተናግሯል፡፡
☞ ይኽቺውም የገነት ዛፍ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስትኾን፤ የማይጠወልገው ቅጠሏ ለዘላለም የማይለወጠው የድንግልናዋ፤ የዛፏ ፍሬ የልጇ የፍሬ ሕይወት የክርስቶስ ምሳሌ ነው፤ ያ ፍሬ ሲቈርጡት እየተካ እንደማያልቅ ኹሉ ለቤዛ ብዙኀን የተሰጠ የጌታ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ ዕለት ዕለት እየተሠዋ ሲሰጥ የመኖሩ ምሳሌ ነውና፤ ይኽነን ልዩ ምስጢር የተረዱ ሊቃውንት ይቺ ነቢዩ ሔኖክ ያያት በሱራፊ መልአክ የምትጠበቅ የገነት ዛፍ የድንግል ማርያም ምሳሌ መኾኗን መስክረዋል፡፡
☞ ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስም በእንዚራ ስብሐት መጽሐፉ፡-
“ኦ እግዝእትየ ማርያም ደብረ ትንቢት ዘየዐውድዋ ዕፀወ መዐዛ
በውስተ መጽሐፉ ለሔኖክ እንተ ተጽሕፈ ዕዘዛ”
(እመቤቴ ማርያም ሆይ በሔኖክ መጽሐፍ ውስጥ ክብሯ የተጻፈ፤ የመዐዛ ዕፀዋት የሚከብቧት የትንቢት ተራራ ነሽ) በማለት በእውነት ምሳሌዋ መኾኑን አስተምሯል፡፡
☞ የማሕሌተ ጽጌ ደራሲያን ሊቃውንት አባ ገብረ ማርያም ዘደብረ ሐንታና አባ ጽጌ ድንግል በማሕሌተ ጽጌ መጽሐፋቸው፡-
“በኲናተ እሳት ዘይነድድ ዘየዐቅበኪ ሱራፊ
ወአጼነወ መዐዛኪ ሔኖክ ጸሐፊ
ጽጌ ዕፀ ገነት ማርያም ዘኢትትነገፊ”
(ሱራፊ መልአክ የእሳት ጦርን ይዞ የሚጠብቅሽ፤ መዐዛሽንም ጸሐፊ ሔኖክ ያሸተተልሽ የማትረግፊ የማትጠፊ የገነት ዛፍ ማርያም) በማለት ሔኖክ ያያቸው የገነት ዛፎች በእውነት የድንግል ማርያም ምሳሌ መኾናቸውን ተናግረዋል፡፡
☞ ዳግመኛም እነዚኹ ሊቃውንት የቅድስት ድንግልን የመዐዛ ንጽሕናዋን፣ የመዐዛ ቅድስናዋን፣ የመዐዛ ምግባሯን ድንቅነት በገነት ውስት ባሉት ልዩ ሽታን በሚሸቱ በገነት ዛፎች ሲመስሉ፡-
“እንዘ ይፀውረኪ በሐቂፍ ወይስዕመኪ በአፍ
አመ አፍለሰኪ ወልድ ውስተ የማኑ ለዐሪፍ
ጽጌ ዕፀ ገነት ማርያም ዘትጼንዊ ለአንፍ
እንዘ ይትጓድዑ አክናፈ በክንፍ
ለቀበላኪ ወረዱ አእላፍ”
(ለአፍንጫ መዐዛን የምትሰጪ የገነት ዛፍ ማርያም ሆይ፤ ልጅሽ በክንዱ ዐቅፎ በአፉ እየሳመ በቀኙ ሊያሳርፍሽ ባሳረገሽ ጊዜ፤ አንቺን ለመቀበል ክንፍ ለክንፍ እየተጋጩ እልፍ አእላፋት መላእክት ወረዱ) በማለት የመዐዛዋን ታላቅነት መስክረውላታል፡፡
☞ ኢትዮጵያዊዉ ቄርሎስ ዐምደ ሃይማኖት የተባለው ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም ቅድስት ድንግል ማርያም አማናዊት ዕፀ ገነት መኾኗን በአርጋኖን መጽሐፉ፦ “ዕፀ ገገት ዘበጽጌሃ ንትሜዐዝ ወእምፍሬሃ ንሴሰይ ወታሕት አዕጹቂሃ ናጸልል… ኦ ድንግል ዖመ ገነት ዘተከላ የማነ እግዚአብሔር ወአጽገያ ኀይለ መንፈስ ወአፍረያ ጽላሎተ አብ - በአበባዋ የምንሻተትባት፤ ከፍሬዋም የምንመገባት፤ በሥሯም (በቅርንጫፎቿም) የምንጠለልባት የገነት ዕንጨት ናት… ድንግል ሆይ የእግዚአብሔር ቀኝ የተከላት፣ የመንፈስ ቅዱስ ኀይል እንድታብብ ያደረጋት፣ የአብ ጥላ እንድታፈራ ያደረጋት የገነት ዛፍ ነሽ።” በማለት በሥልጣነ እግዚአብሔር ተጠብቃ በሃይማኖት፣ በምግባር፣ በንጽሕና፣ በቅድስና ጸንታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን አፍርታ የተገኘች አማናዊት ዕፀ ገነት የመኾኗን ምስጢር አጒልቶ አሳይቷል። ሉቃ ፩፥ ፴፭- ፵፪
☞ በሕማማት ሰላምታው ላይም፡-
“ማርያም ገነቱ ለወልደ ያሬድ (ኢያራፕ) ወሬዛ
ዘተረክበ ብኪ ለድኂን ወቤዛ
ፍሬ ጽድቅ ምስለ መዐዛ ሰላም ለኪ፡፡”
(ከመልካም መዐዛ ጋራ የጽድቅ ፍሬ ለድኅነትና ለቤዛ የተገኘብሽ ጐልማሳ የሚኾን የያሬድ ልጅ የተክል ቦታ ማርያም ሰላምታ ላንቺ ይገባሻል፡፡)
በማለት ምስጢሩን አመስጥሯል፡፡
☞ የሕይወት ፍሬ ኢየሱስ ክርስቶስን ያስገኘሽልን የገነት ዛፍ ድንግል ማርያም ሆይ በረከትሽን በእኛ በልጆችሽ ላይ አትረፍርፊልን፡፡
ምንጭ፦ ነገረ ማርያም በብሉይ ኪዳን ክፍል ፩ እና መልክአ ሕማማት ንባቡና ትርጓሜው በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ
☞ @gishenmaryam
•᳀͟͞ ͟͞ ̸͟͞ ͟͞ ͟͞ ͞ ͟͞ ̸ ͟͞ ͟͞᯼᳀᯼͟͞ ͟͞ ͟͞ ̸͟͞ ͟͞ †✙† ͟͞ ͟͞ ̸͞͝ ͟͞᯼᳀᯼͟͞ ͟͞ ͟͞ ̸͟͞ ͟͞ ͟͞ ͟͞ ̸͞͝ ͟͞᳀•
✥ በዚህ መንፈሳዊ ቻናል ላይ የሚተላለፉ መንፈሳዊ ጦማሮች ለእርስዎና ለወዳጆችዎ እንዲደርሱ ቻናሉን Join / Follow በማድረግ ሌሎችንም ወደ ግሩፓችን ይጋብዙ።
በቴሌግራም ወዳጅ እንሁን?
☞ @Kidusat_Mekanat
☞ @Kidusat_Mekanat
☞ @Kidusat_Mekanat
የዩቲዩብ ቻናላችንን « መኮሬታ Mekoreta Tube »ን በሚከተለው ሊንክ ከፍተው Subscribe & Join ያድርጉ።
https://m.youtube.com/channel/UCUBStsekCniQtATyZDdFqQQ
896 viewsአንተነህ ውብሸት, 12:08