2022-08-27 18:52:04
ጠይሙ ባሌ !
ክፍል.......2
(በእውነተኛ ታሪ የተመሰረተ)
አዘጋጅ፦ ፍቅርን በቃላት
.
.
.
ከጋባዦቻችን ጋር የሞቀ ሰላምት ተለዋውጠን ልጆቻችንን ከታሰሩበት መቀመጫቸው ፈታንና ወደቤት ዘለቅን :: ከባሌ የሚያናድደኝ ዋንኛው ፀባዩ ሰው ፊት ሲሆን የሚፈጥረው ሸብ እረብ ነው ...ፍፁም የሆነ ባልና አባት ሆኖ ቁጭ ይላል :: ሌሎች ታድለሽ ሲሉኝ የሆዴን በሆዴ ይዤ ጥርሴ ኢኝ ይላል ...ድንቄም መታደል ::
ከሚስትነት ወርጄ ከሰውነትም ቀልዬ እንደቤት እቃ መቆጠር ከጀመርኩ ከራርሜያለሁ :: ምርር ሲለኝ "ለልጆቼ ስል " የሚል ሰበብ ለራሴ ሰጥቼ እፅናናለሁ ...ግን እስከመቼ ይሆን እንዲህ እንደ ግዑዝ ተቆጥሬ የምኖረው ? ስሜት አለኝ : መወደድ ... መታቀፍ ... መሳም ... መከበር ...የፍቅር ጨዋታ : አይዞሽ መባልን ...ደከመሽ እረፊ መባልንም እፈልጋለሁ ::
ግን ይህን የጎደለ ቀዳዳ በምን በማን ልሙላው ? እንዳልኩት ወደ ቤት ስንገባ አባትና ባል ተብየው ፈጠን ብሎ የልጆቹን ጃኬቶች አወለቀና በስርአት ሰቀላቸው ::
"ወይ ድራማ " አልኩ በሆዴ :: አሁን በህይወቱ ኢምንት ለውጥ ለማያመጡ ሰዎች ይህ ሁሉ ትርኢት ለምን አስፈለገ ? ወደሳሎን ስንገባ ሁለት ፈረንጅ ባልና ሚስት ከሁለት ልጆቻቸው ጋር ትልቅ ሶፋ ላይ ተደርድረዋል :: "ሄይይይይ " አለ የኔው ጉድ በደስታ እየተፍለቀለቀ :: ሻነን ከሁዋላዬ "ሄንሪም የስራ ጉዋደኛቸው ነው " እለች ጀርባዬን እየነካች "እስዋም ባለቤቱ ነች ...ተዋወቁ "::
ሁለቱም ብድግ ብለው በፈገግታ ሰላምታ ተለዋወጥና እኔም ልጆቼን ይዤ ከፊት ለፊታቸው ያለው መሀከለኛ ሶፋ ላይ ተቀመጥኩ :: ባሌ እንዲቀመጥ ጠጋ ብልለትም እንዳላየኝ ሆኖ ደረቅ ወንበር ላይ ፈንጠር ብሎ ተኮፈሰ :: አፍጥጬ አየሁት ...ኮፍያውንና ጃኬቱን ሳያወልቅ ተከምሮዋል ...አይቼ አልጠግበው እንዳልነበር ዛሬ አፈርኩበት ::
በአማርኛ "ኧረ ኮፍያህን እንኩዋን አውልቅ " ብዬ አንሾካሾኩ :: ለአንድ ሰከንድ ያህል አፈጠጠብኝና እንዳልሰማኝ ሆኖ ጨዋታውን ቀጠለ ::
ይህ ሰው ማነው ? እውነት ይህን ሰው ነው ወድጄ : ከንፌ : አብጄ ያገባሁት ? በቃ ትዳር ማለት ይኸው ነው ...የቁም ገሀነም ? ወዲያው ደግሞ አጠገቤ ሶፋው ላይ የሚተራመሱት ልጆቼ ላይ አይኔ አረፈና ላሰብኩት ተፀፀትኩ :: ጨዋታው ደራ : ምግቡ ቀረበ : መጠጥ ተቀዳ : የሁላችንም ልጆች እየተሩዋሩዋጡ ቤቱን አደመቁት :: ሁለቱም ጥንዶች በየሰበባ ሰበቡ ሲጎሻሸሙ : ሲጎነታተሉ : ሲተቃቀፉና ሲሳሳሙ እያየሁ ቀናሁባቸው :: በዚህ ሁሉ መሀል ጠይሙ ባሌ ከነጮቹ መሀል ተደባልቆ አንዴም ወደኔ አልተመለከተም : እንዴም አላናገረኝም : አይኖቻችን በድንገት ከተገጣጠሙ እንኩዋን የሱ የኔዎቹን በፍጥነት ሲሸሹ አየሁዋቸው ::
"የዛሬው የባሰ ነው " አልኩ በልቤ :: ከላይማ በውሸት ፈገግታ እየተፍለቀለኩ ሰዉን መምሰል ተክኜበታለሁ :: ልጆቼ ብዙም አላስቸገሩምና ጥሩ ጊዜ አሳለፍን ...ከኔ አዲሱን የባሌን ፀባይ ከማፍተልተል በስተቀር :: አመሻሹ ላይ ጋባዦቻችንን አመስግነን እንግዶቹን ተሰናብተን ወደቤታችን አመራን :: ያው የተለመደው ፀጥታ መኪናችንን ወረሰው ...አቤት ድሮ ለማውሪያ ጊዜ ያላጠረንን ያህል ...የዛሬን አያድርገውና :: ቀስ ብዬ ወደባሌ ተመለከትኩ ::
መንገዱ ላይ አይኑን አቡዞ በሀሳብ የነጎደ ይመስላል :: የት ይሆን ያለው ? ምን ይሆን የሚያስበው ? "ቆንጆ ጊዜ አሳለፍን አይደል ?" አልኩት በድንገት የሄደበትን አለም ለማደፍረስ :: "አዎ " አጭር መልስ :: እኔ ግን ቀጠልኩ "ፈረንጆች ግን ደስ ሲሉ ...ፍቅራቸው አይደብቁም " ወዴት እንደምሄድ የገባው ባሌ "ሰው ፊት መላላስና መተቃቀፍ የኛ ባህል አይደለም " ቀጭ ያለች መልስ ወረወረልኝ ::
"ምነው ድሮ ታቅፈኝ ትስመኝ ነበር ?" ቁና ተነፈሰ ...አንዳችም አልመለሰም :: ብዙም ሳንቆይ ቤታችን ደረስን :: በሩ አጠገብ መኪናውን አስተካክሎ አቆመና ...ልጆቹን ሳወርድ እንዳይከብደኝ መሆኑ ነው ...ዘሎ ወርዶ የቤቱ በርጋ ሲደርስ "አግዘኝ እንጂ " ብዬ አንባረቅሁበት :: "ምን አስጮኸሽ ...በሩን ልከፍት ነበር " አለና በንዴት በሱ በኩል ያለውን በር ከፍቶ ትልቅዋን ልጄን አንጠለጠላት ::
እጅዋ ተገነጠለ ብላ ነፍሴ ተሳቀቀች :: በድንገት እንባዬ ገነፈለና ትንሹን ልጄን ከታሰረበት ወንበር ልፈታ ጎንበስ ስል ድንቡሼ እግሮቹ ላይ ተንጠባጠበ :: እዛው እንዳጎነበስኩ "አምላኬ ሆይ አለህ ?" ብዬ አንሾካሾኩ :: አዎን ...ለሁለት ሳምንት የሚሆን ኩርፊያዬን መሰነቄ ልቤ ተረድቶታል :: እንዴታ ...እሱማ ባህላችን አይደል ! ጉዴን አላወቅኩ ...
ይቀጥላል ...........
የመወያያ ግሩፑን ይቀላቀሉን
@ethio_lifes_group
@ethio_lifes_group
@ethio_lifes_group
╔═══❖• •❖═══╗
@fkrn_be_kalat
╚═══❖• •❖═══╝
4 any comment
@fkrn_be_kalat_bot
❥❥________⚘_______❥❥
829 views✧ زوجة الفيلسوف ✧, 15:52